Professional Documents
Culture Documents
Agri Culture
Agri Culture
በሀገራችን የግብርና ባለሙያዎች 90% የፖለቲካ ተልዕኮ አስፈፃሚዎች ናቸው፡፡ ከቀሪ 10% ሥራቸው
በአብዛኛው ደላላዎች ሆነው ማዳበሪያ መሸጥና ማደል ይገኝበታል፡፡ ካድሬ የሆኑ የገበሬው ህዝብ አባላትን
በውሸት ሞዴል ገበሬ እያሉ ማስመረቅም አንደኛው ስራቸው ነው፡፡ በዚህ ሥራቸውም ከግብርና ባለሙያነት
ወደ ፖለቲካ ባለሙያነት ሙሉ ለሙሉ ተሸጋግረዋል፡፡
በአንድ ወቅት በኦሮሚያ ክልል በመንገድ ዳርቻ በባሬስታነት ቡና በቃርጣ ውስጥ በማፍላት የምትደዳደር
አንዲት ወጣት ሴት በኢቢሲ እንደ ሴት ገበሬ ቀርባ መንግስት የእርሻ ቦታና የመንቀሳሻ ገንዘብ ሰጥቷት ወደ
ሞዴል ሴት ገበሬነት እንደተቀየረች ስትቀርብ ታየች፡፡ የሚገርመው ነገር በቀረበች ማግስት በኢቢሲ ያይዋት
የሚያውቋት ሰዎች ቡና የምታፈላበት ድረስ ሄደው እንዴት በአንድ ቀን ከባሬስታነት ወደ ሞዴል ገበሬነት
እንደተቀየረች ሲጠይቋት 500 ብር ተከፍሏት በአንድ ሀብታምገበሬ ማሣ ወስደዋት የምትናገረውን
አለማምደዋትና ቀርፀዋት እንደነበር አጋለጠች፡፡
መንግስት ይህን ያህል ሞዴል ገበሬዎችን አስመርቄአለሁ እያለ በሌላ በኩል የሴፍቲ-ኔት፣ የግሎባል ፈንድና
ሌሎች የውጪ በጎ-አድራጎት ድርጅቶች ዕርዳታን የምግብ ዋስትናን ለማስጠበቅ መቀበሉ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡
ረሃብና ቸነፈር ግብርና ባለበት የገጠሩ ክፍል ሆኖ ሳለ ሞዴል ገበሬዎች የት ሄደው ነው ችግሩ ተፈጠረ
የሚባለው? 84% የህዝባችን ክፍል በግብርና ተሠማርቷል ተብሎ የተራበውም እራሱ ገበሬው መሆኑ አንደበት
ዘጊ ነው፡፡ እንዴትስ ከ 14% በላይ ህዝብ ለረሃብ ይጋለጣል?
አንዳንድ በግላቸው ጥረት ሀብት ያፈሩ ገበሬዎችን በእኔ ድጋፍ ሀብት አፍርተዋል በማለት ለሚዲያ ግብዓት
መለፍለፉ የተለመደ ነው፡፡ በአንድ በኩል ደላላ ሆኖ ማዳበሪያ እየሸጠ በሌላ በኩል ለገበሬው ህዝብ ቆሜአለሁ
ማለቱ አደናጋሪነቱን ያሳያል፡፡ እንደሚታወቀው በየገጠሩ ክፍል በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ በገበሬው ላይ
የማዳበሪያ ዕዳ እየቆለለ መሆኑ ደግሞ በገበሬው ላይ ምን ያህል እየቀለደ እንዳለ ያሳያል፡፡ ይህም የገጠሩ ህዝብ
ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ ከፍተኛ የፖለቲካ ተቀባይነት ካገኘው ብሎ ለማሰቡ አጠያያቂ አይደለም፡፡
በአሁን ጊዜ ገበሬው በግብርና ሥራ ተስፋ ቆርጦ ለም በሆኑ መሬቶቹ ላይ ሳይቀር መሬት አድራቂውን ባህር
ዛፍ አየተከል ይገኛል፡፡ የማዳበሪያ ዕዳና እና የምርት መጠንም አላምር ያለው ገበሬ እንደ አማራጭ
የማይወሰደውን ባህር ዛፍ ተከላ መርጧል፡፡ ምንም እንኳን የባህር ዛፍ ተከላ የረጅም ጊዜ የመሬት ለምነት
መጥፋትን እንደሚያስከትል ገበሬው እራሱ ቢያውቅም ግብርናችን ማፈሪያ እየሆነ ስለመምጣቱ ጠቋሚ
ነው፡፡