You are on page 1of 3

ጸጋ

በተለምዶ ፀጋ ሲባል ወደ አእምሮአችን የሚመጣ ሃሳብ አለ። ይህ ሃሳብ እንደ አደግንበት ማህረሰብ አስተሳሰብና እይታ ይወሰናል።
የእግዚአብሔር ቃል በሮሜ 12፡1 እንደሚነግረን ግን በአእምሮአችን መታደስ መለወጥ ይኖርብናል። ማለትም በተለምዶ የምናውቀውን
ነገር በእግዚአብሔር ቃል እውቀት መቀየር አለብን ማለት ነው። ሰው ፀጋ ማለት እንዲህና እንዲህ ነው ከሚለን ወጥተን የእግዚአብሔር
ቃል የሚለንን መቀበል አለብን።

ቃሎች ወሳኝ ናቸው። ሃሳብ ከቃላት ጋር የተያያዘ ነው። ድርጊትና እምነት ሃሳባችንን ይከተላል። የተሳሳተ መረዳት የተሳሳተ ልምምድን፤
የተሳሳተ ልምምድ ደግሞ የተሳሳተ ኑሮን ይወልዳል። የተሳሳተ ኑሮ ስንል እግዚአብሔር ልንኖረው ያላቀደልን ማለታችን ነው።

ፀጋን በእግዚአብሔር ቃል በመመልከት እግዚአብሔር ወደ አዘጋጀልን የፀጋ ሙላት እንገባለን። ስለዚህ ፀጋ ምንድን ነው የሚለውን ቃል
በቃልነቱ ሳይሆን በተሸከመው ሃሳብ እንመልከተው።

1. ከዘላለም ዘመናት በፊት የተሰጠን ነው።

2 ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 1፡9 ያዳነን በቅዱስም አጠራር የጠራን እግዚአብሔር ነውና፥ ይህም እንደ ራሱ አሳብና ጸጋ መጠን ነው እንጂ
እንደ ሥራችን መጠን አይደለም፤ ይህም ጸጋ ከዘላለም ዘመናት በፊት በክርስቶስ ኢየሱስ ተሰጠን፥

10-11 አሁን ግን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መገለጥ ታይቶአል። እርሱ ሞትን ሽሮአልና እኔ ሰባኪና ሐዋርያ አሕዛብንም
አስተማሪ እንድሆን በተሾምሁበት በወንጌል ሕይወትንና አለመጥፋትን ወደ ብርሃን አውጥቶአል።

ሐዋርያው ጳውሎስ መከራን እየተቀበለ ያለው ስለሚሰብከው ወንጌል እንደሆነና ይህ ወንጌል ምን እንደሆነ ለመንፈሳዊ ልጁ ጢሞቲዎስ
ሲነግረው፤ ወንጌል ከዘላለም ዘመናት በፊት በክርስቶስ ለእኛ የተሰጠንን አሁን በጌታ በኢየሱስ መገለጥ እየታየ ያለውን የእግዚአብሔርን
ፀጋ የሚገልጥና ወደመታየት የሚያመጣ ነው ይላል። በዚህ ክፍል መሰረት ፀጋ የተሰጠን ከዘላለም ዘመናት በፊት እኛ በሌለንበት ጊዜ፤
ክፉም ሆነ ደግ ባላደረግንበት ጊዜ ነው።

ፀጋ እግዚአብሔር ለያዘልን የከበረ አሳብ እንድንበቃ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንዲያው የተሰጠን ሃብት ነው። እግዚአብሔር ሲጠራህ
አሁን ያለህበትን ሁኔታ አመሳክሮ ሳይሆን አስቀድሞ ከያዘልህ አሳብ አንፃር ነው። መጠራትህ በእርሱ ዘንድ እንደተያዘልህ አሳብና ፀጋ
መጠን ነው እንጅ እንደ አንተ ፍላጎት፤ እውቀት ወይም ችሎታ መጠን አይደለም። “ይህም እንደ ራሱ አሳብና ጸጋ መጠን ነው እንጂ
እንደ ሥራችን መጠን አይደለም፤”

አንዳንድ ጊዜ ክርስቲያኖች በአለም በሃብት ወይም በተሰጥኦ የታወቁ ሰዎችን ያዩና ይህ ሰው ወይም ይህች ሴት ወደጌታ ቢመጡ
እንዴት ጌታን ያገለግሉ ነበር ብለው ይቀናሉ። ይህ ድንቅ የእግዚአብሔር ቃል ግን የሚነግረን ጥሪ የሚጀምረው ከእግዚአብሔር ነው።
ሲጠራህ ስለአንተ ላሰበው አሳብ የሚያበቃህ ነገር ሁሉ በነፃ ያኔ ተዘጋጅቶልሃል። ጥሪው እንደ አሳቡና ፀጋው መጠን ነው።
እግዚአብሔር የሰውን የታመቀ ችሎታና ብቃት አስቀድሞ አይቶ ሳይሆን ሰውን የሚጠራው ለጠራው ሰው ምን እንደሚሰጠውና
በሰጠው ነገር ምን እንዲሆን አስቦ ነው።

2. ፀጋ የእግዚአብሔር አምላክ ብቻ የነበረውን ነገር አንተ በክርስቶስ እንድትካፈል የተዘጋጀ መንገድ ነው።

ጳውሎስ እንዳለው ሕይወትና አለመጥፋት የፀጋው ውጤቶች ናቸው። ሕይወትና አለመጥፋት ወይም ኢመዋቲነት የአምላክ ባህሪ እንጅ
የፍጡር ባሕሪ አይደለም። ይህን ባህሪ ለአንተ በነፃ ሲያካፍልህ ፀጋ ይባላል።

እግዚአብሔር በባህሪው ጻድቅ ሆኖ ሳለ በክርስቶስ ስራ አማካይነት ይህንን የጽድቅ ባህሪውን ሲያካፍልህ አንተ ጻድቅ ትሆናለህ።
የተካፈልከው ጽድቅ ፀጋ ይባላል። የእግዚአብሔርን ጽድቅ በክርስቶስ ስትካፈል በጸጋው ጸደቅህ። ቀጥሎ ያለውን ክፍል እንመልከት፡
ወደ ሮሜ ሰዎች 3፡21 አሁን ግን በሕግና በነቢያት የተመሰከረለት የእግዚአብሔር ጽድቅ ያለ ሕግ ተገልጦአል፥ 22 እርሱም፥ ለሚያምኑ
ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው፤ ልዩነት የለምና፤
23 ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤
24 በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ።
እግዚአብሔር ዘላለማዊ አምላክ ሆኖ እያለ አንተ በክርስቶስ አማካይነት ይህን የዘላለም ሕይወት ስትቀበል ዘላለማዊ ትሆናለህ።
ዘላለማዊ ሕይወት ጸጋ ነው። “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ
ከእናንተ አይደለም፤” ኤፌ 2፡8 በአጠቃላይ እግዚአብሔር የሆነውንና ያለውን እንድትካፈል የሚያስችልህ ፀጋ ይባላል። ይህም ጸጋ
የተሰጠን እግዚአብሔር ለእኛ አስቀድሞ እንደአሰበልን አሳብ መጠን ነው። ይህ አስቀድሞ የታሰበ አሳብ ምንድን ነው ? የእግዚአብሔርን
በጸጋው በመካፈል እርሱን መምሰል ነው።

3. ፀጋ የእግዚአብሔር ፍቅር በተግባር ሲገለጥ ነው።

ወደ ኤፌሶን ሰዎች 2፡4 ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥


5 ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና፥
6-7 በሚመጡ ዘመናትም በክርስቶስ ኢየሱስ ለእኛ ባለው ቸርነት ከሁሉ የሚበልጠውን የጸጋውን ባለ ጠግነት ያሳይ ዘንድ፥ ከእርሱ
ጋር አስነሣን በክርስቶስ ኢየሱስም በሰማያዊ ስፍራ ከእርሱ ጋር አስቀመጠን። 8 ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር
ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤
9 ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም።

በዚህ ክፍል ያለውን እውነት ጠቅለል አድርገን ብናየው እንዲህ ማለት እንችላለን

እግዚአብሄር እኛን እጅግ ትልቅ በሆነ ፍቅር ወዶናል። ሆኖም ግን በበደላችን ሙታን ስለነበርን ይህን ፍቅሩን ለማርካት አልቻለም ።
ከቸርነቱ ብዛት የተነሳ ልጁን በእኛ ቦታ እንዲሞትልን አሳልፎ በመስጠት ከሞት አዳኖን አስቀድሞ ለአሰበልን አሳብ አበቃን። ይህን
ያደረገው ሞት ለሚገባን ለእኛ እንዲሁ ባደረገው ነገር የፀጋውን ብዛት ያሳይ ዘንድ ነው።

 እግዚአብሔር አጋፔ የሆነውን ፍቅሩን ለሰው ልጅ የገለጠበት መንገድ ፀጋ ነው።

አጋፔ ፍቅር ከተወዳጁ ለመወደዱ ምንም ምክንያት ሳይኖር ከወዳጁ ፍላጎት የመነጨ ፍቅር ነው። የአንድ አቅጣጫ ፍቅር ነው።
ከእግዚአብሔር ወደ ሰው ያለ ፍቅር ነው። እግዚአብሔር ሰውን ለመውደድ ከሰው አስቀድሞ ያየው ምክንያት የለም። ሰው
የሚጠበቅበት ለዚህ ፍቅር ምላሽ መስጠት ብቻ ነው።

ፀጋም እንዲሁ ነው። በጎነት የተደረገለት ሰው በጎነት እንዲደረግለት የሚያስችል ምንም ምክንያት ሳይኖር የሰጪው ፍቅር ምክንያት ሆኖ
የሚደረግ ቸርነት ነው።

ወደ ሮሜ ሰዎች 4፡4 ለሚሠራ ደመወዝ እንደ ዕዳ ነው እንጂ እንደ ጸጋ አይቈጠርለትም፤


5 ነገር ግን ለማይሠራ፥ ኃጢአተኛውንም በሚያደድቅ ለሚያምን ሰው እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርለታል።

የመወያያ ጥያቄዎች

1. የእግዚአብሔርን ፀጋ በራስህ መረዳት እንዴት ትገልፀዋለህ?


2. ፍቅርና ፀጋ ያላቸው ግንኙነት ምንድን ነው?
3. እግዚአብሔር ሃጢያተኛውን ለምን ያጸድቀዋል? እንዴትስ ያጸድቀዋል?

የማዛመድ ጥያቄዎች
1. በሮሜ 6፡14 ከፀጋ በታች እንጅ ከህግ በታች አይደላችሁም ይላል። ይህን ከአንተ የክርስትና ሕይወት ኑሮ ጋር እንዴት
ታየዋለህ?

2. እግዚአብሔር ከእርሱ በሆነ ነገር ለእርሱ እንድንኖር ከፈለገ አሁን ከእርሱ በሆነ ነገር እየኖርክ ነው?
3. ከእርሱ በሆነው ነገር በሁሉም የሕይወት ዙሪያህ መኖር ብትጀምር ምን አይነት ሰው የምትሆን ይመስልሃል?

You might also like