Professional Documents
Culture Documents
ወንጌል ያስፈራን ክርስቲያኖች
በዚህ ዘመን በምንኖር አማኞች የዕለት ተዕለት ኑሮና ግንኙነት ውስጥ ያሉ መንፈሳዊ እሴቶች፣
እሳቤዎችና ምልክቶች ቀሰ በቀስ እየተሟጠጡና እየጠፉ ናቸው ። አብዛኛዎቻችን መንፈሳዊ
እርቃናችንን የቀረን ክርስቲያኖች እየሆንን የመጣን ይመስላል ። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ
መንፈሳዊነት እንደ ኋላ ቀርነት እየታሰበ ነው። በቀድሞ ዘመን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሰው
የሚከበረው በክርስቲያንነቱና በመንፈሳዊነቱ ነበር፤ አሁን ግን ዋጋ አሰጣጣችን እየተቀየረ በመምጣቱ፣
ለቤተ ክርስቲያን በሚሰጠው በአሥራት እና በፍቅር ስጦታ ገንዘብ፣ በእውቀቱ ወይም በትምህርት
ደረጃው፣ በሙያውና በሀብቱ ሆኖል። አንድ ሰው ትርፍ የሚያስገኝልን እስካልሆነ ወደ ቤተ ክርስቲያን
መምጣቱም ሆነ መሄዱ አያስደንቀንም። እያንዳንዳችንም ሆነ፣ቤተ ክርስቲያን
መንገዳችንን እየቀየስን ያለነው በመጽሓፍ ቅዱስ ዋጋ አሰጣጥ ሳይሆን፣ በዚህ ዓለም አሠራረና ስርዓት
እየሆነ ነው።
በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የወንጌሉን ቃል ለዓለም በማድረስ የዚህን ዓለም እኩይ ዕለት ዕለት እያሸነፍን
መሄድ የምንችለው እንዴት ነው? ከዚህ ሁሉ ክፉ አስተሳሰብና ተግባር እያንዳንዳችን በመዳን ቃሉ
የሚፈልግብንን ሕይወት መኖር የምንችለው ምን ብናደርግ ነው? በምድር ላይ ያለችው የክርስቶስ
ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን በመላው አገሪቱ በመስፋፋት ትውልዱን በወንጌል ኃይል ተጽዕኖ ወደ
እግዚአብሔር የመመለስ ጥሪ አለባት፤
የሰው ልጆችን ከታሰሩበት የኃጢአት፣ የዓለምና የሠይጣን እስራት ነፃ እያውጡ በሳል የኢየሱስ
ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ማድረግ ይቻላል? እንዴት? ለእነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መልሱ ጌታ ራሱ በልዩ
ጉብኝት ወደ ምድራችንና ወደ ሕይወታችን መምጣት አለበት ( ልዩ መንፈሳዊ ተሓድሶና መነቃቃት
ያስፈልገናል የምንለው ለዚህ ነው)ይህ እንዲሆን ደግሞ የጌታን መንገድ መጥረግና ማስተካከል
ያስፈልገናል። ለፈጣን መለኮታዊ ጉብኝት የመንገድ ጠረጋውን ሥራ የሚሠሩ አገልጋዮችን
እግዚአብሔር እንዲቀሰቅስልን ብንጸልይ መጎብኘታችንን እግዚአብሔር ያፈጥነዋል። ለወንጌሉ
አገልግሎት የኋላ ደጀን የሚሆኑ፣እንዲሁም ምዕመናንን፣ በአጥቢያና በቤተ እምነት ደረጃ ያሉ ልዩ ልዩ
የአገልግሎት ክፍሎችን በጸሎት የሚደግፉ በቂና ተዋጊ የጸሎት ቡድኖችን በማቋቋም የቤተ ክርስቲያን
አገልግሎቷ ሠፊ የጸሎት ሽፋን እንዲያገኝ ማድረግ ያስገልጋል።
የተዘጉ ቦታዎች እንዲከፈቱ የምንፈገልግ ከሆነ ፣ በቅጡ የተደራጀና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የታጠቀ
(የተሞላ) የጸሎትሕይወት እጅግ አስፈላጊ ነው። ታላቅ የሆነ መንፈሳዊ ተሓድሶና መነቃቃት
እንዲሆንልን የምንፈልግ ከሆነ የእግዚአብሔር ሀልዎት የሚገኝበት የጸሎት ሕይወት
ያስፈልገናል።የጌታን መንገድ አዘጋጁ የሚለው የነቢዩ ኢሳይያስ መልእክት በዚህም ዘመን ለምንኖር
አማኞች መልእክት አለው። የጌታን መንገድ ስናዘጋጅ ጌታ ይመጣል።
ካሱ ቦስተን
መቅደሱ ይፈተሽ
ካሱ ቦስትን
ጋብቻ
መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር
ይፈርድባቸዋል።
(ወደ ዕብራውያን 13፥4)
በመጀመሪያ ደረጃ እግዚአብሔር ጋብቻን በሁሉ ዘንድ ክቡር ይሁን ነው ያለው በሁሉ ዘንድ ሲል
በሴቷም በወንዱም በእስልምናውም በክርስትናውም በማንኛውም የሰው ዘር ሊከበር ይገባዋል ነው
የሚለው እንዲሁ እንደቀልድ የሚታይ ነገር አይደለም እንደቀልድ ዛሬ ተገብቶበት ነገ የሚወጣበት
እንደዘበት የሚታይ ጉዳይ አይደለም ነው የሚለን ።
ካሱ ቦስተን
ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን?
የሠዎችን ልጆች በማዳን አዲስ ምዕራፍ አዲስ ኪዳን የከፈተው ጌታ ኢየሱስ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት
ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፣ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው፡፡ ለብዙ ጊዜ
ደቀመዛሙርቱን በተለያዩ መንገዶች አስተምሯል አንዳንዴ በቃል በምሳሌ በተግባር ዛሬ ደግሞ በዚህ ክፍል ፍቅርን
በተግባር ሲያስተምራቸው እንመለከታለን፡፡
በዚህ ክፍል ያደረገው ነገር ደቀመዛሙርቱን አስደንግጦአቸዋል ምክንያቱም እግር ማጠብ ዝቅ ማለትን
ያመለክታል በተለይም አንድ መምህር ተማሪዎቹን ጌታ አገልጋዮቹን ዝቅ ብሎ እግር ማጠብ የማይታሰብ ነው፡፡
ሌላውን የአካል ክፍል ቢሆን ችግር የለውም ነበር ጌታ ኢየሱስ ግን ተነስቶ እግራቸውን አጠበ በታጠቀበትም ማበሻ
ጨርቅ አበሠ በጣም የሚገርም ነው፤ ደቀ መዛሙርቱ ከዚህ ቀደም እንዲህ ሲደረግ ሠምተውም አይተውም
አያውቁም፤ ምናልባትም መምህር የሚባሉት ጌታ የሚባሉት የከበሬታ ወንበራቸው ላይ ቁጭ ብለው እግር
ሲያሳጥቡ ነው የሚያውቁት ዛሬ ግን የተገላቢጦሽ ሆነባቸው፡፡ ለዚህ ነው ስምዖን ጴጥሮስ የእኔን እግር ለዘላለም
አታጥብም ያለው፡፡
ጌታ ሆኖ መምህር ሆኖላቸው ዝቅ ብሎ እግራቸውን አጠበ፡፡ እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ
ከተቀመጠ በኋላ አንድ ጥያቄ ጠየቃቸው ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን? አዎን መምህር ነኝ ደግሞም ጌታ
ነኝ እንዲህ ሆኖ ሳለ እኔ ይህንን ካደረኩላችሁ በተግባር ካሳየኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ልትተጣጠቡ
ይገባል አላቸው፡፡ ጌታ ኢየሱስ ሠዎች ሊኖራቸው ስለሚገባው ፍቅር እራሱን ዝቅ በማድረግ በተግባር ገለፀ፤ እኔ
እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ፡፡
የዘመናችን አገልጋዮች ቄሶች፣ መምህራን፣ ነቢያት፣ ፓስተሮች፣ ሃዋርያት እንዲሁም ሽማግሌዎች . . . እስቲ
እንደ ጌታችን እንዳስተማረንም ወርደን የደቀመዛሙርቱን እግር እንጠብ ፍቅርንም ለሕዝብ በተግባር እናሳይ
የከበሬታ ወንበርን አንፈልግ፡፡
ወዳጄ ዛሬ ይህ ምሳሌ የተሠጠን ፍቅራችንንና ትህትናችንን ዝቅ እስከ ማለት ድረስ እንድንገልፅ እንጂ በየቤቱ
እየሄድን የሠዎችን እግር እንድናጥብ አይደለም ነገር ግን በፍቅርና በትህትና ተገቢ እስካማይሆንበት ድረስ እንኳ
ሠዎችን በትህትና ይቅር እንድንል እንድንወድድ ነው፡፡
ጌታ ኢየሱስ እኔ እንደወደድኋሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ አለ፡፡
እንዲሁም እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያወቃሉ አለ፡፡(ዮሃ
13:34)
ወዳጄ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ነህን? ትህትና በተሞላበት ሕይወት ባልንጀራህን ውደደው እግር እስከ ማጠብ ድረስ
እስከ መጨረሻ ውደደው፡፡ እኔ እንደወደድኋችሁ ነው ያለው ጌታ ኢየሱስ፡፡ ለመሆኑ የተወደድክበትን ፍቅር ጥልቀት
ታውቀዋለህን? ከአእምሮ በላይ ነው ፍፁም፣ ጥልቅ እውነተኛ በሆነ ፍቅር ተወድደሃል የኢየሱስን ፍቅር ልትገልፀው
ትችላለህን? ቆሻሻህን ጉድህን ሸፍኖ በአደባባይ ሳያወጣ በደሙ አጥቦልሃል ያለፈውን ጉድፍ ከሰው ፊት
የማያቀርበውን ሃጢዓትህን ይቅር ብሎልሃል ዳግመኛ ላያስበውም ቃል ገብቶልሃል ፍቅሩን ትዘነጋለህ? ታዲያ እርሱ
እንዲህ ከወደደህ ጉድህን በአደባባይ ሳያወጣ ይቅር ካለህ ለምን የባልነጀራህን ጉድ ታወጣለህ? ለምን ስለ ባልንጀራህ
ቆሻሻ ታወራለህ? ዓመት ሁለት ዓመት ዓምስት ዓመት የቆየ ቁርሾ እየነቀስክ ለምን ታወራለህ፡፡ ይቅር የተባልክበትን
ታላቅ ፍቅር አስብ እንደዛው ጌታ እንደ ወደደህ ባልንጀራህን ውደድ ይቅር በለው፡፡ ይህ ፍቅር በመካከላችን በእውነት
ይኑር፡፡
በጩኸታችንና በዝማሬያችን ብዛት ሳይሆን በፍቅራችን ብዛት በእውነት የጌታ ኢየሱስ ደቀ መዝሙር መሆናችንን
ሰዎች ሁሉ ይወቁ፡፡
ተባረኩልኝ፡፡
ካሱ ቦስተን
ካሱ ቦስተን
ወስጤ በሚጮህ የቅዱሳን ፍቅር እጦት ላይ ያለኝን ሃሳብ በፍቅር ብዕሬ አስፍሬ
ብቅ ብያለሁና ሳትሰለቹ ማንበባችሁን ቀጥሉ።
ካሱ ቦስተን
የክርስቶስ ክቡር ደም
የክርስቶስ ደም የሚቀድስ ከመሆኑ የተነሳ፣ አሁንም እንደገና ክቡር ነው።
ኃጢአታችንን በማስወገድ ያጸደቀን ያው ክቡር ደም መልሶ ደግሞ አዲሱን ሰው
በመቀስቀስ ኃጢአትን በማሸነፍና የእግዚአብሔርን ትእዛዛት በመፈጸም እንዲኖር
አበርትቶ ወደ ፊት ያስኬደዋል። ክቡሩ ደም ደካማውን ሰው ያበረታዋል።
ለቅድስና ህይወት መነሳሳትም ሆነ ለጽድቅ ኑሮ ከኢየሱስ ደም ሥሮች
ከሚፈሰው ክቡር ደም በላይ የላቀ ቀስቃሽ ኃይል ከቶ የለም።
ካሱ ቦስተን
በመንፈሳዊ ሕይወት እያደግን ስንሄድ የደስታችን ምንጭ ምን መሆኑን እንገነዘባለን። መሰረታዊ እውነቶችን
በአግባቡ እየተረዳን ስንመጣ ሙሉ በሙሉ ልንገልጸው የማንችለውን የዘለዓለም ሕይወት፣ ደስታና ሰላም
የሰጠንን እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት እንናፍቃለን። ከነዚህ መሰረታዊ እውነቶች መካከል አንዱ በጌታ
በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የዘለዓለም ሕይወትን ያገኙ ሁሉ የክርስቶስ አካል የሆነችው የቤተ ክርስቲያን
ብልቶች መሆናቸው ነው።
አዲስ ኪዳን ስለዚህ ሲናገር፤ “እናንተም የክርስቶስ አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ” ይላል (1 ኛ
ቆሮንቶስ ምዕራፍ 12:27) ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ ሆና እንድትገኝ ለክርስቶስ
ታጭታለች። ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን እንደዚህ ይገልጸዋል፤ “በእግዚአብሔር ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፣
እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና፣” 2 ኛ ቆሮ 11፡2
ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን በላከው መልእክት ደግሞ፡ “በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለ
እርስዋ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፣ እድፈት ወይም የፊት መጨማደድ ወይም እንዲህ ያለ ነገር ሳይሆንባት፣ ቅድስትና
ያለ ነውር ትሆን ዘንድ ክብርት የሆነችን ቤተ ክርስቲያን ለራሱ እንዲያቀርብ ፈለገ።” ይላል (ኤፌሶን 5፡27)።
ልዑል እግዚአብሔር በክቡር ልጁ ደም የዋጃት የቤተ ክርስቲያን፣ የክርስቶስ አካል፣ ብልቶች ከሆንን እና ጌታ
አምላክ ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት፣ ንጽህት እና ነውር የሌለባት እንድትሆን ካዘዘ፤ እኛም እያንዳንዳችን
በቃሉና በመንፈሱ በመታጠብ ልንቀደስና ለእርሱም ቅዱስ ቤተ መቅደስ ለመሆን ልንሰራ ያስፈልጋል።
ዛሬ በአዲስ ኪዳን ዘመን ያለን ክርስቲያኖችም እንዲሁ በገዛ ራሱ ደም የዋጀንን እና የዘለዓለምን ሕይወት
የሰጠንን ጌታ የምናመልከው በቤተ ክርስቲያንና በህብረት ብቻ ሳይሆን በግላችን፣ በአእምሮአችን፣
በሰውነታችን፣ በስሜታችንና በማንነታችን ሁሉ ነው። ፈርጀ ብዙ በሆነው በግል ኑሮአችን እንዲሁም
በቤተሰባችን እና በግንኙነቶቻችን ሁሉ መካከል እርሱን ማክበርና ደስ የሚያሰኘውን ለማድረግ መትጋት
እንዳለብን እንዲህ ሲል መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል ያዝዘናልም፤
“እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ”
ክፍል 2.
“እንግዲህ እንደ እግዚአብሔር ምርጦች ቅዱሳን ሆናችሁ የተወደዳችሁም ሆናችሁ፣ ምሕረትን ርኅራኄን፣
ቸርነትን፣ ትሕትናን፣ የዋህነትን፣ ትዕግሥትን ልበሱ፣እርስ በርሳችሁ ትዕግሥትን አድርጉ፣ ማንም በባልንጀራው
ላይ የሚነቅፈው ነገር ካለው ይቅር ተባባሉ፣ ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተ ደግሞ እንዲህ አድርጉ፣
በእነዚህም ሁሉ ላይ የፍጻሜ ማሰሪያ የሆነውን ፍቅርን ልበሱት። በአንድ አካልም የተጠራችሁለት ደግሞ
የክርስቶስ ሰላም በልባችሁ ይግዛ። የምታመሰግኑም ሁኑ፣ የእግዚአብሔር ቃል በሙላት ይኑርባችሁ፣ በጥበብ
ሁሉ እርስ በርሳችሁ አስተምሩና ገስፁ፣ በመዝሙርና በዝማሬ በመንፈሳዊም ቅኔ በጸጋው በልባችሁ
ለእግዚአብሔር ዘምሩ፣ እግዚአብሔርን በእርሱ እያመሰገናችሁ በቃል ቢሆን ወይም በሥራ የምታደርጉትን
ሁሉ በጌታ በኢየሱስ ስም አድርጉት።” (ቆላስይስ 3፡12-17)
ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን ስንቀበል በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ከእግዚአብሔር ዳግም ተወልደናል፣ ስለዚህ አዲስ
ፍጥረቶች ነን። ኃጢዓት ካመጣብን የዘለዓለም ሞት ድነናል፣ ስለዚህም በክርስቶስ ጽድቅ ምክንያት ጻድቃን
ሆነናል። በዓመጻችን ምክንያት ተጣልተነውና ተለይተነው ከነበረው ከአምላካችን ከእግዚአብሔር ጋር
በክርስቶስ ደም ታርቀናል፣ ስለዚህም የእግዚአብሔር ልጆች ነን። ይገዛን ከነበረውና ዛሬም የማያምነውን
ዓለም ከሚገዛው ከጨለማው ገዥ ከዲያብሎስ፣ ከጭፍሮቹና ከአጋንንት ስልጣን ነጻ ወጥተን ወደ ኢየሱስ
ክርስቶስ የፍቅር መንግሥት ፈልሰናል፣ በጨለማው ገዥና በሥርዓቱም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጥቶናል።
ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ሲገለጽ እኛም ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር እንድንገለጥና አብረነው በሕይወት
እንድንነግስ ታጭተናል። እነዚህን እውነቶች ሁሉ እንዳንረሳ፣ እንዳንደክምና እንዳንታክት፣ ወደ እውነት ሁሉ
እንዲመራንና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገልንን እና ያስተማረንን የሚያስታውሰንን መንፈስ ቅዱስን እንደ
ርስታችን መያዣ ተቀብለናል
(ዮሐ 1፡12-13 ዮሐንስ 3፡16-18 ሮሜ 5፡1-2 ሮሜ 6፡6 2 ኛ ቆሮ 5፡17 ቆላስይስ 1፡13-14 ሉቃስ 10፡19-20)
በዚህ ሁሉ እውነት ለተከበብን ክርስቲያኖች ነው ታዲያ ሐዋርያው ጳውሎስ “እንደ ተወደዱ ልጆች
እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ” የሚለን። ልጆች በብዙ መንገድ ወላጆቻቸውን እንደሚመስሉ ሁሉ እኛም
በክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዳግም የተወለድን ክርስቲያኖች ዳግም የወለደንን እግዚአብሔርን እንድንመስል
ይጠበቅብናል። ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎአል፡
“እናንተ ስለነገርኋችሁ ቃል አሁን ንጹሐን ናችሁ፣ በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር
ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም። እኔ የወይን ግንድ ነኝ
እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና፣ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፣እርሱ
ብዙ ፍሬ ያፈራል። ....ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል።” ዮሐንስ ወንጌል
15፡3-8
ክፍል 3
እፉኝት እንደማንኛውም እንሰሳ ስትሆን፣ የእድሜ ጣሪያዋ አርግዛ እስከምትወልድ ብቻ የተገደበ ነው።
የባሏም እድሜ ከሷ ግንኙነት(ሩካቤ) እስኪያደርግ ብቻ ነው። የመጀመሪያ ሩካቤ ካደረጉ በኋላ የባሏን ብልት
ትበላና ትገድለዋለች። የምታረግዘውም በአንድ ጊዜ ግንኙነት ብቻ ስለሆነ ታረግዝና መውለጃዋ ጊዜ ሲደርስ
ልጆቿ የሚወለዱት እንደ ብዙዎች እንሰሳት በመወለጃ ብልቷ ሳይሆን ሆድዋን በልተው በመቅደድ ስለሆነ
እሷም እንደ ባሏ ትሞትና የወለደቻቸው ልጆች ያለ እናትም ያለ አባትም ይድጋሉ ይህ ሂደት እንግዲህ
ለእፉኝት ቀጣይ የህይወት ሂደት ነው ማለት ነው። ታዲያ ዮሃንስ ለምን እነዚህን ሰዎች የእፉኝት ልጆች
አላቸው ? አይገርምም እፉኝቶች እየተገዳደሉ ሂደት እንዲቀጥል ያደርጋሉ።
ስለዚህ የዛሬውን መልእክቴን ይህን ጥያቄ ጠይቄያችሁ ልለፍ ዛሬ ዮሃንስ ቢኖር እኛን ምን ብሎ ይጠራን ይሆን
??
ስለዚህ መንፈሳዊ ቤት ሆነን ለመሰራት እርስ በርስ ከመነካከስና ከመበላላት ከመጠፋፋትም እራሳችንን
እንጠብቅ እንጠንቀቅም ቃሉ እንደሚለን
'' ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱ ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ። ነገር ግን እላለሁ፥
በመንፈስ ተመላለሱ፥ የሥጋንም ምኞት ከቶ አትፈጽሙ'' ይለናል ። ገላ 5፣15 አሜን !!!
ክፍል 4
“ ...... ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ?” ማቲ 3፣7
ዮሃንስ ከፈሪሳዊያንና ከሰዱቃዊያን ብዙዎች ወደ እርሱ ሲመጡ ሲያይ እነዚህ አብርሃም አባት አለን እያሉ
የሚመጻደቁ በሰዎች ንስሃ መግባት የሚያሾፉ በራሳቸው ላይ ጥፋትን እየከመሩ ያሉ የሃይማኖት ሰዎችን
ያለፍርሃት እያስጠነቀቀ ያሳስባቸው ነበር። ዮሃንስ እነዚህን ሰዎች እያባረረ እያሳደደ ከበስተኃላቸው
የሚከተላቸው ቁጣ የተባለ ነገር እንዳለ በመንፈስ ተረድቶ ሲናገራቸው እናያለን ። ዮሃንስ እየመጣ ያለ ቁጣ
አለ ይህ ቁጣ ደግሞ የሚምር አይደለም የሚያጠፋ እንደደራሽ ውሃ ትልቅ ሃይል ያለው ነው ፣ ይህ እንደ ደራሽ
ውሃ እየመጣ ያለው ቁጣ ደግሞ የተቀመጠውንም፣የተኛውንም፣ ስር ሰዶ የተተከለውንም፣ በተለያየ መሰረት
የተገነባውንም ሁሉ ገንድሶ የመጣል፣ የማፈራረስና የመበታተን ሃይል ያለው ነው ። ከዚህ ኃያል ቁጣ
እንድታመልጡና እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ ማን መከራችሁ እያላቸው ነበር።
ዛሬም እየመጣ ያለ የእግዚአብሄር ታላቅ የክብር ደምና አለ በዚህ በክብር ደመና ውስጥ ደግሞ የሚያጠራ
እሳት አለ። ይህ እሳት የእግዚአብሄር ክብር የሚያርፍበትን ስፍራ የተስተካከለ እንዲሆን የሚያጠራና
የሚያስተካክል እሳት ነው ። ይህ እሳት በውስጥም በውጭም ያለውን ከክብሩ ጋር ሊሄድ የማይችለውን ሁሉ
ያቃጥላል (ልክ ወርቅ በእሳት እንደሚጠራ) ይህ ታላቅ ቁጣ እንዳይመጣብን እንጠንቀቅ። የእግዚአብሂር የክብሩ
ማደሪያ ቤት ሆኖ ለመሰራት ልክ ቤት ሲሰራ ድንጋዩም ብረቱም በእሳት ግሎ በመዶሻ ተቀትቅጦ ተጠርቦ
መልክና ውበት እንደሚያወጣ ሁሉ የእኛም ሁለንተናችን ማለትም መንፈሳችን፣ ነፍሳችን፣ ስጋችን የተመቸ
እንዲሆን በየእለቱ በመንፈስ ቅዱስ እሳት ሊቃኝና ሊሞላ ያስፈልገዋል። ከወይን ጠጅ ይልቅ በየዕለቱ
ልንሞላበት የሚገባን፣ ኢየሱስ እኔ ብሄድና እሱ ቢመጣላችሁ ይሻላችኃል ያለለት ቅዱስ የሆነ መንፈስ አለንና
።
ስለዚህ ወገኖቼ ዛሬ የእግዚአብሄር የክብሩ ማደሪያ ቤት ሆነን ለመሰራት ራሱ የሰላም አምላክ (መንፈሳችንን
፣ ነፍሳችንን ፣ ስጋችንን ) ጌታ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ ያለነቀፋ ሆነን እንድንጠብቀው ሁለንተናችንን ይቀድስ
(1 ኛ ተሰሎንቄ 5፣23 ) አሜን !!!
ክፍል 5
ካላይ ያየናቸው ሰዎች በዓካልና በሃሳብ መሸሽ ካለባቸው ነገር ሲሸሹ የሚያሳይ
ነው በዛሬው ጊዜም በዓለም ዙሪያ የምንኖር እውነተኛ ክርስቲያኖች በአስቸኳይ
መሸሽ ያለብን ነገሮች አሉ። መጥምቁ ዮሐንስ ‘መሸሽ’ የሚለውን ቃል
የተጠቀመበት በዚህ መንገድ ነበር። ዛሬም እኛ ልንሸሻቸው የሚገቡ ጌታ
የማይፈልጋቸው አብረናቸው እየኖርን ያለነው ብዙ የተጣበቁብን ተጋብተናቸው
አብረን እየኖርን ያለነው የህይወት ዘይቤዎች እንደሎጥ ተቀላቅለን
እየኖርንባቸው ያለንበት አካባቢዎች አሉ ከዚህ ህይወት መላቀቅና መሸሽ
አለብን። መንፈሳዊ ቤት ሆነን ለመሰራትና ጌታ እንዲኖርብን ካስፈለገ አንዱ
መንገድ ከገባንበት ጌታ ከማይከብርበት የህይወት ኑሮ ሎጥ ሰዶምን ጥሎ
እንደታዘዘና እንደወጣ ዮሴፍ ከጴጢፋራ ሚስት እንደሸሸ እኛም በአስቸኳይ
ልንወጣ ያስፈልጋል። ዛሬም እንደሎጥ አስቸኩሎ የሚያወጣ የመንፈስ ቅዱስ
ሃይል አለና እራሳችንን ለመንፈስ ቅዱስ እናስረክብ በሃሳብም በዓካልም
እጃችንን ይዞ ያወጣናል።
ካሱ ቦስተን
የልጁን መልክ እንዲመስሉ !
መጽሃፍ ቅዱስ በሮሜ 8፤29 ላይ ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኩር ይሆን ዘንድ አስቀድሞ
ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና ይላል።
ኤፌሶን 1:5 በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ
ወሰነን።
እግዚአብሄር አምላክ አለምን ከመፍጠሩ በፊት የእኔንና የእናንተን ፍጻሜ አዘጋጅቶ ወስኖ
አስቀምጧል። የእኛ ስራ መሆን ያለበት ይህንን የእግዚአብሄርን ሃሳብ አውቀን መራመድና መጓዝ
ነው።
ወገኖቼ እግዚአብሄር አስቀድሞ የእኛን ጉዞ ወይም የእኛን ፍጻሜ አንድያና የበኩር ልጁን
የኢየሱስ ክርስቶስን መልክ እንመስል ዘንድ ነው እግዚአብሄር በእኛ ውስጥ ልጁን መቅረጽና ማየት
ይፈልጋል። እንግዲህ መንፈሳዊ ቤት ሆነን ስንሰራ የቤቱ ፍጻሜና መልኩ መሆን ያለበት ልክ
ኢየሱስ ክርስቶስን መምሰል ነው ማለት ነው። አሜን !!!
አቅጣጫችን ወዴት ነው ??
አንድ ገበሬ እርፉን ለሚጎትተው የበሬዎች ኃይል መገዛትና እርፉን ጨብጦ እነርሱ
ወደሚሄዱበት አቅጣጫ ብቻ መሄድ እንደሚገባው ሁሉ አንድ ደቀ መዝሙርም
የእግዚአብሔርን መንግስት ማለትም ክርስቶስን ካገኘ በኋላ ለመንግስቱ ጉልበት ተሸንፎ
መንግስቱ ወደምትሄድበት አቅጣጫ ብቻ የሚሄድ ነው። ከእግዚአብሔር የተወለደ
የመንግስቱ ደቀመዝሙር በነፋስ መመሰሉና ከወዴት እንደመጣ ወዴትም እንደሚሄድ
አለመታወቁ ለምን ይሆን? በራሱ መንገድና መርህ «እናቴንና አባቴን ልቅበር ልሰናበት»
በሚለው መርህ መመላለስ አቁሞ በመንግስተ ሰማያት ምህዋር ውስጥ ስለገባ
አይደለምን? እናቱንና አባቱን ሊቀብርና ሊሰናበት የሚሄደውንማ ሁሉም ሰው ከየት
እንደመጣ ወዴትም እንደሚሄድ ያውቀዋል የሰው ሁሉ ምልልስ ነውና። ከእግዚአብሔር
ተወልደን የክርስቶስን ማንነት ተካፍለን «ከመንፈስ የተወለደ» ስንሆን ግን
እንቅስቃሴአችን ሁሉ በእግዛኢብሔር መንፈስ የሚመራ፣ በጉ ወደሚሄድበት ብቻ የሆነ
ለሰዎች የማይታይና በሰዎች የማይገመት ይሆናል። ዓለም የሰው ልጆች
እንዲመላለሱበት በቀረጸችው የኑሮ መርህ ሳይሆን በእግዚአብሔር መንግስት ስርዓት
እንመላለሳለን። የሂደታችን አቅጣጫ ሰዎች ወደሚሄዱበት አይደለም በጉ ወደሚሄድበት
እንጂ። እንደ ነፋስ በዚህ ዓለም እንዳለን ይታወቃል፣ ሰዎች ድምጻችንን ይሰማሉ፣
የእንቅስቃሴአችንን ዱካ ግን ሊያውቁ አይችሉም። እንቅስቃሴአችን በጣም ዝቅተኛ
ከሆነው የሰው ልጆች መርህ ወጥቶ በመንግስቱ መንኮራኩር ውስጥ ተሰውሮአልና።
የእንቅስቃሴአችን እዝ ማእከል እግዚአብሔር እንጂ ስጋና ደም፣ የምድር ሥርዓት፣
ፖለቲካ፣ ምድራዊ ጥበብ በጭራሽ አይደለም። ወደ መንግስቱ ስንመጣ የመንግስቱ
ጉልበት ዑደት (አዙሪት) ወደርሱ ጎትቶ ካላስገባንና ለዚህ ሰማያዊ ጉልበት ወዲያው
ተሸንፈን ኢየሱስን ካልተከተልን የመንግስተ ሰማይ ደቀመዝሙር አይደለንም።
ካሱ ቦስተን
፩
እግዚአብሔርን ማወቅ የነገር ሁሉ ግብ ነው
(The audio version is here)
በዚህ በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ “ሰዓት” የሚለው ቃል ከሌሎቹ ወንጌላውያን ለየት ያለ ትኩረትና በዮሐንስ-ነገረ
መለኮታዊ ትረካ ውስጥ እያደገ የመጣ ሐሳብ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ሰዓት ከወልድ ተልዕኮ ጋር የተያያዘ
ጥልቅ መለኮታዊ እውነትን የሚያንጸባርቅ ቃል ነው። ለምሳሌ ያህል፤ ለማርቆስ የሰዓቱ መድረስ (ማር 1:15)
ከነብያት ድምጽ ጋር በማገናኘት (ማር 1፡2-3)፤ በኢየሱስ ማንነትና አገልግሎት (አገልግሎት የሚለውን ቃል
ለክርስቶስ ስጠቀም በቃልና በሥራ የተሰጠውን የክርስቶስን መለኮታዊ አስተርዕዮ ማመልከቴ ነው – what
some call the ‘Christ-event’) የእሥራኤልን ተሥፋ በሰውነቱ ለብሶ መገለጡን ይገልጻል። ስለዚህ በማርቆስ
ወንጌል ሰዓት በክርስቶስ (የዳዊት ልጅ -መዝ 2፡7/ 2 ሳሙ 7:14) አገልግሎት (በማንነቱ፤ በቃሉናና በሥራው)
አማካይነት የእግዚአብሔር መንግሥት መጥባቱን ያውጃል። እግዚአብሔር የሰጣቸው የማዳን ተስፋዎች ሁሉ
አሁን በገሊላ አውራጃ እየተፈጸሙ መሆናቸውን ያውጃል። ይህም የወንጌል መጀመሪያ ነው።
ወንጌላዊው ዮሐንስ ግን የክርስቶስን ማንነት ከድንግል ከመወለዱ (ወይም ከትሥጉት) አንድ እርምጃ ዕምር
ብሎ ከሥነ-ፍጥረት መጀመሪያ ይጀምራል። እንደዚሁም የክርስቶስን አገልግሎት ትረካ ከገሊላው አገልግሎት
ፈቀቅ አድርጎ ከአንድ የሰርግ በዓል ድግስ ይጀምራል። በዚህ መጽሐፍ ክብር፤ ምልክት፤ የአብ ፈቃድ መፈጸም፤
የወልድ ተልዕኮ፤ መውጣትና መውረድ፤ የመስቀሉ ውርደት፤ የዘላለም ሕይወት ከዚህ አንድ ቃል -ሰዓት- ጋር
የተያያዙ ናቸው። ሆኖም ግን ይህች ሰዓት በዮሐንስ የነገረ-መለኮት ትረካ ውስጥ ከሰው ልጅ አገልግሎት
መጀመሪያ ጋር ሳይሆን ከሰው ልጅ ታልፎ ከሚሰጥባት ለሊት ጋር የተያያዘች ነች። ለምሳሌ ያህል
የመጀመሪያውን ምልክት ሲያደርግና ደቀ መዛሙርቱ በእርሱ ሲያምኑበትና ክብሩን ሲያዩ ይህች ሰዓት ገና
አልደረሰችም፡
“የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፤ የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም አለችው። ኢየሱስም፤ አንቺ ሴት፥
ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት” ዮሐ 2:3-4
o (“οὔπω ἥκει ἡ ὥρα μου” የአዲሱ መደበኛ ትርጉም ‘ሰዓቴ’ ሆራ-ሙ’ ለሚለው የግሪኩ ቃል
ይበልጥ ይቀርባል)
ስለዚህ ሊይዙት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን ጊዜው ገና ስላልደረሰ ማንም እጁን አልጫነበትም። ከሕዝቡ ግን
ብዙዎች አመኑበትና። ክርስቶስ በመጣ ጊዜ ይህ ካደረጋቸው ምልክቶች ይልቅ ያደርጋልን? አሉ። (John 7:30–
31 )
ኢየሱስ በመቅደስ ሲያስተምር በግምጃ ቤት አጠገብ ይህን ነገር ተናገረ፤ ጊዜው ገና አልደረሰምና ማንም
አልያዘውም። ኢየሱስም ደግሞ። እኔ እሄዳለሁ ትፈልጉኛላችሁም በኃጢአታችሁም ትሞታላችሁ እኔ
ወደምሄድበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም አላቸው። (John 8:20–21 )
ሆኖም ግን ይህች ሰዓት መድረሷን አብ ለሚወደው ልጁ “ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን” ብለው በመጡት በግሪክ
ሰዎች አመለከተው። ይህም አሕዛብ ወደ ኪዳኑ በረከት መጠጋታቸው ለአብርሃም የተሰጠውን የተሥፋ ቃል
አሁን በወልድ የመስቀል ተልዕኮ የሚፈጽምበት ሰዓት መድረሱ ሲያመላክት
ኢየሱስም መለሰላቸው፥ እንዲህ ሲል። የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል። እውነት እውነት
እላችኋለሁ፥ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ
ታፈራለች።… አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ? ነገር ግን ስለዚህ
ወደዚህ ሰዓት መጣሁ። አባት ሆይ፥ ስምህን አክብረው። ስለዚህም። አከበርሁት ደግሞም አከብረዋለሁ የሚል
ድምፅ ከሰማይ መጣ…አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል፤ እኔም
ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደ ሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ። በምን ዓይነትም ሞት ይሞት ዘንድ እንዳለው
ሲያመለክታቸው ይህን ተናገረ። John 23:27–33
ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም
ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው። (John 13:1 )
ከዚህ ወደ ጥልቅ ጅረት ከሚወስደን ዋና እንውጣና ወደ ጀመርንበት እምር እንበል። ወልድ ወደ መስቀል
ከመውጣቱ በፊት ሲጸልይ (የታላቅ-ሊቀ-ካህናት ጸሎት) መጀመሪያ ከአፉ የወጣው ቃል “አባት ሆይ ሰዓቱ
ደርሶአል” ነበር። የዚህች ሰዓት ትልቅነት የተመሰረተው በዚህች ሰዓት ውስጥ የሚከናወነው ሥራ ነው።
መለኮታዊ ተልዕኮ ነው፡- ይህ ሥራ አለም ሳይፈጠር አብ ለወልድ የሰጠውና በአገልግሎቱ አብ ሲያሳየው (ዮሐ
5:19-39) ለነበረው ሥራ ጫፍ ነው። በዚህ ተልዕኮ አብ ይከብራል። ይህም የመስቀሉ ተልዕኮ ነው። “የሰው ልጅ
ከምድር ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ” የሚለው ሐረግ ዮሐንስ እንደዘወትሮው ድርብ ትእምርትን በመጠቀም የክርስቶስ
ውርደት የክብር ጎዳና እንደሆነ ያሳየናል። የሮማውያን ወታደሮች መስቀሉን በገመድ ወደ ላይ ከፍ እያደረጉ
ወልድን በአየር ላይ ሲያንጠለጥሉት፤ በዚህ አንድ የውርደት መስቀል ላይ ወልድ የአባቱን ሥራ በፈጸሙ
የሚከብርበትም መንገድ ነው። ሥለዚህ መስቀሉ የክብር ጎዳና ነው። በዚህ መንገድ ወልድ ይዋረዳል፤ አብ
ይከብራል፤ ወልድን አብ ዓለም ሳይፈጠር በነበረው ክብር መልሶ ያከብረዋል፤ በሰዎች ልጆች ሁሉ ላይ ሥልጣን
ይጎናጸፋል፤ የዚህ ዓለም ገዚ ወደ ውጪ ይጣላል!
መለኮታዊ አስተርዕዮ ነው፡- በዚህች ሰዓት በተገለጠው ሥራ ውስጥ እውነተኛው አምላክ አብና የተላከው ወልድ
ተገልጠዋል።
የዘላለም ሕይወት ነው፡’ ምልክቶቹ የተሰጡበት ዓላማ አንባቢው፡ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ
እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ ውጤቱም በስሙ የዘላለምሕይወት ይሆንልን ዘንድ ነው
o ዘላለማዊ ሕይወት ኢየሱስ ዳግም ሲገለጥ ዕውን የሚሆነው የመጪው ዘመን ሕይወት ማለት (The
Life of the age to come, “zoe-aionios”)
o ስለ እኔና ስለ ወንጌል ቤትን ወይም ወንድሞችን ወይም እኅቶችን ወይም አባትን ወይም እናትን
ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን ወይም እርሻን የተወ፥ 30 አሁን በዚህ ዘመን ከስደት ጋር ቤቶችን
ወንድሞችንና እኅቶችንም እናቶችንም ልጆችንም እርሻንም መቶ እጥፍ፥ በሚመጣውም
ዓለም/ዘመን የዘላለም ሕይወት የማይቀበል ማንም የለም። “31 ግን ብዙ ፊተኞች ኋለኞች ኋለኞችም
ፊተኞች ይሆናሉ።” ማር 10፡ 30-31
o እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም
ሕይወት ናት። “እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርሁህ”
ከዚህ የተነሳ የዘላለም ሕይወት ከላኪው አብና ከተላኪው ወልድ ጋር የተቆራኘ ነው። ያለ ወልድ ሕይወት
የለም። ሆኖም ግን ልንገነዘበው የሚገባው ነገር፤ አብንና ወልድን ማወቅ ያለው ወልድ በሰጠን ቃሎቹና
በፈጸማቸው ሥራዎች ውስጥ መሆኑን ነው። ዮሐንስ የአንድያ ልጁ የሆነውን ክብሩን ያየነው በምልክቶቹ
(በሥራዎቹ) ውስጥ እንደሆን ያሳየናል። ሰዎች ክብሩን እንዴት አዩ? ወልድ ከባህር አጠገብ በጀልባ ቁጭ ብሎ፤
ታዳሚው አንድ በአንድ በአጠገቡ እያለፉና አፋቸውን በእጃቸው እየጫኑ፤ “አቤት የእግዚአብሔር ልጅ?” እያሉ
ነበር? ታስታውሱ እንደሆን ብዙ ሰዎች ወደ እርሱ ሲሰብሰቡ ማቴዎስ ሲነግረን “አፉንም ከፍቶ
አስተማራቸው እንዲህም አለ…” ትምሕርቱንም ሲጨርስ ሰዎች “ኢየሱስም ይህን ነገር በጨረሰ ጊዜ ሕዝቡ
በትምህርቱ ተገረሙ፤ እንደ ጻፎቻቸው ሳይሆን እንደ ባለ ሥልጣን ያስተምራቸው ነበርና” ይላል። ስለዚህ
ሕይወት ያለው ወልድን በማወቅ ውስጥ ነው። ወልድንም ማወቅ በቃሉና በሥራው ላይ ያነጣጠረ ነው።
የእግዚአብሔር ሕዝብ አብ የሚወደውንና ወደ ዓለም የላከውን አንድያ ልጁን እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ
አማካይነት የፈጸመውን ተልዕኮ ማወቅ እንዲሁ ግርድፍ ያለ እውቀትና ቃል ብቻ ሳይሆን ሕይወትን የሚሰጥና
ለማዳን የሚችል መለኮታዊ ሐይል ነው።
በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፥ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ
ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ
ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።
(1 John 4:7–10 )
ይህ የቤተ-ክርስቲያን አባት አስምሮ የተናገርው ነገር ምንድር ነው፤ የሰው ልጆች ሐጥያት እምብርት አመጽ
ስለሆነ፤ ይህም ለእግዚአብሔር አለመገዛት፤ ከእግዚአብሔር ሥልጣንና አገዛዝ ማፈንገጥ፤ የእግዚአብሔርን
ክብር በሌላ በተፈጠሩ ነገሮች እንደዚሁም የእግዚአብሔርን መለኮታዊ እውነት በሐሰት መለወጥ እስከሆነ
ድረስ፤ እውነተኛ መዋጀት እነዚህ ነገሮች ያስተካከለ እንደሆን ብቻ ነው። ሰው ወደ እግዚአብሔር ሥልጣን
ሲመለስ፤ ተንበርክኮ ይህንን አምላክ አዳኜ ያለ እንደሆን ብቻ ነው። አንሰልም ጥሩ አይቷል። በነብዩ ኢሳያስም
ያህዌህ እንዲህ ይላል
ስለዚህ እውነተኛ መዳን ሁለት ነገሮችን ያቅፋል። እነዚህ ሁለት እውነታዎችን በብዙ መንገድ አዲስ ኪዳን
ያሰቀምጣቸዋል። ለግልጽነት እንዲመች ግን ሁለት መደቦችን ልጠቀም። በአንድ እጅ እነዚህን ቃሎች እንያዝ፦
መጽደቅ፤ መዋጀት፤ እርቅ፤ ሰላም፤ መግባት፤ ሥርየት። በሌላ እጅ ደግሞ መክበር፤ ልጅነት፤ ተስፋ፤ ርስት።
እነዚህ ሁለት እውነታዎች የሚያንጸባርቁት በአንድ ወገን ከየት እንደመጣን ሲሆን በሌላ እጅ ደግሞ ወዴት
እንደምንሔድ ነው። በአንድ ወገን ድነናል በሌላ ወገን ደግሞ ገና በሙላት እንድናለን። መጽሀፍ ቅዱሳዊ
ደህንነት ‘ከ’ እና ‘ወደ’ የሚሉትን መስተዋድዶች ገንዘቡ ማድረግ አለበት።
እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና፥ በቅርብም ያለውን ብቻ ያያል፥ የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት
ረስቶአል። ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን
ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉምና። እንዲሁ ወደ ዘላለሙ ወደ ጌታችንና መድኃኒታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ
መንግሥት መግባት በሙላት ይሰጣችኋልና (2 Peter 1:9–11 )
ክርስቶስ ራሱን መስዋዕት አድርጎ በማቅረብ ለሐጥያታችን ሥርየት ሲል “ሐጥያታችንን በእንጨት በሰውነቱ
ተሸክሞ ከእግዚአብሔር አብ ቁጣ፤ ከሞትና ከሐጥያት አድኖኗል። እዚህ ጋር ግን አያበቃም። ይህ ግማሽ
እውነት ነውና። ስለዚህ እውነተኛ ደህንነት ግን “የልጁን መልክ” በመምሰል መክበርን ገንዘቡ ማድረግ አለበት።
የመጨረሻ ግባችን ልጆች መሆን ነው (1 ዮሐ 3:1-5) መዳናችንን ከሌሎች ፍጥረታት መዋጀት የሚለየው
መዳናችን የእግዚአብሔርን ልጅ ኢየሱስን መምሰላችን ነው። የእግዚአብሔር ቤተሰቦች በመሆን ከመለኮት
ባሕርይው እንድንካፈል ተዋጅተናል (2 Pet 1:2 ; John 1:2-3 )። ይህ ከፍ ብዬ ወደ ጀመርኩት ነጥብ
ያመራኛል። ይህም የመንፈስ ቅዱስ በበዓለ ሃምሳ ተልኮ መምጣቱና በልባችን ማደሪያ መሥራቱ አላማው
በግል የልጁን መልክ እንድንመስል እንዲሁም እንደ አካል ደግሞ እግዚአብሔር የሚኖርበት ሕያው ቤተ-መቅደስ
ሆነን እንድንሰራ ነው (there is an eschatological progression of sonship as well as temple imagery)
መንፈሱንም ‘የክርስቶስ መንፈስ’ በማለት የመንፈስ ቅዱስን ተልዕኮና ሥራ ይገልጽልናል። ይህ መንፈስ
በስሉሱ አምላክ የውስጥ ሕይወት ውስጥ የሚሰርጽ እንደመሆኑ መጠን ለአካሉ የሚመጥነውን ሥራ ደግሞ
በእኛም ሕይወት ይሰራል። ከዚህ የተነሳ መዳናችንን ስሉስ በሆነ መልክ በኤፌሶን ተገልጧል። ይህም
የምንቀርብበት መንገዱም ሆነ ፍጻሜያችን በስሉሱ አምላክ የተቀመረ ነው። ስለ አቀራረባችን ሲያሳየን
“በእርሱ [በክርስቶስ] ሥራ ሁላችን በአንድ መንፈስ ወደ አብ መግባት አለንና (Ephesians 2:18 )”
የምንቀርበው በአብ ፊት ሲሆን መንገዱ ደግሞ በወልድ ሥራ አማካይነት በአንዱ በመንፈስ ቅዱስ በኩል ነው
(depicted in highly in Trinitarian terms but reverse order. The father revealed himself to us,
through Christ, by the holy Spirit. We experience this revelation by the Spirit, through Christ.)
እኛም ሁላችን በመጋረጃ በማይከደን ፊት የጌታን ክብር እንደ መስተዋት እያብለጨለጭን መንፈስ ከሚሆን
ጌታ እንደሚደረግ ያን መልክ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንለወጣለን። (2 Corinthians 3:18 )
በውስጣችን ያለው የልጅነታችን መንፈስ ሊመጣ ላለው ርስት መያዣ መሆኑንም መጽሐፍ ቅዱስ ያሳየናል
(በዚህ ምክኒያት ሐዋርያው መንፈስ ቅዱስን የርስታችን መያዣ/አራቦን የሚል ሥያሜ ይሰጠዋል ‘ἀρραβὼν
ኤፌ. 1:14’)
ስለዚህ መጽሀፍ ቅዱስ በልጁ በኩል የተገለጠውን ደህንነት ‘የማስመለጥ’ ተልዕኮ ብቻ ሳይሆን (ምንም እንኳ
ይህ ትልቁን ሥፍራ የሚይዝ እውነት ቢሆንም) ‘የመለወጥ’ ተልዕኮን ይጨምራል። ይህንን ተልዕኮ ወልድ ይዞ
ተገልጧል። ለማጠቃለል በዮሐንስ 17 ላይ የወልድ ተልዕኮ፦
a. ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ፥ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ
አልለምንም፤ አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ፥ አንተ፥ አባት ሆይ፥ በእኔ እንዳለህ እኔም
በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ። እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ
ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ
ሰጥቻቸዋለሁ፤ እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ
ወደድሃቸው ያውቃል። John 17:20–23 (AMHB)
ስለዚህ መዳን እግዚአብሔርን ማወቅ ነው። እግዚአብሔር ሲያድነን ከጠላትነትና ከሃጥያተኛነት ወደ ክብርና
ወደ ልጅነት አምጥቶናል። ከአባቱ ጋር የመለኮት ክብር ገንዘቡ ሆኖ ሲኖር ከነበረበት ልዕልና ክብሩን ወደ
ማታውቅ ወደዚህች ዓለም በመምጣት ራሱን አዋረደ (John 17:19 , Phil 2:9-11 ) ። የመጣው የአባቱን
ፈቃድ ለመፈጸም ነበር። ሆኖም ግን በዚህ በተዋረደ የመስቀል ሞት በኩል የአባቱን ፈቃድ በመፈጸሙ አብን
አከበረ። አብ ደግሞ ወልድን ያለልክ አከበረው፤ በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ሥልጣንን ሰጠው፤ ከብሮ እኛንም
አከበረን። በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ ደግሞ ክብር ገንዘባቸው ሆነ!
እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርሁህ፤ አሁንም፥ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ
ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ።
ስለዚህ እኛም በባህሪያችን ሞት የተገባን፤ በሐጥያት የተለወስን ጸያፍ ሰዎች፤ ከልጁ ሕይወት/ደም ክቡርነት
የተነሳ ከዚህ ስሉስ ሕይወት እንድንካፈል (በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ)
በር ተከፈተልን። መዳን ሕይወት ነው። ሕይወትንም ማግኘት መዳን ነው። መዳን እግዚአብሔርን ማወቅ
ነው፡፡ ይህም የዘላለም ሕይወት ነው። ለምን ይሆን ወደ መንግሥቱ ገብተን፤ ከእልፍኙ ውስጥ አብረን ታድመን
ከስሉሱ ንጉስ ገበታ የምንጋራው? የማይጠገበውን የልጁን ክብር እናይ ዘንድ ነው። ይህም ክብር ወልድ በአብ
መወደዱ ነው። ይህ መወደድ ለወልድ ክብሩ ነው (አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ)። ከዚህ ገበታ
የሚፈረፈርውን የፍቅር ፍርፋሪ ብንለቅም አቤት እንዴት ታላቅ ክብር ይሆን!? ነገር ግን አብ ያፈሰሰልንን
ፍቅር ተመልከቱ (1 ዮሐ 3:1-5)! ልጆች አደረገን። ይህም ልጁ በሚወደድበት ፍቅር ተወደድን! ይህንን ፍቅር
ተመልካቾች ብቻ ሳንሆን ነገር ግን ከዚህም ፍቅር ተካፋዮች እንድንሆን አበቃን! (እኔንም የወደድህባት ፍቅር
በእነርሱ እንድትሆን እኔም በእነርሱ፥ ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ) ፍቅር እንደዚህ ነው!
እኛ እንደወደድ ሳይሆን አብ እንደወደደንና ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከልን
ነው። ለምን ወደ መንግሥተ ሰማይ መግባት ይናፍቀናል? አንዳንዶች እንደሚሉት ወርቅ ስላለ ነው? እረፍት
ስላለ ነው? ወይስ ለመዘመር ነው? የመጠቀ ዕይታ አለን፤ የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ብሎናል፡-
የሰጠኸኝ ክብሬን እንዲያዩ እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ።
ማራናታ እንበል! ወደ መዳናችን ለመግባት እንዘጋጅ። ስንሔድ የልጁን ክብር እናያለንና! መዳን ማለት ስሉሱን
አምላክ በማወቅ ወደ ሚገኝ ፍጹም አንድነት መድረስ ነው። ይህንን ዳርቻ በልጅነት ይገልጸዋል። ልጆች ሆነን
እንከብራለን። ሆኖም ግን ያ ክብር አሁን በውስጣችን እንዲኖር ከሰጠን በመንፈሱና በሐዋርያቱ አማካይነት
ትቶልን በሔደው ቃሎቹ መቅመስ ጀምረናል።
፪
ሦስት ገጽታ ያለው መዳናችን
ከላይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ድነት ሁለት እይታዎችን ገንዘቡ እንዳደረገ በፈረስ ግልቢያ ይመስል ፈጠን ፈጠን ብለን
አይተናል። እነዚህም፤ ከእኛ ዕይታ አንጻር፤ መዳን እንደ ሁለት ጫፎች መስለነው ‘ከየትና ወዴት’ ብለናቸዋል። በጉዞ ላይ
እንዳለ የእሥራኤል ሕዝብ፤ ለቀውት የመጡት ግብጽ ከኋላቸው፤ ከፊታቸው ደግሞ ሊገቡባት ያለችው ማርና ወተት
የምታፈሰው የተስፋይቱ ምድር እንደነበረች፤ እኛም መዳናችን ከኋላ የተረፍንበት፤ ደግሞም ከፊት የምንወርሰው
ሐብታችን ነው። ይህም መዳናችን አሉታዊና አዎንታዊ ገጽታ አለው ማለት ነው። አሉታዊ ያልነው መዳን መትረፍን
ያመለክታልና ነው፤ ለሐጥያታችን ቅን ፍርድ ከሆነው ከእግዚአብሔር ቁጣ የተረፍን ሕዝቦች ነንና (ትሩፋን)።
እግዚአብሔር አምላካችን እዚህ ጋር ቢተወን ኖሮ ጻድቅ፤ መልካምነቱም ወደር የለሽ በሆን ነበር። ምክኒያቱም ዝም
ቢለን ኖሮ እንደ ሶዶምና እንደ ጎሞራ የምንሆነውን እኛን በጸጋው አንድያ ልጁን በመላክ አተረፈን። ግን የአምላካችንና
የአዳኛችን ታላቅ ምህረት ሲገለጥ አትርፎ ቢተወን ኖሮ የሚበቃንን እኛን ‘ልጆቹ እንሆን ዘንድ አስቦ ወለደን። ይህንን
ነው ‘ወዴት በሚለው ያካተትነው። ይህንን ታላቅ እውነት ቀለል አድርጎ ለማስተዋወቅ ያህል ብቻ እንጂ መዳን ሌላ
ሦስተኛ ገጽታም አለው።
መጽሀፍ ቅዱስ ስለመዳናችን ሲናገር አንድቀን በሕይወታችን የተጠናቀቀ ፕሮጀክት እንደሆን አያቀርበውም።
ለምሳሌ ያህል አማኞች ብዙውን ጊዜ እንዲህ ሲሉ ይደመጣሉ። በተለይ ደግሞ ይህንን ስህተት መስራት
የማይገባን አገልጋዮችን ጨምሮ “አሁን ስለሚያደርግልኝ ከማመሰገነው ይልቅ፤ ከሁሉ በላይ ስለመዳኔ
አመሰግነዋለሁ” ስንል እንደመጣለን! በግርድፉ ስታዩት እውነት ይመስላል “የቀን ውሎ ሥራ…የደሞዝ
ጭማሬ…ልጆች…ትዳር…ሐዘኔ..ደስታዬ…መከራዬ..ስኬቴ.. ከመዳኔ ጋር ምን አገኛነው?” ስለዚህ ይህ
አባብል “ከዚህ ሁሉ በላይ ግን ስለመዳኔ ተመስገን” ባይ ይመስላል። በርግጥ ይህ አባባል ሊበረታታ የሚገባና
እውነት ነው። እውነትነቱ ግን በከፊል ብቻ ነው። በተጨማሪ ግን እንደምታው ያልታሰበ ጎጂ ኢ-መጽሐፍ
ቅዱሳዊ መዘዝ አለው። ይህ አነጋገር በመጀመሪያ መዳን ያኔ ያመንን ቀን ብቻ የሆነ ክዋኔ እደሆን የአማኙን
መረዳት ያሳያል። ሁለተኛ አሁን በአማኙ የሚሆነው ከፍታና ዝቅታ ከመዳኑ ጋር እንብዛ ግኙነት እንዳለውም
አያሳይም። አማኙ ከእግዚአብሔር የሚቀበለው ደስታ ይሁን መከራ ከመዳኑ ጋር ምንም ግንኙነት አለው?
የአሁኑ ገጠመኝ፤ የሥራ በር መከፈት…ወዘተ…ከመዳናችን ጋር ግንኙነት የለውም? ስለዚህ ይህ አነጋገር
ጠለቅ ብለን ስናየው የቅርቡን ብቻ የሚያይ ይመስላል። ሦስተኛ፤ በአንድ ቀን መዳናችንና በአሁን የለውጥ
ሒደታችን መካከል ረጅም ገደል በአማኙ ሐሳብ ውስጥ እንዳለም ይጦቁማል። ከዚህ ቀጥሎ
እንደምንመለከተው ይህ አነጋገር መዳናችን በጣም ተራ በሚመስሉ ነገሮች ውስጥ ዕለት ዕለት እየሰራ መሆኑን
አያስተውልም። እዚህ ጋር ይህችን ነገር-ቀመስ አነጋገሬን ልተውና ሁልጊዜም እንደማደርገው ወደ ቅዱስ ቃል
ትንታኔ ውስጥ እንግባ። ከዚያ ወደዚህ ወደ ጀመርነው ሐሳብ እነመለስና እንዳኛለን።
ድነናል (ኤፌ 2፡ 8-10)፦ “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ
አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም። እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር
አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን።”
ይህ ክፍል የሚያስገነዝበን መዳናችን አንድቀን የተከናወነ ነው። ሃላፊ ግስ ነው። ያድናችኋል ወይም እያዳናችሁ
አይልም ሆኖም ግን አድኗችኋል። (ነገር ግን አንባቢው ቀጥሎ ያለውን ያንብብ። ይህ አንድ ቀን የተከናወነው
መዳን በአዲስ ፍጥረት በመምሰል- መመላለስ በሚለው ቃል ሒደታዊ እንደሆነም ይጦቁመናል)
እንድናለን (ሮሜ 5:8–10.)፦ ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ
ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን።
ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን፤
የሚገርመው እዚህ ጋር ሐዋርያው ስለ መታረቃችን ሲጽፍ እንታረቃለን አይልም። ክርስቶስ የተሰቀለ ዕለት
በጥቅልና ያመንን ዕለት በግል ታርቀናል። ሰላምን ተቀብለናል። ወደ ቆምንበት ጸጋ መቅረብ ችለናል። ሆኖም
ግን ሐዋርያው መዳናችን ገና ያልተጠናቀቀ ፕሮጄክት እንደሆን ሲጦቁመን ሁለት ጊዜ ደጋግሞ “ከቁጣው
እንድናለን…በሕይወቱ እንድናለን” ይለናል። ። ስለዚህ አሁን ብንታረቅም፤ አሁን ብንድንም ነገርን ገና
በሙላት እንድናለን። (ተጨማሪ፡ 1 ተሰ 5:6-8፤ 1 ጴጥ 1:3-5) በተለይ ጴጥሮስ መዳናችንን “በመጨረሻው
ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ” በማለት መዳናችን ወደ
ፊት የሚከናወን ጭምር እንደሆን ያስረዳናል።
“እንግዲህ እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ፥ ክርስቶስም ደግሞ እንደ ወደዳችሁ
ለእግዚአብሔርም የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደ ሰጠ
በፍቅር ተመላለሱ” (ኤፌ. 5:1–2) ይህ ማለት በወንጌል የተገለጠው የክርስቶስ ተልዕኮ ለመዳናችንም ደግሞም
በመዳናችን ከሕይወቱ ተካፋዮች እንድንሆን ምሳሌንም ሊተውልን ጭምር ነው። ይህንን ምሳሌ መከተል ልክ
ልጅ አባቱን እንደሚመስል መለወጥ ነው። ስለዚህ በዚህ ምዕራፍ ክርስቶስን መምሰል ውጤቱ ምን ይመስላል?
o ለቅዱሳን እንደሚገባ ግን ዝሙትና ርኵሰት ሁሉ ወይም መመኘት በእናንተ ዘንድ ከቶ አይሰማ (ቁ.3)
o የሚያሳፍር ነገርም የስንፍና ንግግርም ወይም ዋዛ የማይገቡ ናቸውና አይሁኑ፥ (4)
o የብርሃኑ ፍሬ በበጎነትና በጽድቅ በእውነትም ሁሉ ነውና ለጌታ ደስ የሚያሰኘውን እየመረመራችሁ፥
እንደ ብርሃን ልጆች ተመላለሱ፤ፍሬም ከሌለው ከጨለማ ሥራ ጋር አትተባበሩ፥ ይልቁን ግለጡት
እንጂ፥9-11
o እንግዲህ እንደ ጥበበኞች እንጂ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንዴት እንድትመላለሱ በጥንቃቄ
ተጠበቁ
o በመዝሙርና በዝማሬ በመንፈሳዊም ቅኔ እርስ በርሳችሁ ተነጋገሩ፤ ለጌታ በልባችሁ ተቀኙና ዘምሩ፤
ሁልጊዜ ስለ ሁሉ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምላካችንንና አባታችንን ስለ ሁሉ አመስግኑ።
o ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤
o ባሎች ሆይ፥ ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ፤ በውኃ
መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለ እርስዋ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤ስለዚህ ሰው አባቱንና
እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ። ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው፥
እኔ ግን ይህን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን እላለሁ። ሆኖም ከእናንተ ደግሞ እያንዳንዱ የገዛ
ሚስቱን እንዲህ እንደ ራሱ አድርጎ ይውደዳት፥ ሚስቱም ባልዋን ትፍራ።
o ልጆች ሆይ፥ ለወላጆቻችሁ በጌታ ታዘዙ፥ ይህ የሚገባ ነውና።
o ባሪያዎች ሆይ፥ ለክርስቶስ እንደምትታዘዙ በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ በልባችሁ ቅንነት በሥጋ
ጌቶቻችሁ ለሆኑ ታዘዙ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደሚያደርጉ እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች እንጂ
ለሰው ደስ እንደምታሰኙ ለታይታ የምትገዙ አትሁኑ።
o እናንተም ጌቶች ሆይ፥ ዛቻውን ትታችሁ እንዲሁ አድርጉላቸው፥ በእነርሱና በእናንተ ላይ የሚገዛው
ጌታ በሰማይ እንዳለ ለሰው ፊትም እንዳያደላ ታውቃላችሁና።
o በቀረውስ በጌታና በኃይሉ ችሎት የበረታችሁ ሁኑ። የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ
እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ።
ወንጌል በአማኙ ሕይወት ሥር ሲሰድ ከላይ እንደተመከትነው የሚዳሥሠው የሰውን ሁለንተና ነው። ከነዚህ
መካከል (ከኤፌ 5:1-6፡12) ሥነ-ምግባራዊ ለውጥን ገንዘቡ ያደረገ ነው፤ በጥበብ መመላለስን፤ በመዝሙርና
በቅኔ ማወደስን ገንዘቡ ያደረገ ነው፤ የባልና የሚስት፤ የ ወላጆችና የልጆችን፤ የአሠሪና የሰራተኞችን ግንኙነት
ይዳስሳል። የምለው ይህንን ነው፤ እነዚህ ለውጦች ግን “ክርስቶስም ደግሞ እንደ ወደዳችሁ ለእግዚአብሔርም
የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደ ሰጠ” የሚለው የወንጌል
እውነት ይከተላሉ እንጂ አይቀድሙም። አማኙ የመረዳት ብልጽግና በመንፈስ ቅዱስ ሲያገኝ የሚሆኑ ነገሮች
ናቸው። (በተጨማሪ እነዚህን ለናሙና ያንብቡ ፊል 2፡ 2-8፤ ሮሜ 15፡ 2-7) ስለዚህ የምንም ለውጥ ሒደት
ብንናገር በመጀመሪያ የወንጌል እውነት ሥር ከተመሰረተ በኋላ መሆን አለበት። በርግጥ ለውጥ ማለት ክርስቶስ
ስለ እኛ የሆነውን መምሰል ነው (there is a mirroring of relationship) ካልሆነ አትንካ አትቅመስ የሚል
ከንቱ የሰው ሥርዓቶች ብቻ ናቸው፡፤ እነዚህም በተግባር ሲደረጉ የሚጠፉና ለሥጋ ልቅነት አንዳች ፋይዳ
የሌላቸው መርሆች ናቸው። ይህ በተለይ ለእኛ ለሰባኪዎች ትልቅ ማስጠንቀቂያ ነው። የለውጥ ስብከት በፊት
መቅደም ያለበት የወንጌል እውነት ነው። ኢየሱስ ማነው? ተልዕኮውስ ማንድር ነው? የስውን ልጅ ማን
ይሊታል? ከዚህ አንጻር ስንመለከት የለውጥ ሕይወት የወንጌል እንደምታ ነው። ወንጌል የሐይል ቃል እንጂ ባድ
ንግግር አይደለም፡፤ ሐይል ከሆነ ዘንዳ በአማኙ ውስጥ ሰርጾ መስራት የሚችል ጉልበት ነው።
ቆላስይስ ምዕራፍ 1 እስከ 2 እርሱ የማይታየው ቆላስይስ ምዕራፍ 3 እስከ 4 እንግዲህ ከክርስቶስ
አምላክ አምሳል ነው፤ ከፍጥረት ሁሉ በፊት ጋር ከተነሳችሁ ፣ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ
በኩር ነው፤ እኛም እያንዳንዱን ሰው በክርስቶስ በተቀመጠበት በላይ ያሉ ነገሮችን እሹ፣
ፍጹም አድርገን ማቅረብ እንችል ዘንድ፣ ሰውን
ሁሉ በጥበብ ሁሉ እየመከርንና እያስተማርን
እርሱን እንሰብካለን ፤ እኔም በብርታት በውስጤ
በሚሰራው በእርሱ ኃይል ሁሉ እታገላለሁ፤
ለዚህ ዐላማ እጥራለሁ።
1 ቆሮንቶስ ምዕራፍ 1 እስከ 2 የመስቀሉ ኃይል 1 ቆሮንቶስ ምዕራፍ 3 እና ከዚአ በህዋላ ያሉት
ለሚጠፉ ሞኝነት ነው፤ ለእኛ ለምንድነው ግን ፣ጳውሎስ የቆሮንጦስ ሰዎች የጻፉለትን
የእግዚአብሔር ኃይል ነው ፤ ጥያቄዎችና ጉዳዮች ሁሉ በመጀመሪያዎቹ
ሁለት ምዕራፎች በአቀረበው ወንጌል መሠረት
መመለስና መፍታት ይጀምራል
በልማድ መዳን የሚለውን ቃል ስንጠቀም በጠባቡና በመጀመሪያው ገጽታ ነው። ይህም ባመንን ዕለት አንድ
ቀን የተከናወነ ነው። ሆኖም ግን ሊሰመርበት የሚገባው ይህ ባመንን እለት የሆነው የመዳን ሙሉ ገጽታ
አይደለም። እውነት ነው፤ የማይደገሙ አንድ ጊዜ የሆነ በመዳን ሥር የሚካተቱ ክንዋኔዎች ተፈጽመዋል።
ሆኖም ግን እነዚህ መዳን የሚለውን እውነታ ሙሉ በሙሉ መግለጫዎች አይደሉም። ባመንን እለት ምን ሆነ?
እግዚአብሔር ይመስገን አዳነን! መዳናችን ግን በዙ ገጽታ ባላቸውና ብዙ እውነታዎችን በሚያንጸባርቁ
ዘይቤያዊ አነጋገሮች ተገልጦአል። ከእነዚህ መካከል ጥቂቶቹ ይህንን ይመስላሉ፦ መጽደቅ፤ ጥሪ፤ ቅድስና፤
ዳግም ልደት፤ ልጅነት፤ ዕርቅ፤ ትድግና፤ መዋጀት፤ ቤዛነት፤ ሥርየት፤ ሰላም፤ መግባት፤ መክበር ወዘተ… እነዚህ
ሁሉና እነዚህን የመሳሰሉ የአንዱ መዳን ለሚለው እውነታ ገጽታዎች እንጂ ምትኮች አይደሉም። ሐዋርያው
ጳውሎስ ለምሳሌ እነዚህ የአንዱ መዳን ገጽታዎች እንደሆኑ ሲያሳየን “ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኵር
ይሆን ዘንድ፥ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና፤ አስቀድሞም
የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም
እነዚህን ደግሞ አከበራቸው።” በተጨማሪ ያህል ከእነዚህ የአንዱ መዳን ገጽታዎች ከሆኑት ብዙ ዘይቤያዊ
አነጋገሮች መካከል እንደ ናሙና አድርጌ “የጽድቅን ብያኔ ስለመቀበል” (justification) እንመልከት፡-
የጽድቅን ብያኔ ተቀበልን (Justification)፡- በእኛ ላይ የነበረው ክስ፤ ኩነኔና ፍርድ ተሠረዘ ማለታችን ነው።
በሕያው እግዚአብሔር ፊት ወንጀለኛ የሚል ሥያሜ ተነሳልን። የሰውን ፊት አይቶ በማያዳላው፤ በጻድቅ
ፈራጅ፤ በዓለሙ ሁሉ አምላክና ዳኛ ፍርድ ቤት ውስጥ ጉዳያችን በንጉስ ማህተብ ተዘጋ። ከእንግዲህ ወዲህ ይህ
የንጉሰ ነገስት ፍርድ ቤት በልጁ ደም ስርየት ምክኒያት ወንጀልህ እንዳልነበረ ተሰርዟል። በአንተ(ቺ)(እርሶ) ላይ
ያለው ሰነድ ስለ በደል የሚናገረው ጉዳይ የለም። (criminal record in this country can be cleared if
proven innocence of the crime)። ይህ ባመንን እለት እግዚብሔር አብ በእኛ ፈንታ ከፈሰሰው ከክርስቶስ
ደም የተነሳ የተቀበልነው ብያኔ ነው። (ከሐጥያታችን የተነሳ በቁጣው ፍርድ ምክኒያት የእኛ ደም መፍሰስ ቅን
ፍርድ ሆኖ ሳለ ከታላቅ ምሕረቱ የተነሳ የእርሱ ንጹህ ደም ፈስሶ እኛ በነጻ ተለቀቅን) ይህ የመዳናችን አንድ
ገጽታ ነው። ለምሳሌ
o እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፤ 2
በእርሱም ደግሞ ወደ ቆምንበት ወደዚህ ጸጋ በእምነት መግባትን አግኝተናል፤ በእግዚአብሔር ክብርም
ተስፋ እንመካለን።
o እርሱም፥ ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው
(የጽድቅ ብያኔ ነው)፤ ልዩነት የለምና፤ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር
ጎድሎአቸዋል፤ በኢየሱስ ክርስቶስም በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ(የጽድቅ
ብያኔ ይቀበላሉ)። እርሱንም እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ
አቆመው፤ Ro 3:22–25 .
o ተጨማሪ፦ Rom. 5:17 ; Rom 3:21 ; 9:30 ; 10:3–10 ; 2 Cor. 5:21 ; Phil. 3:9
ስለዚህ መዳን ማለት ሁሉን የሚጠቀልል፤ እግዚአብሔር በልጁ አምሳል ዳግም ለፈጠራቸውና ለጥቅል ፍጥረቱ
የተዘጋጀው ታላቅ ፕሮጀችት ነው ማለት ነው። ሆኖም ግን ምንም እንኳ መዳናችን አሁን እየሰራና ወደ ፊት
የሚገልጥ ቢሆንም አንዳንድ የመዳን በረከቶች ግን ዳግም ላይደገሙ የተከናወኑ ናቸው። ለምሳሌ ያህል
ሲያድነን ከጨለማ ወደ ብርሃን፤ ከሞት ወደ ሕይወት ተሸጋግረናል። በዚህ ገጽታው ከሆነ መዳናችን እለት
እለት እየሆነ አይደለም። ጌታን በየሳምንቱ አንቀበልም። አንድ ቀን አምነን የጌታ ሆነናል። ይህንን ነው
በመግቢያዬ ላይ የገለጥኩት። ብዙ ጊዜ አማኞች መዳን የሚለውን በዚህ ብቻ ወስነው በጠባቡ ይመለከቱታል።
ሆኖም ግን መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን በሥራ ላይ ነው። ሁሉ ነገር ተያይዞ (ሁሉ ነገር!) የሚሰራው ለአንድ
ግብ ነው። የልጁን መልክ እንድንመስል እየተሰራን ነው። ይህም ሒደት መጽሀፍ ቅዱሳችን መዳን በሚለው
ሰፊ ፕሮጀክት ላይ ያጠቃልለዋል እንጂ ሌላ ተጨማሪ ተልዕኮ አይደለም። ይህ ሒደት (process of
sanctification) ከመጽደቃችንና ከመታረቃችን የቀጠለ እንጂ ሌላ አዲስ ሥራ አይደለም። ግባችንም በሙላት
ልጆች መሆን ነው፤ ይህንን ዓላማ ክብር ይለዋል። ወደ ክብሩ ተጠርተናል፡ ልክ ለወልድ በአባቱ መወደዱ ክብሩ
እንደሆን ክብራችንም ልጆች መሆን ነው።
ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ…
“በክርስቶስ በሰማያዊ ስፍራ በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ የባረከን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት
ይባረክ። ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን። በበጎ
ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። በውድ ልጁም
እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ። በውድ ልጁም፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት
መጠን፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት። ጸጋውንም በጥበብና በአእምሮ ሁሉ
አበዛልን። በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤ በዘመን ፍጻሜ
ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው። እንደ ፈቃዱ
ምክር ሁሉን የሚሠራ እንደ እርሱ አሳብ፥ አስቀድመን የተወሰንን በክርስቶስ ደግሞ ርስትን ተቀበልን።
ይኸውም፥ በክርስቶስ አስቀድመን ተስፋ ያደረግን እኛ ለክብሩ ምስጋና እንሆን ዘንድ ነው። እናንተም ደግሞ
የእውነትን ቃል፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፥ በተስፋው
መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤ እርሱም የርስታችን መያዣ ነው፥ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ
እስኪዋጅ ድረስ፥ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል” (Ephesians 1:3–14 )
ሐዋርያው ይህንን ደብዳቤ ለመጻፍ የተጠቀመበትን ቋንቋ አንባቢ የሆናችሁ ይህንን ማስተዋል ትችላላችሁ።
በምዕራፍ አንድ ከቁጥር 3-14 ሲጽፍ ትንፋሽ አልወሰደም። በመሃከል ነጠላ ሰረዝ፤ ሁለት ነጥብ፤ አራት ነጥብ
አልተጠቀመም። ይህ ማለት ከቁጥር ሦስት ጀምሮ እስከ ቁጥር አሥራ አራት ድረስ አንድ ረጅም ዓረፍተ-ነገር
ነው። ሐዋርያው እግዚአብሔር በክርስቶስ በኩል የገለጠልንን መዳን ታላቅ መሆኑን በማስገንዘብ ልባዊ
ምሥጋናውን ሲገልጥ እረፍት ሊያደርግ አልወደደም።
የተባረክነው በሚወደው ልጁ በክርስቶስ ነው፦ በዚህች አጭር አረፍተ ነገር ውስጥ ከ 11 ጊዜ በላይ በመደጋገም
ሁሉን ነገር የተቀበልነው “በክርስቶስ/ በእርሱ/በሚወደው” መሆኑን ይነግረናል። ይህም መዳናችን ከክርስቶስ
ጋር አንድ መሆናችን ነው። እርሱ ሐጥያታችንን በመሸከም እኛን መሰለ፤ እኛ ደግሞ የሐጥያትን ሥርየት
ካስገኘልን በኋላ እርሱን እንመስል ዘንድ።
የባረከን የክርስቶስ አባት ነው፦ እዚህ ጋር አሁን አባት ብለን የምንጠራው አምላካችን በመጀመሪያ ደረጃ
የወልድ አባት መሆኑን ያሳየናል። ለዚህ ነው ስለ ክርስቶስ ሲናገር “በሚወደው ልጁ” ሲል ስለ እኛ ግን “ለእርሱ
ልጆች እንሆን ዘንድ አስቀድሞ ወሰነን” የሚለን። ክርስቶስ የዘላለም ልጅ ሲሆን እኛ ግን ልጆች እንሆን ዘንድ
የተቀበለን ልጆች ነን (adopted sons)። ይህ የሐዋርያው የባረከንን የሚባርክበት ታላቅ ምክኒያት ነው።
ከመዝሙረኛው ዳዊት አንሥቶ እስከ ክርስቶስ ዘመን የነበሩ አይሁዳውያን እንደጸሎት ቀመር አድርገው
የሚጠቀሙበት ሐረግ አለ። ለምሳሌ ዳዊት የባረከውን አምላክ እየባረከ ሲዘምር “የልመናዬን ቃል ሰምቶኛልና
እግዚአብሔር ይባረክ…ከዘላለም እስከ ዘላለም የእስራኤል አምላክ እግዚአሔር ይባረክ” መዝ. 28፡ 6 ፤ 31፡ 21፤
41፡13፤ 119፡12 በተጨማሪ “ዳዊትም በጉባኤው ሁሉ ፊት እግዚአብሔርን ባረከ፤ ዳዊትም አለ። አቤቱ፥
የአባታችን የእስራኤል አምላክ ሆይ፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ተባረክ” 1 ዜና 29:10። ክርስቶስ በተገለጠበትም
ዘመን አይሁድ፤ ከዚህ ተከትለው በዘወትር ጸሎታቸው መጀመሪያ “ባሩክ አታህ አዶናይ ኤሎሔኑ…ብሩክ ነህ
አንተ ጌታ አምላካችን….” በማለት ባርኮታቸውን መዘርዘር ይጀምራሉ። ጳውሎስም ክርስቶስን በደማስቆ
መንገድ ላይ ከመገናኘቱ በፊት ብዙ ጊዜ እንዲህ ብሎ ይጸልይ እንደነበር መገመት አዳጋች አይደለም። እዚህ ጋር
ግን ሐዋርያው ጳውሎስ በልማዱ ላይ ሠበር ቃል ይከታል። ይህም ያ የአባቱ የአብርሃም አምላክ አዳናይ-
ኤሎሔኑ (ጌታ-አምላክ) አሁን የሚታወቀውና በጸሎት የሚጠራው “አምላክ የጌታችን የክርስቶስ ኢየሱስ
አባት ተብሎ ነው!” እዚህ ጋር ብዙ መሠረታዊና ጥልቅ እውነታዎች ተንጸባርቀዋል። በመጀመሪያ ዳዊትና
አይሁድ ‘ጌታ’ ብለው ያህዌህን እንደጠሩት አሁን ይህንኑ ስም (ጌታ) ለኢየሱስ በማጎናጸፍ ክርስቶስ ከአባቱ ጋር
በማዕረግ አንድ መሆኑን ያሳየናል (ከዘዳ 6:4 ጋር ያጣቅሱ)። ሁለተኛ በክርስቶስና በአብ መካከል ያለውን
ግኑኝነት ያጎላል። ክርስቶስ የአብ ልጅ ነው። መዳን ማለት ደግሞ በሚወደው ልጅ አማካይነት ልጅ መሆን ነው።
የተባረክነው በመንፈሳዊ በረከቶች ነው፡- እዚህ ጋር ሐዋርያው መንፈሳዊ ሲል ከቁሳዊ ነገር ጋር እያቃረነ
እንዳለሆነ ሊሰመርበት ይገባል። ይህም የመዳን በረከት ቁሳዊ ሳይሆን መንፈሳዊ አድርጎ ማቅረብ ማለት ነው።
ሆኖም ግን ይህ አስተሳሰብ የግሪኮች መንትያ አስተሳሰብ (dualism) እንጂ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተሳሰብ
አይደለም። ሐዋርያው ግን መንፈሳዊ ሲል፤ የበረከታችንን ምንጭ ለማመልከት ነው። ይህም ያገኘናቸው
በረከቶች ከአሮጌው ሥርዓት የፈነጠቁ ሳይሆኑ ሁሉን ሊጠቀልል በወደደበት በልጁና የርስታችን መያዣ አድርጎ
በሰጠን በመንፈሱ የታቀፈ በረከት እንደሆን ለማመልከት ነው። (እዚህ ጋር ወደ ረቀቀ የቃል አጠቃቀም ትንታኔ
ውስጥ መግባት ለምትፈልጉ መንፈሳዊ ተብሎ የተተረጎመው ቃል ‘ፕኑሟቲካስ/πνευματικός’ ነው)
የተባረክነው በመንፈሳዊ ሥፍራ ነው፦ ሲል አሁንም እነዚህን በረከቶች የተቀበልንበትን ልዕልና ለማመልከት
እንጂ እነዚህ በረከቶቹ በመንፈሳዊ ዓለም ብቻ የተወሰኑ እንደሆን ለማመልከት አይደለም። ይህ ሥፍራ ጌታችን
ወደ አባቱ ዘንድ ሲመለስ ጌታና ክርስቶስ ሆኖ የተሾመት ሥፍራ ነው። ስለዚህ ይህ ቃል የክርስቶስን ሹመት፤
በርሱ በኩል ወደ ተመረቀው አዲስ ሥርዓትና መሲሐዊ ዘመን መፈንጠቅ ያመለክታል (Inaugurated
Eschatology)። ክርስቶስ አንድ ቀን የምንሆነውን ሁሉ አሁን በአብ ቀኝ እኛን ወክሎ ይዞልናል። እኛም
መንፈሱን ስለተቀበልን ከክርስቶስ ጋር አንድ እንድንሆን ተጠምቀናል ያም በረከት ከመንፈሱ የተነሳ በመጠን
መካፈል ጀምረናል። ያህዌህ በዘመን ፍጻሜ ሊያደርግ የወደደው አሁን ተመርቋል፤ ምንም እንኳ ይጠናቀቅ ዘንድ
ግን ዳግም-ምጽዓቱን ገና ቢጠብቅም። ስለዚህ ይህ እውነታ (በክርስቶስ በሰማያዊ ስፍራ) መዳናችን አሁን
እውን እንደሆን ነገር ግን ገና ወደ ፊት ደግሞ በሙላት እንደሚገለጥ ያሳየናል።
o “በሚመጡ ዘመናትም በክርስቶስ ኢየሱስ ለእኛ ባለው ቸርነት ከሁሉ የሚበልጠውን የጸጋውን ባለ
ጠግነት ያሳይ ዘንድ፥ ከእርሱ ጋር አስነሣን በክርስቶስ ኢየሱስም በሰማያዊ ስፍራ ከእርሱ ጋር
አስቀመጠን።”
የተባረክነው በሥሉሱ አምላክ አሰራር ነው፡- ከላይ እንዳየነው በዚህ ወጥ ረጅም ዓረፍተ-ነገር ውስጥ አዝማች
መሰል ሐረጎችን ሶስት ጊዜ በመደጋገም ሐዋርያው በመዳናችን ውስጥ የእያንዳንዱን የስላሴ አካል ሚናና ዓላማ
ይነግረናል (ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ…ቁ 6፤ 11 ና 14 ላይ)። መዳናችን በስሉስ አምላክ አካላት የተቀመረ፤
የተቀነባበረና የሥሉሱን አምላክ ክብር የሚያንጸባርቅ ነው። በስሉስ አካላት መዳፍ የተቀረጽን ነን። አንዱ
አምላክ አብ በወልድና በመንፈሱ የተዳሰሰ ስጦታ ተሰጥቶናል። ስለዚህ ስጦታው አምላካችንን እንድናውቅ
ያደርገናል።
o አብ፦ ልጁን የሚመስሉ ንፁሃን ልጆች እንሆን ዘንድ እንደ በጎ አቀደ
ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን።
በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን።
“በውድ ልጁም እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ”
በአጭሩ የመዳናችን ግብ የእግዚአብሔርን ቤተሰቦች እንድንሆን ነው፤ ይህም ልጅነታችን ነው። ለመከለስ ያህል
መዳናችን ሁለት ጫፎችና ሦስት ገጽታዎች እንዳሉት አይተናል። መዳናችን ከየትና ወዴት የሚሉ ጫፎች
አሉት። ከዬት የሚለው ጥያቄ የሚያሳየን ባመንን ጊዜ አሮጌው ሰው ከነ ፍርዱ ተሽሮ አዲሱን ሰው
መልበሳችንን (ይህም እግዚአብሔር አብ በወልድ ሥራ አማካይነት በመንፈስ ቅዱስ ማሕተም አትሞን
የሓጥያትን ይቅርታ መቀበላችን) ሲሆን ወዴት የሚለው ደግሞ በዚሁ በአንዱ መንፈስ አማካይነት ዳግም
ክርስቶስ ሁሉን ሊጠቀልል በሚገለጥበት ጊዜ ሙሉ በሙሉ እውን ወደ ሚሆነው ልጅነታችን ላይ ያነጣጥራል።
ከዚህ የተንሳ መዳን ሦስት ገጽታ አለው። በአንድ ገጽታ ድነናል። በሌላ ገጽታ አሁን ዕለት ዕለት እየዳንን ነው።
ደግሞ አንድ ቀን ልጁ ሲገልጥ በሙላት እንድናለን። ክብር ሁሉ ለሉሱ ጌታ ይሁን!
፫
በሁለት እውነታዎች ተወጥሮ የተቃኘ
መዳናችን
መዳናችን አሁን ተገልጧል…መዳናችን ገና በሙላት ይገለጣል!
ከዚህ ቀደም ከወንጌላዊው ዮሐንስ ነገረ-ትረካ ወስደን፤ ወልድ ተልዕኮውን የሚፈጽምበት ሰዓት አይተናል፤
ይህም የመስቀሉ ሥራ ነው። ይህ ተልዕኮ ታላቅን መዳንን ገልጧል። በዚህ ተልዕኮ ውስጥ እውነተኛው አብና
የተላከው ወልድ ተገለጠዋል። ይህንን ማወቅ የዘላለም ሕይወት ነው። ይህንን ተመልክተናል። ሆኖም ግን
ይህንን ታላቅ መዳን በሌላ ገጽታ ደግሞ ሦስቱ ወንጌላውያን (ማቴዎስ፤ ማርቆስና ሉቃስ) በእግዚአብሔር
መንግሥት ዙሪያ በተቃኘ ዕይታቸው ሲተርኩ የነብያትን ድምጽ ሊፈጽም በዳዊት ቤት ክርስቶስ ሆኖ፤
መንግሥትን ይዞ፤ በመገለጡ ላይ በማነጣጠር ፤መዳን የእግዚአብሔር መንግሥት አሰራር እንደሆን ያሳዩናል
(ማር 1:15)። ልክ በዮሐንስ ወንጌል መስቀልና የዘላለም ሕይወት የማይለያዩ ገጽታዎች እንደሆኑ፤ ሦስቱም
ወንጌላውያን መስቀልና ዙፋን እነደማይለያዩ ይነግሩናል። ስለዚህ መዳን የእግዚአብሔርን መንግሥት ባሕርይ
የተጎናጸፈ እንደሆን እንመለከታለን።
ከዚህ የተነሳ የመዳናችን ሌላው ገጽታና ሊሰመርበት የሚገባ እውነታ፤ አሁን በእውነት ድነናል! መዳንን
ተጎናጽፈናል፤ መዳን አሁን ገንዘባችን ሆኗል፤ ቃል ኪዳን ውስጥ ታስረናል፤ ሆኖም ግን መዳናችን ክርስቶስ
በግርማው ከመላዕክቱ ጋር መንግስቱን ይዞ ዳግም እስኪገለጥ ድረስ ቀና ብለን አንጋጠን የምንጠብቀውም
እውነታ ነው!” ስለዚህ ልክ የእግዚአብሔር መንግስት በመጀመሪያ መምጣቱና በዳግም ምጻአቱ መካከል በሁለት
ዘመናት እነደተወጠረ እንዳየን (ክፍል 008-06 እስከ 008-08 ን ያድምጡ) መዳናችንም የመንግሥቱ አሰራር
በረከት ከመሆኑ የተነሳ በነዚህ ውጥረቶች ውስጥ አለን። ድነናል…ገና ደግሞ እንድናለን። የጌታ ነን…ደግሞ
አንድ ቀን የጌታ እንሆናለን። አሁን አንድ ቀን የምንሆነውን ሆነናል…በሌላ እጅ ደግሞ ተዘርግተን ወደ ፊት
አሁን ገንዘባችን የሆነውን በሙላት እንወርሳለን።
“በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ” 1
Pe 1:3–5 .
ሁለቱም አሁን በዘመን መጨረሻ (በመጀመሪያ መምጣቱና በዳግም ምጻአቱ መካከል) ላለን አማኞች እውነት
ነው። መዳናችን ገና የሚገለጥ ነው…መዳናችን አሁን የምንቀበለው ነው። ይህ እወነታ የተመሰረተው ግን
ከእግዚአብሔር መንግሥት አገላለጥ አንጻር ነው። ይህንን ነው ጌታ የመንግሥተ ሰማያት ሚስጢር ብሎ
ያስተማረው። አሁን በዚህ በጨለማው ዓለም ውስጥ ሰርጾ ልጁን በመበላክ መንግሥቱ ተመርቃለች፤ ሆኖም
ግን መንግሥቱ ሁሉን ልትጠቀልል ገና ትገለጣለች። ይህንን ለምሳሌ፡
ክርስቶስ በምድር ሳለ የእግዚአብሔር መንግሥት በምድር ላይ በሐይል ተገልጣ ነበር። ከዚህ የተነሳ መሲሐዊ
ዘመን ፈነጠቀ። ነብያት ይሆናል ያሉት መፈጸም ጀመረ ሆኖም ግን የፍርድን ሥራ አልገለጠም (here you have
fulfillment without consummation)። የኢየሱስ ደ/መዛሙርት በአዲሱ መሲሃዊ ዘመን ውስጥ ናቸው።
መንግሥቱ በዙሪያው ላሉ ሁሉ ሠፍኗል። መብላትና መጠጣት የመሲሃዊ ግብዣ ምሳሌ በመሆኑ ንጉሱ እያለ
ጾም ተገቢ አይደለም። ሆኖም ግን አሮጌው የሙሴ ኪዳን አልፎ አዲስ ኪዳን ስለሚመረቅ፤ አሮጌው የሕግ
ሥርዓት ስለሚሻርና አዲሱ የመንፈስ ሕግ ስለሚደነገግ፤ እንደ ድሮው ሥርዓት መመላለስ አይችሉም። አሁን
ንጉሱ ክርስቶስ ከእነርሱ ጋር እያለ መጦም አያስፈልጋቸውም። ሆኖም ግን አንድ ቀን “ሙሽራው ከእነርሱ
የሚወሰድበት ወራት ይመጣል፥ በዚያ ወራትም ይጦማሉ” ይህ ማለት ክርስቶስ፤ ሙሽራው ከመካከላቸው
ሲወሰድ ከዚህ ቀደም ወዳልነበረ እውነታ ውስጥ ስለሚገቡ መጦም ይጀምራሉ። ይህ እውነታ ሙሽራው
ክርስቶስ መጥቷል ደግሞም ለሁለተኛ ጊዜ ይመጣል የሚል ነው…ይህን እውነታ ነው በውጥረት መያዝ ያለብን
ያልኩት። ይህ ጾም በዚህ ምድራዊ ድንኳን ከብዶብን ማራናታ የሚል ጾም ነው። አዳኛችን ተመለስ…
መድኅናችን ተገለጥና መዳናችንን ፈጽም የሚል ጩሀት ነው። ይህንን ዘመን ነው የመጨረሻ ዘመን የሚለው።
ይህ ልጁ የተገለጠበት ዘመን ነው። እግዚአብሔር በብዙ መንገድ በብዙ ጎዳና በነብያቱ የተናገረበት ዘመን
ሳይሆን፤ ይህ አሁን በልጁ የተናገረበት የመጨረሻ ዘመን ነው። መንፈሱ የተላከበትና ከነገድ ከቋንቋ አሕዛብ
እየተቀደሱ በእምነት ወደሆነ መታዛዝ የሚቀደሱበት ዘመን ነው። መዳናችን በተሰጠን መያዣ እናረጋግጣለን፤
በሌላ መልኩ ደግሞ ይሄው መንፈስ ለቤዛ ቀን የታተምነበትም መንፈስ በሆኑ ፍጻሜ ገንዘቡ የሆንን ሕዝቦች
ነን። አዲስ ኪዳን ይህንን እውነታ በብዙ ዓይነት ዘይቤያዊ አነጋገሮች ይገልጥልናል። አንድን ምሳሌ እስኪ
እንመልከት
እጮኛ…ሙሽራ…ታዳሚ!
“በእግዚአብሔር ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፥ እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ
አጭቻችኋለሁና” (2 ቆሮ 11:2)
በአይሁድ አስተሳሰብ እጮኝነት የዝግጅት ጊዜ እንጂ በአሁን ዘመን አስተሳስብ እንደሆነው ተጋቢዎቹ ለትዳር
ምቹ እንደሆኑ እርስ በእርስ የሚተያዩበት መንገድ አልነበረም (ይህ ማለት ግን በዘመኑ አሰራር ላይ ተመርኩዞ
መለኮታዊውን ሐሳብ ለማንጸባረቅ እንጂ ይህ እ/ር ለተጋቢዎች ያለውን ፈቃድ ማንጸባረቁ አይደለም)
ከእጮኝነት ወደ ጋብቻ ያለው ወቅት ሙሽራው ቤት የሚሰራበት፤ እርሻውን የሚያርስበት፤ ከአባቱ የልጅነት
ድርሻውን የሚረከብበት…በአጭር ቃል ሦስት ጉልቻ የሚመሰርትበት ወቅት ነበር። ስለዚህ ቤተክርስቲያንን
የክርስቶስ እጮኛ አድርጎ በዘይቤያዊ አነጋገር ሲመስላት አሁን ቤተክርስቲያን የክርስቶስ ብትሆንም ሆኖም ግን
አንድቀን በሙላት የክርስቶስ የምትሆንበትም ቀን እንዳለ ማመልከቱ ነው። ልክ እጮይቱ በዚህ ወቅት ለሌላ
ወንድ መታጨት የትዳር ኪዳንን በማጣረስ ምንዝርና እንደፈጸመች እንደሚቆጠር እንደነበር (ማርያም ፀንሳ
ስትገኝ ዮሴፍ በስውር ሊተዋት መፈለጉ ከዚህ የተነሳ ነበር) አሁንም የክርስቶስ አካል የክርስቶስ ናት። ልቧ
የሁለት ወዳጆች ሊሆን አይችልም። ሆኖም ግን ይህ የዝግጅት ወቅት አልፎ ሙሽራው ወደ ሙሽራይቱ
የሚመለስበት ቀን አለ።
ከዚህ በኋላ ቀን ተወስኖ ድግስ ይጀምራል። በዚህ በምዕራቡ ዓለም ደጋሽ የሙሽራይቱ ቤተሰብ በመሆኑ
ብዙውን ውሳኔ የሚያደርጉት (ሥፍራውን፤ የታዳሚውን ቁጥር..ወዘተ)ና የራት ድግሱን የሚጥሉትም እነርሱ
ናቸው። በክርስቶስ ዘመን ግን ወንድ ሙሽራው ነበር ይህንን ሐላፊነት የሚወጣው (ግርምቢጥ ማለት ይህ
ነው)። በተጨማሪም በኛ ዘመን “እነሆ ሙሽራይቱ…here comes the bride” እስኪባል ድረስ የታዳሚው ልብና
ዓይን የሚንጠለጠለው በሙሽራይቱ ወደ አዳራሹ መግባት ላይ ነው። በሠርጋችን ዕለት ላይ እኔ ሙሽራው ወደ
አዳራሹ ስገባ ከጥቂት ጭብጨባና “ጎበዝ የኔ ልጅ” የሚሉኝ ይመስል ከአውራ ጣትና ከራስ ንቅነቃ በስተቀር
ብዙ አልደመቀም ነበር። ነገር ግን ይህ ቅናቴ ብዙውም ሥፍራ አልነበረውም ምክኒያቱም የምወዳት ሙሽራ
ለጥቂት ደቂቃ ዘገየችና ነው። በሩ አልተከፈተም። የእጇን አበባ አቀብሉኝ እያለች ያልተረዱላት
አስተናጋጆቿዋ ሲይሯሯጡ ደቂቃ በደቂቃ ሲጨምር መዘግየቷ፤ ኋላ ብቅ ስትል ለእርሷ እልልታውን ለእኔም
እፎይታውን አደመቀልን። አሁንም በክርስቶስ ዘመን የድግሱ ጭፈራና የታዳሚው ግፊያ ያለው በሙሽራው
ቤት ነበር። በሌላ አነጋገር “here comes the groom” (እውነቶትን ነው ግርምቢጥ ማለት ይህ ነው)። ስለዚህ
ሙሽራው ወደ ሙሽራይቱ ቤት በቀን ይመጣና የመጀመሪያውን መጠነኛ የምሣ ድግስ በሴቲቱ ቤት
ይካሔዳል። ከዚያ በኋላ እንደ ሙሽራው ቤት መንገድ ርዝማኔ የምሣው ድግስ አጠር ይላል። ሆኖም ግን
አንዳንድ ጊዜ በመንገድ ላይ ምን እንደሚገጥም ስለማይታወቅ በሙሽራው ቤት ያሉት ሚዜዎችና ታዳሚ
እንግዶች ቁጭ ብለው መጠባበቅ ምርጫ አልነበራቸውም። እንደ አሁኑ ዘመን የእጅ ስልክ በሌለበት ዘመን
ቀጠሮ አክባሪነት ትግሥትን ይጠይቃል። በዚህ መንፈስ እስኪ ይህንን የክርስቶስን ምሳሌ አድምጡ፡
በዚያን ጊዜ መንግሥተ ሰማያት መብራታቸውን ይዘው ሙሽራውን ሊቀበሉ የወጡ አሥር ቆነጃጅትን
ትመስላለች። 2 ከእነርሱም አምስቱ ሰነፎች አምስቱም ልባሞች ነበሩ። 3 ሰነፎቹ መብራታቸውን
ይዘው ከእነርሱ ጋር ዘይት አልያዙምና፤ 4 ልባሞቹ ግን ከመብራታቸው ጋር በማሰሮአቸው ዘይት ያዙ።
5
ሙሽራውም በዘገየ ጊዜ ሁሉ እንቅልፍ እንቅልፍ አላቸውና ተኙ። 6 እኩል ሌሊትም ሲሆን። እነሆ፥
ሙሽራው ይመጣል፥ ትቀበሉት ዘንድ ውጡ የሚል ውካታ ሆነ። 7 በዚያን ጊዜ እነዚያ ቆነጃጅት ሁሉ
ተነሡና መብራታቸውን አዘጋጁ። 8 ሰነፎቹም ልባሞቹን። መብራታችን ሊጠፋብን ነው፤ ከዘይታችሁ
ስጡን አሉአቸው። 9 ልባሞቹ ግን መልሰው። ምናልባት ለእኛና ለእናንተ ባይበቃስ፤ ይልቅስ
ወደሚሸጡት ሄዳችሁ ለራሳችሁ ግዙ አሉአቸው። 10 ሊገዙም በሄዱ ጊዜ ሙሽራው መጣ፥
ተዘጋጅተው የነበሩትም ከእርሱ ጋር ወደ ሰርግ ገቡ፥ ደጁም ተዘጋ። 11 በኋላም ደግሞ የቀሩቱ ቈነጃጅት
መጡና። ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ፥ ክፈትልን አሉ። 12 እርሱ ግን መልሶ። እውነት እላችኋለሁ፥
አላውቃችሁም አለ። 13 ቀኒቱንና ሰዓቲቱን አታውቁምና እንግዲህ ንቁ። (Mt 25:1–13)
የዚህ ምሳሌ ዓላማ ጌታችን የመንግሥቱን አገላለጥ ሚስጢር በምሳሌ ለማስተማር ነው። የእግዚአብሔር
መንግሥት ባሕርይ ይህንን ይመስላል….እንደ አንድ ሠርግ ድግስ። ሆኖም ግን የዚህ ምስሌ ዋና እምብርት
“ሙሽራውም በዘገየ ጊዜ” የሚለው ነው። የእግዚአብሔር መንግሥት ትወሰዳለች (ይህም የክርስቶስ ሞት
ነው )…ከዚህ የተነሳ ዳግም እስኪመለስ ድረስ የምትዘገይ ትመስላለች። መጠባበቅ የሞላባት ናት። ይህ ነው
የምሳሌው ዋና እምብርት (ስለዚህ ጉዳይ ምሳሌዎችን፤ ወንጌላትን…እንዴት ላንብብ በሚለው ትምህርት
ሥር እንነጋገራለን)። ሚዜዎቹ መተኛታቸው ስህተት አልነበረም። ሁለቱም ዓይነት ሚዜዎች፤ ልባሞችና
ሰነፎች፤ ተኝተዋል። ሆኖም ግን ልባሞቹ ተዘጋጅተው ሲተኙ ሰነፎች ግን ሳይዘጋጁ ተኙ።ግን አንድ ቀን
“ትቀበሉት ዘንድ ውጡ የሚል ውካታ” ይሆናል። ስለዚህ በዚህ ምሳሌ ውስጥ የተጠቀሱት መብራት፤ ዘይት፤
ማሰሮ፤ ቆነጃጅት፤ አሥር ሚዜዎች መሆናቸው….ልዩ ትጉም የላቸው። እነዚህ ለትረካው ቀጣይነት
መረማመጃ ይሆኑ ዘንድ ና የትረካው ዋና መልእክት እንዲደርስ ከአይሁድ እለት ሕይወት ጋር የሚዛመዱ
ማጀቢያዎች ናቸው። ለምሳሌ በዚህ ምሳሌ እንቅልፍ አልተተቸም። (በአንጻሩ ግን ለሐዋርያው ጳውሎስ
በሮሜ 13፡ ላይ አሁን የምንተኛበት የእንቅልፍ ጊዜ አይደለም ሲል ጌታ እስኪገለጥ ድረስ በዝግጅት መጠባበቅ
እንዳለብን ይነግረናል። ምንም እንኳ የሁለቱም ዝይቤያዊ አነጋገሮች ዋና ነጥብ “በንቃት መጠበቅ” ቢሆንም
ማቴዎስ የክርስቶስን ምሳሌ “ተዘጋጅቶ መጠበቅ” ላይ ሲያተኩር ሐዋርያው ግን ምሳሌውን “ከእንቅልፍ ነቅቶ
መጠበቅ” ላይ ያተኩራል ማለቴ ነው)።
ስለዚህ በዚህ የሰርግ ምሳሌ መዳናችን በሁለት መንገዶች ተገልጾልናል። በአንድ ወገን አሁን የጌታ ነን። በሌላ
ወገን ደግሞ ሙሽራውን በዝግጅት ገና እየተጠባበቅነው ነው። አንድ ቀን ግን ሁላችን ወደ በጉ ዕራት
እንታደማለን። ይህንን ግብ የራዕይ መጽሐፍ “የበጉ እራት” ብሎ ይጠራዋል። በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ታላቁ
የነገሥታት ንጉሥ ዳግም ሲመለስ ሁለት እራቶች እንዳሉ ያሳየናል። እነዚህም፡ የበጉ ዕራትና የታላቁ
የእግዚአብሔር እራት ናቸው
“እርሱም። ወደ በጉ ሰርግ እራት የተጠሩ ብፁዓን ናቸው ብለህ ጻፍ አለኝ። ደግሞም። ይህ የእግዚአብሔር እውነተኛ ቃል
ነው አለኝ” (Re 19:9 )
በበጉ ደም ለበጉ ክብር ይሆኑ ዝንድ ከነገድና ከቋንቋ የተዋጁት እነዚህ ወደ በጉ ሠርግ ገበታ ይታደማሉ። ይህም
የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ህዝብ መዳን ምሳሌ ነው። አንድ ቀን ከጌታ ጋር እንሆናለን። ይህም በምድራዊ
ቋንቋ ለመግለጽ ቢሞከር በድንግዝግዝ ታላቅ የሠርግን ቀን ይመስላል። ሆኖም ግን ደግሞ ሌላ ዕራት አለ።፡ይህ
እራት ግን አሰቃቂና የሚያስፈራ እራት ነው።
“አሕዛብንም ይመታበት ዘንድ ስለታም ሰይፍ ከአፉ ይወጣል፤ እርሱም በብረት በትር ይገዛቸዋል፤ እርሱም ሁሉን የሚገዛ
የእግዚአብሔርን የብርቱ ቍጣውን ወይን መጥመቂያ ይረግጣል። በልብሱና በጭኑም የተጻፈበት። የነገሥታት ንጉሥና
የጌታዎች ጌታ የሚል ስም አለው። አንድም መልአክ በፀሐይ ውስጥ ቆሞ አየሁ፥ በሰማይም መካከል ለሚበሩ ወፎች
ሁሉ። መጥታችሁ የነገሥታትን ሥጋና የሻለቃዎችን ሥጋ የብርቱዎችንም ሥጋ የፈረሶችንም በእነርሱም የተቀመጡትን
ሥጋ የጌታዎችንና የባሪያዎችንም የታናናሾችንና የታላላቆችንም ሁሉ ሥጋ እንድትበሉ ወደ ታላቁ ወደ እግዚአብሔር
እራት ተከማቹ ብሎ በታላቅ ድምፅ ጮኸ።” (Re 19:15–18 )
እዚህ ጋር “በብረት በትር ይገዛቸዋል” የሚለው ከመዝ 2:7-9 የተወሰደ ነው “አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወለድሁ፤
ለምነኝ አሕዛብን ለርስትህ የምድርንም ነገስታት ለግዛትህ እሰጥሃለሁ አንተም በብረት በትር ትገዛቸዋለህ
በብረት በትር ትጠብቃቸዋለህ፥ እንደ ሸክላ ሠሪ ዕቃዎች ትቀጠቅጣቸዋለህ” ከዚህ ቀደም የዳዊትን ኪዳን
በሰፊው ተነጋግረናል። ከዳዊት ጋር ያህዌህ የገባው ኪዳን በአብርሃም ተስፋ መሰረት ላይ ተመርኩዞ “በአንተ
የምድር ወገኖች ሁሉ ይባረካሉ…” ሲሆን በዚህ ኪዳን ለአህዛብ በረከትና ለምድር ሁሉ የእግዚአብሔርን ፍርድ
ይገልጣል። ለዚህ ነው በወንጌላት ላይ የእግዚአብሔር መንግሥት በእራት የተመሰለው። ወደ እራቱ የተጠሩት
ማለት የዳኑት ሲሆኑ ጥሪውን ንቀው ውጪ የቀሩት ግን ጥርስ ወደ ማፏጨት ይሔዳሉ። ጌታችን ኢየሱስ
በላተኛና የሐጥያተኞች ጓደኛ የተባለው በዚህ ምክንያት ነው። የአገር ስሜታዊነት የገዛ ልባቸውን ዓመጽ
የሸፈነባቸው (በሥጋ ብቻ የአብርሃም ልጆች የሆኑ) አይሁዳውያን፤ ይህ ታላቅ አዳኝ መሲህ ሲመጣ፤
ሐጥያተኞችንን፤ ቀራጮችንና ሮማውያንን ይበቀልልናል ብለው ሲጠብቁ፤ እርሱ ግን ሐጥያተኞችን ወደ
ገበታው ጠራ። አብሯቸው በላ። ተቀበላቸው። የመንግስቱ ተካፋዮች ሆኑ። የእስራኤል፡ጥሪም ሆነ የያህዌህን
ጽድቅ ካለማወቅ የራሳቸውን ጽድቅ ሊመሰርቱ የተገበዙት ግን ውጪ ቀሩ። ወደ ታላቁ ንጉስ እራት አህዛብ
ይመጣሉ “እላችኋለሁም፥ ብዙዎች ከምሥራቅና ከምዕራብ ይመጣሉ ከአብርሃምና ከይስሐቅ ከያዕቆብም
ጋር በመንግሥተ ሰማያት ይቀመጣሉ፤ የመንግሥት ልጆች ግን በውጭ ወደ አለው ጨለማ ይጣላሉ፤ በዚያ
ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል (Mt 8:11–12 ) በስሞዖን ቤት ግብዣም ላይ ይህንን መመልከት
ትችላላችሁ።
በተጨማሪ በዮሐንስ ራዕይ ሑለት እራት እንዳለ ሁሉ፤ ሁለት ሴቶችና ሁለት ከተሞች አሉ። አንዷ የበጉ
ሙሽራ ስትሆን ሌላኛይቱ ደግሞ ታላቂቷ ጋለሞታ ነች።
ከዚህ በኋላ በሰማይ። ሃሌ ሉያ፤ በዝሙትዋ ምድርን ያጠፋችይቱን ታላቂቱን ጋለሞታ ስለ ፈረደባት፥
የባሪያዎቹንም ደም ከእጅዋ ስለ ተበቀለ፥ ፍርዶቹ እውነትና ጽድቅ ናቸውና ማዳንና ክብር ኃይልም
የአምላካችን ነው ብሎ ሲናገር እንደ ብዙ ሕዝብ ታላቅ ድምፅ ያለ ድምፅን ሰማሁ። Re 19:1–2 .
እንደ ብዙ ሕዝብም ድምፅ፥ እንደ ብዙ ውኃዎችም ድምፅ፥ እንደ ብርቱም ነጐድጓድ ድምፅ ያለ ድምፅ ሰማሁ
እንዲህ ሲል። ሃሌ ሉያ፤ ሁሉን የሚገዛ ጌታ አምላካችን ነግሦአልና። የበጉ ሰርግ ስለ ደረሰ ሚስቱም ራስዋን
ስላዘጋጀች ደስ ይበለን ሐሤትም እናድርግ ክብርንም ለእርሱ እናቅርብ። ያጌጠና የተጣራ ቀጭን የተልባ እግር
ልብስ እንድትጐናጸፍ ተሰጥቶአታል። ቀጭኑ የተልባ እግር የቅዱሳን ጽድቅ ሥራ ነውና። እርሱም። ወደ በጉ
ሰርግ እራት የተጠሩ ብፁዓን ናቸው ብለህ ጻፍ አለኝ። ደግሞም። ይህ የእግዚአብሔር እውነተኛ ቃል ነው
አለኝ። Re 19:6–9 .
ሆኖም ግን ባለራዕዩ ዘይቤውን ይቀይጠዋል። ይህም ወደ በጉ ዕራት የተጠሩ ብጹዓን ናቸው…በማለት ይህ እራት በአንድ
ወገን የክርስቶስና የቤተክርስቲያን (በጥቅሉ) ሠርግ ሲሆን፤ በነጠላ ደግሞ አማኞች በዚያው ሠርግ ላይ የተጠሩ
ታዳሚዎችም እንደሆኑ ተመስሏል። ይህንን ነው ቅይጥ ዘይቤ ያልኩት። አንድ እውነታ ነገር ግን ድርብ ዘይቤ (ይህ
አማኞች በነፍስ ወከፍ ይህ የሙሽርነት ዘይቤ አይመለከታቸውም ምክኒያቱም ጋብቻው በጥቅል በእ/ር ሕዝብና
በክርስቶስ መካከል ሲሆን…ሆኖም ግን ደግሞ ይህ ዘይቤ የሚያመላክተው ጥልቅ አንድነት በረከት ተካፋዮች ናቸው)
በተጨማሪ ልክ አዳምና ሔዋን በኤደን ገነት ከአምላካቸው ጋር በከፊል አንድነት ይኖሩ እንደነበር፤ የእግዚአብሔርም
ሕዝብ ከሰማይ በምትወርደው በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ሰማይ ከምድር ጋር ይጋባል። የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች
መካከል ይዘረጋል። የእ/ር ማደሪያ ከሰው ማደሪያ አይለይም። ፊት ለፊት እያየን፤ ክብሩ እንደ ጸሐይ እይበራልን
የምንኖርበት እውን አለም ይህም የመዳናችን ሌላ አገላለጽ ነው። እነደዚሁ ሁለተኛ ከተማ ደግሞ አለች፤ ይህችም
ታላቂቱ ባቢሎን ናት።
“በግምባርዋም ምስጢር የሆነ ስም። ታላቂቱ ባቢሎን፥ የጋለሞታዎችና የምድር ርኵሰት እናት ተብሎ ተጻፈ።
ሴቲቱም በቅዱሳን ደምና በኢየሱስ ምስክሮች ደም ሰክራ አየኋት። ባየኋትም ጊዜ እጅግ ታላቅ ድንቅ
አደነቅሁ” ከዚህ በኋላ ታላቅ ስልጣን ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ፥ ከክብሩም የተነሣ ምድር
በራች። 2 በብርቱም ድምፅ። ታላቂቱ ባቢሎን ወደቀች፥ ወደቀች፥ የአጋንንትም ማደሪያ ሆነች፥ የርኵሳንም
መናፍስት ሁሉ መጠጊያ የርኵሳንና የተጠሉም ወፎች ሁሉ መጠጊያ ሆነች፤ 3 አሕዛብ ሁሉ ከዝሙትዋ ቍጣ
ወይን ጠጅ የተነሳ ወድቀዋልና፥ የምድርም ነገሥታት ከእርስዋ ጋር ሴሰኑ የምድርም ነጋዴዎች ከቅምጥልነትዋ
ኃይል የተነሳ ባለ ጠጋዎች ሆኑ ብሎ ጮኸ። 4 ከሰማይም ሌላ ድምፅ ሰማሁ እንዲህ ሲል። ሕዝቤ ሆይ፥
በኃጢአትዋ እንዳትተባበሩ ከመቅሠፍትዋም እንዳትቀበሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፤አንድም ብርቱ መልአክ
ትልቅን ወፍጮ የሚመስልን ድንጋይ አንስቶ ወደ ባሕር ወረወረው እንዲህ ሲል። ታላቂቱ ከተማ ባቢሎን
እንዲህ ተገፍታ ትወድቃለች ከእንግዲህም ወዲህ ከቶ አትገኝም”
“አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት
የለም። 2 ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ
ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ። 3 ታላቅም ድምፅ ከሰማይ። እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች
መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ
አምላካቸው ይሆናል፤ 4 እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥
ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና
ብሎ ሲናገር ሰማሁ። 5 በዙፋንም የተቀመጠው። እነሆ፥ ሁሉን አዲስ አደርጋለሁ አለ። ለእኔም። እነዚህ ቃሎች
የታመኑና እውነተኛዎች ናቸውና ጻፍ አለኝ። 6 አለኝም። ተፈጽሞአል። አልፋና ዖሜጋ፥ መጀመሪያውና
መጨረሻው እኔ ነኝ። ለተጠማ ከሕይወት ውኃ ምንጭ እንዲያው እኔ እሰጣለሁ። ድል የሚነሣ ይህን ይወርሳል
አምላክም እሆነዋለሁ እርሱም ልጅ ይሆነኛል” Re 21:1–7
ስለዚህ በእግዚአብሔር ሕዝብ አንድ ቀን መዋጀትና በአሁኑ መካከል የእግዚአብሔር ሕዝብ ይህንን ታላቅ
መዳን እየተጠባበቅን እንኖራለን። ይህ መጠባበቅ ግን የሕይወት ተሐድሶን ገንዘቡ ያደረገ እንጂ፤ እጅንና እግርን
አጣጥፎ መቀመጥን አያሳየንም። ያንን እራት እያሰብን አሁን የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆንን የጌታን እራት
እንቋደሳለን። እንደገና አሁንም ይህ መስቀልና ዙፋን አብረው እደሚሰሩ እናያለን። የጌታ እራት በአንድ መንገድ
ጌታ ስለ መዳናችን ደሙን ማፍሰሱንና ሥጋውን መቁረሱን ስናስብ፤ በሌላ መንገድ ደግሞ በእ/ር መንግሥት
አንድ ቀን የምንካፈለውን ታላቅ መዳን መጠባበቃችንን ይሳያል “ጽዋንም ተቀበለ አመስግኖም። ይህን
እንካችሁ በመካከላችሁም ተካፈሉት፤ 18 እላችኋለሁና፥ የእግዚአብሔር መንግሥት እስክትመጣ ድረስ ከአሁን
ጀምሮ ከወይኑ ፍሬ አልጠጣም አለ (Lk 22:17–18 )”
አሁን ድነናል ደግሞ በሙላት እንድናለን (this is because when Christ was personal present on earth, he
inaugurated both the Kingdom and the new covenant in their real sense but not in their
consummated sense)። ከዚህ የተነሳ መዳናችን በነዚህ ሁለት እውነታዎች መካከል ተወጥሮ የተቃኘ ነው።
ሥጋዊ ሞትን ገና እንሞታለን ሆኖም ግን ሞትን አሁን አሸንፈናል፤ በርግጥ ከሞት ወደ ሕይወት አሁን
ተሸጋግረናል (John 5:24 ; 3:18 11:24 ; 1 Cor. 15:52 )። በእርሱ የሚያምኑትም የማያምኑትም ገና
ዙፋን ተዘርግቶ የምንዳኝበት ቀን ወደ ፊት ነው፤ ሆኖም ግን አሁን እኛ ያመንን ከኩነኔ አምለጠናል (John
3:18 በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን
ተፈርዶበታል)። አሁን ሐጥያት አይገዛንም (ሮሜ 6፡14) ከሐጥያት ሐይል ነጻ ሆነናል። ሆኖም ግን ገና ሐጥያት
ከህይወታችን ሙሉ በሙሉ የሚወገድበት ቀን ይመጣል (ራዕ 21፡4-5)፤ እስከዚያ ድረስ ከሐጥያት ጋር
እንጋደላለን (1 ዮሐ 1:8-10፤ ዕብ 12:4)፤ ከሥጋ ጋር ጠብ አለን (ሮሜ 8:13)
ከላይ እንዳየነው “ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ወራት ይመጣል” ይህ ነው ይህንን ውጥረት
የወለደው። በክርስቶስ መጀመሪያ መምጣትና ዳግም መምጣት መካከል ያለው ልዩነት የተመረቀ ኪዳን/
መንግሥት ነው። ንጉሳችን ከምድር የተወሰደበት ወራት ውስጥ ብንሆንም፤ አዲስ ኪዳን ግን ይህንን ልዩ
አስደናቂ እውነት ያውጅልናል።
“ጌታ ጌታዬን ጠላቶችህን የእግርህ መረገጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ…” መዝ 110:1
እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም ነገር ግን። አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ
ያለው እርሱ ነው፤ 6 እንደዚህም በሌላ ስፍራ ደግሞ። አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ
ይላል። 8 ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ ከተፈጸመም በኋላ በእግዚአብሔር እንደ
መልከ ጼዴቅ ሹመት ሊቀ ካህናት ተብሎ ስለ ተጠራ፥ ለሚታዘዙለት ሁሉ የዘላለም መዳን ምክንያት
ሆነላቸው። (Hebrews 5:5–6 )
ንጉሳችን በተሻለ ኪዳን፤ በተሻለ ዙፋን፤ በተሻለ መቅደስ፤ በተሻለ ክህነት እጅ ወዳል ሰራው ቤተ መቅደስ
ገብቷል እንደዚሁም በአብ ቀኝ ዙፋን ተቀምጧል። መዳን ተመረቀ! አዲስ መንገድ ተከፈተ! ይህንን ነው
እርሱ ግን ስለ ኃጢአት አንድን መሥዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፥ ጠላቶቹም የእግሩ መረገጫ
እስኪደረጉ ድረስ ወደ ፊት ይጠብቃል። አንድ ጊዜ በማቅረብ የሚቀደሱትን የዘላለም ፍጹማን አድርጎአቸዋልና… 19-20
እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት
በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን፥ በእግዚአብሔርም ቤት ላይ የሆነ ታላቅ ካህን ስላለን፥ ከክፉ ሕሊና ለመንጻት
ልባችንን ተረጭተን ሰውነታችንንም በጥሩ ውኃ ታጥበን በተረዳንበት እምነት በቅን ልብ እንቅረብ፤ (Hebrews 10:12–
14 ፤ 19-22)
መንፈስ ቅዱስንም ከአብ ዘንድ ተቀብሎ ወደ ምድር አፍሶልናል። ከመንፈስ ቅዱስ የተነሳ ክርስቶስ
የጀመረውን ሥራ በምድር ይቀጥላል (ጰራቅሊጦስ) ደግሞም በሰማያዊ ሥፍራ እውነት የሆነውን
በቤተክርስቲያን እውን እንዲሆን ያደርጋል።ከዚህ የተነሳ፦
አሁን ሞተናል…አዎን በሥጋ እያለን ሞተናል። ይህ ማለት የአሁኑ ኑሯችን ምትሃት ነው ለማለት አይደለም።
እጅግ ረቂቅ በሆነ መልኩ ሕይወታችን ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ከመተሳሰሩ የተነሳ፤
የክርስቶስ እውነታዎች በእኛም እውነት ሆነዋል። ታያላችሁ? እርሱ በመስቀል እደሞተ፤ እኛም ተሰቅለናል፤
እንደ ተቀበረ በጥምቀት ተቀብረን በአዲስ ሕይወት ተነስተናል፤ እርሱ በአባቱ ዘንድ እንደተመለሰ እኛም
ከእርሱ ጋር ተሰውረናል። ውጤቱ በዚህች ምድር ላይ ስንኖር እንደ መጻተኛ መስቀሉን ተሸክመን እንኖራለን
ማለት ነው። አሁን ከክርስቶስ የተነሳ ሞተናል። አንድ ቀን እርሱን ስናየው እርሱን ስንመስል ይህ አሁን
በክርስቶስ እውነት የሆነው የዚያኔ ክቡሩን ሥጋ ስንመስል ሙሉ በሙሉ እውነት ይሆናል። እስከዚያ ድረስ ግን
በዚህ ውጥረት ውስጥ አለን። ውጥረቱ የሚገለጠው “ራሳችንን በመካድና መስቀሉን በመሸከም ደቀ/መዝሙር
በመሆን ነው። ሞተናል ማለት አሁን በመንፈስ ቅዱስ ሐይል ተጸእኖ ሥር ውስጥ እንኖራለን ማለት ነው
በመንፈስ ቅዱስ የሥጋን ምኞት እንገድላለን። በመንፈስ እንመላለሳለን ደግሞም እንኖራለን። ሁለቱንም
ገጽታዎች ሐዋርያው በአንድ ላይ ያቀርብልናል። አሁን ሞተናል፤ ተነስተናል በክርስቶስ ተሰውረናል (ቁጥ.3)
አንድ ቀን ደግሞ በክብር እንገለጣለን (ቁጥ. 4)፤ እስከዚያስ? “ ….. ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ
ባለበት በላይ ያለውን እሹ። በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም (ቁጥ 1–2)”
እዚህ ጋር ተመለከታችሁ? ልጆች ነን ይለናል ደግሞም ገና ሲገለጥ ደግሞ እርሱን እንመስላለን። ይህንን ነው
ውጥረት ያልነው። ነን….ደግሞ እንሆናለን። ልዩነቱን ን ተመልከቱ፤ አሁን ልጆች በመሆናችንና ደግሞ ወደፊት
በሙላት ሲገለጥ በምንሆነው መካከል ሐላፊነታችን ምንድር ነው? ልክ ሐዋርያው ጳውሎስ ሐሳባችሁን
በሰማይ ይሁን እንዳለን..ዮሐንስ ደግሞ እንዲህ ይለናል “ይህን ተስፋ የሚያደርግ ሁሉ እርሱ ንጹሕ እንደ ሆነ
ራሱን ያነጻል።” አሁን በሕይወታችን ልጅነታችን የምንገልጠው በመንፈስ ቅዱስ ሐይል በመታዘዝ ነው!
መታዘዝ ያልሆነውን ለመሆን ሳይሆን በክርስቶስ የሆነውን ለመሆን ነው። መታዘዝ ለመዳን ሳይሆን በርግጥ
ስለዳንን የተገባ ህይወት ነው። መቼም አንባቢዪ ይህንን ይረዳል ብዬ ባምንም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት
በትንሳኤ አካል ስንወርስ፤ ትዕዛዛት ሥፍራ የላቸውም። ስንቶቻችሁ አሁን ልባችሁን እንዲመታ እያዘዛችሁት
ነው? ርግጥ ነው ይህንን ስታነቡ አይናችሁን እያዘዛችሁት ነው። ግን ደግሞ ሳንባችንን እያዘዝነው አይደለም።
እነደዚሁ ሁሉ ይህ የአሁን ኑሯችን በመታዘዝ ልጅነታችንን የምንገልጥበት ሕይወት ሲሆን፤ መጪው ዓለም
ውስጥ የምንወርሰው የትንሳኤ አካል ግን ሙሉ በሙሉ በመንፈስ ቅዱስ የተመራ ከመሆኑ የተነሳ በባሕሪያችን
እንዲሁ ጽድቅን እያደረግን እንኖራለን። ለዚህ ነው
“ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፥ መንፈሳዊ አካል ይነሣል። ፍጥረታዊ አካል ካለ መንፈሳዊ አካል ደግሞ አለ። ፊተኛው ሰው
አዳም ሕያው ነፍስ ሆነ ተብሎ ተጽፎአል፤ ኋለኛው አዳም ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ሆነ…” 1 ቆሮ 15:45
እነሆ፥ አንድ ምሥጢር እነግራችኋለሁ፤ ሁላችን አናንቀላፋም ነገር ግን የኋለኛው መለከት ሲነፋ ሁላችን በድንገት
በቅጽበት ዓይን እንለወጣለን፤ መለከት ይነፋልና ሙታንም የማይበሰብሱ ሆነው ይነሣሉ እኛም እንለወጣለን። ይህ
የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋልና።
በሞት ትንሳኤ ይህ የሚበሰብሰው የሚሻር ከሆነ፤ ታድያ ይህ የአሁኑ ሕይወት ምን ፋይዳ አለው? ይህንን ክፍል
ሲዘጋ እንዲህ ብሎ ይጨርሳል
ስለዚህ፥ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ድካማችሁ በጌታ ከንቱ እንዳይሆን አውቃችኋልና የምትደላደሉ፥
የማትነቃነቁም፥ የጌታም ሥራ ሁልጊዜ የሚበዛላችሁ ሁኑ። 1 Co 15:58
በዚህ በአሁኑ ሰውነታችንና ወደ ፊት በምንለብሰው ሰውነት መካከል ልዩነት እንዳለ ሁሉ፤ ግንኙነትም አለው።
በዚህ ሥጋ የምንዘራውን በሌላ መልኩ እናጭዳለን (ገላ 6)። ስለዚህ በመንፈስ እንጂ በሥጋ አንዘራም።
ከመንፈስ የዘላለምን ሕይወት እንድናጭድ።፡ስለዚህ በክርስቶስ የተወደዳችሁ ቅዱሳን መዳናችን መጀመሪያ
ካመንበት ቀን ይልቅ አሁን ወደ እኛ ስለቀረበ የመዳንን ተስፋ እንደ ጋሻ፤ መዳናችንን እንደ ራስ ቁር፤ የሰላሙን
ወንጌል የሚያበስሩ እግሮች ተጫምተን እንጠብቅ!
ክራር-ነክ ሙዚቃ መሳሪያዎች በየጊዜው ይቃኛሉ። ይህም በሁለት ጥግ እያንዳንዱ ክሮች ትክክለኛ
ቅኝታቸውን እስኪይዙ ድረስ መወጠር አለባቸው። አሊያ ዜማቸው ጥዑም አለመሆን ብቻ ሳይሆን የዜማን
መርህ ስለሚጣረስ ዜማ መደርደር አይችሉም። አንዷ ክር በግማሽ ወይም በሙሉ ኖታ ወጣ ወይ ወረድ
ብትል፤ ዜማው ስለሚበላሽ ተጨዋቹ መሳሪያውን መቃኘት አሊያም ቅኝት የሚያውቅ ሰው መጥራት
አለበት። ልክ እንዲሁ ወንጌላችንም በክርስቶስ መምጣትና ዳግም መምጣት ተወጥሮ የተቃኘ ቃል ነው። ከዚህ
ውጥረት የተነሳ መዳናችን፤ ተስፋችን፤ ልጅነታችን፤ በረከታችን፤ አላማችን፤ ቅድስናችን..ወዘተ ልክ እንደ
እያንዳንዱ የክራር ክሮች ቅኝት ይዘዋል። ክርስቶስ ከሰማያዊ ሥፍራ ሆኖ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት ይህንን
ታላቅ የማዳን ዜማ በዓለም ዙሪያ ላሉ ህዝቦችና በአየሩ ላይ ላሉ አለቆች ብዙ ገጽታ ያለውን ጥበብ
ይደረድራል። ይህ ግን በጥሩ መልክ የተቃነች ከሆነ ብቻ ነው። ይህን ሚዛናዊነት ካለመጠበቅ የተነሳ፤
ቤተክርስቲያን በታሪኳ ውስጥ ጽንፈኛ እንቅስቃሴዎች ሲነሱ አይታለች። ይህ ማለት፤ በአንድ እጅ በእውነት
ድነናል በሌላ መልኩ ደግሞ ገና ሙሉ በሙሉ መዳናችን አንድ ቀን እንደሚገለጥ በሚዛን አለመያዝ ነው።
በአዲስ ኪዳን እነዚህ ሁለት ጽነፈኝነቶች በቅዱሳት መጻሕፍት ለትምህርታችን ተጽፈውልናል። ለምሳሌ
ያህል የተሰሎንቄን ቤተክርስቲያንና የቆሮንቶስን ቤተክርስቲያን እንደ ናሙና አድርገን እንውሰድ።
ለዚህም ደግሞ እንደ አምላካችን እንደ ጌታም እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፥ የጌታችን የኢየሱስ
ክርስቶስ ስም በእናንተ ዘንድ ሊከብር እናንተም በእርሱ ዘንድ ልትከብሩ፥ አምላካችን ለመጥራቱ
የምትበቁ አድርጎ ይቈጥራችሁ ዘንድ፥ የበጎነትንም ፈቃድ ሁሉ የእምነትንም ሥራ በኃይል ይፈጽም
ዘንድ ስለ እናንተ ሁልጊዜ እንጸልያለን።
ለዚህች አይነቷ ጽንፈኛ ቤተክርስቲያን በሥቃይ ማለፍ፤ በመከራና በውርደት ማለፍ ልክ እንደ ክርስትና
ማረጋገጫ ምልክት ትወስዳለች። የተቀደደ ጫማና የተቦጫጨቀ ልብስ የሌለው እውነተኛ አማኝ አይደለም።
ቃል አጋኖዬ መቼም ግልጽ ይሆናል ብዬ አስባለሁ። ሐዋርያው ጳውሎስ ሮሜ ምዕራፍ ሠባትን ብቻ ሳይሆን
ምዕራፍ ስምንትንም የጻፈው እርሱ መሆኑን ማሰብ ተገቢ ነው።
በአንጻሩ ደግሞ የቆሮንቶስ ቤተክርስቲያን አለች። አቤት! አቤት! ይህች ደግሞ ያዙኝ ልቀቁኝ የምትል ሁከት
የበዛባት ቤት ነች። ይህች ቤተክርስቲያን ደግሞ አሁን በክርስቶስ በተሰጠን በረከቶች ላይ ትልቅ አጽኖኦት
ከማድረጓ የተነሳ ዘላለማዊ ርስቷን አሁን ያደረገች፤ ክርስቶስን መጠባበቅ የዘነጋችና ገና ኢየሱስ ሲገለጥ
በሙላት የምንወርሰውን አሁን ሙሉ በሙሉ እንደወረስን አድርጋ የምታጋንን ነች። ከዚህ የተነሳ አንዳንዶች
እንደመልአክ ሆነናል ቢሉና ሙታን ትንሳኤ አሁን አሁን ሆኗል የሚል አማኖች ቢሞሉባት አያስገርምም፡፤ ገና
የሚሆነው ለእርሷ አሁን ነውና። የዓለም ሀብት ትወርሳለህ…የረገጥከውን ትወርሳለህ….ሕንጻው ያንተነው…
ብሩና ወርቁ ያንተ ነው…ሳታጠና ፈተና ታልፋለህ…ሳትሰራ ወርቅ በወርቅ ትሆናለህ….የንጉስ ልጅ ስለሆንህ
ኮትና ሱሪህ ከምን እንደተሰራ እያወራህ የመንፈሳዊነትህን ልክ ትገልጣለህ። ለዚህች አይነቷ ቤተክርስትያን
ለመከራ ሥፍራ የላትም። በህመም ማለፍ ሽንፈት ነው። የንጉስ ልጅ ነህና እንደ ንጉስ ትንቀባረራለህ ባይ ናት።
ይህንን የሐዋርያውን ምጸት እስኪ ስሙልኝ?
ይህች ቤተክርስቲያን ጌታ በመካከሏ ከሰራው አስደናቂ ማዳን ልቧ ከመሸፈቷ የተነሳ ሚዛናዊነቷን አጣች። ጌታ
ከመካከሏ ለጥቂት ጊዜ በሃይልና በብዙ የጸጋ ሥጦታ ስለሞላት ያገለገላትን ሐዋርያና መንፈሳዊ አባቷን በንቀት
ዓይን መመልከት ጀመረች። የጳውሎስና የጓደኞቹ በመከራና በሕመም ማለፍ እንደ መንፈሳዊ ግለት መቀዝቀዝ
መለኪያ አድርጋ አሁን ወደ ቤተክርስቲያን ከመጡት ዘራፍ በሚሉ ሐዋርያ ሳይሆኑ ሐዋርያት በሆኑ አዳዲስ
መሪዎች የጳውሎስን ሐዋርያነት ማናናቅ የጀመረች ትመስላለች።
ይህ አሁን ያለንበትን ዘመን ይመስላል። የእምነት-ቃል እንቅስቃሴ በይፋ ከጀመረ ከአንድ ሰው እድሜ በታች
ነው። የዚህ አስተምህሮት ትልቅ አባት አድርገው የሚቆጠሩት ከሞቱ ጥቂት ዓመት ጊዜው ነው። የዚህ
እንቅስቃሴ አራማጅ የሆኑት ጥቂቶች ግን የክርስቲያኑን ቴሌቪዥን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠሩት ከመሆኑ
የተነሳ የዛሬ 30 ዓመት ይህ ትምህርት የትም አይደርስም ብለው ብዙዎች ቢገምቱም አሁን ትልቅ ሥር ሰዶ
መፍትሔ ከየት እንደሚመጣለት የማይታወቅ ችግር ሆኗል። የዚህ እንቅስቃሴ ትልቅ ስህተት ይህ ከላይ ያየነው
ጽንፈኝነት ነው። በአሁኑ ላይ ጥልቅ ትኩረት ከመስጠታቸው የተነሳ ብልጽግና እንጂ ክርስቶስ የማይሰበክበት
መድረኮች ሆነዋል። ለምሳሌ ያህል ከመሰረታዊ ትምህርታቸው መካከል ሦስቱ
(1) “በቃል ነገሮችን ካለመሆን ወደ መሆን ታመጣለህ” የሚለው እጅግ አሰቃቂ አነጋገር ነው (ምክኒያቱም
ምንም ቢደባበስና ከአውዱ የተለየ ጥቅስ ከማምረው እውነት ለማስመሰል ቢሞክሩም ይህ የመለኮትን ሥራ
መሻማት ነው።፡እግዚአብሔር ብቻ ነው ተናግሮ የሌለውን ወደ መሆን የሚያመጣው። በኢሳያስ መጽሐፍ
ያህዌህ ራሱን ከጣኦታትና ከአሕዛብ አማልክት የለየው በዚህ ሐይሉ ነው “እነዚህን ሁሉ በቃሉ የፈጠረ ማን
ነው?”)። በመጽሀፍ ቅዱስ መለኪያ ይሁን በቤተክርስቲያን ታሪክ ማስረጃ፤ ይህ እንቅስቃሴ የተወገዘና
ከየትኛውም ቤተእምነት ያሉ የቤተክርስቲያን መሪዎችና የመጽሐፍ ቅዱስ አዋቂዎች ያወገዙት
አስተምሕሮት ነው። በርግጥ ይህ አስተምህሮት ሥር ከመስደዱ የተነሳ እውነት ቢመስልም ጠለቅ ብሎ ላየው
ግን ቅዱሳት መጻህፍትን የሚጣረስ ብዙ ነገር አለው።
(2) ሌላው ለዚህ አስተምሕሮት መሰረት የሆነው አዋጅ ቃላቸው “እግዚአብሔር በእምነት የሌለውን አድርጎ
ይናገራል…ስለዚህ አንተም በእምነት የሌለውን ነገር አድርገህ ተናገር” ባዮች ናቸው። በርግጥ እግዚአብሔር
ያምናልን? ማንን ያምናል? እኔና እናንተ ሁሉን ቻዩ አምላክ በክርስቶስ በፈጸማው የማዳን ሥራ ላይ አምነን
ድነናል። ከእርሱ በላይ የሚምልበት ማንም ስለሌለ በራሱ አልማለምን? እምነት መታመንና ማመንን ገንዘቡ
ያደረገ እንደሆን ነው መጽሀፍ ቅዱሳዊ የሚሆነው። ዝም ብሎ ማመን የኒው ኤጅ ትምህርት ነው። መኪና
መኪና መኪና በል መኪና ታገኛለህ። አጋንንታዊ ነው። ይህ እንቅስቃሴ ነው “በአየሩ ላይ ቃል እንዝራ…ቃላችን
ሀይል አለው…ቃላችን አካባቢው ላይ ተጽ ዕኖ ያመጣል” የሚለውን ፉከራ የሰጡን። መጽሐፍ ቅዱስ ግን
በወንጌላት ላይ በክርስቶስ እግር ሥር ተደፍተን “ቃል ብቻ ተናገር ብላቴናዬም ይፈወሳል” እንድንል
ያደፋፍሩናል። መልሳችን ያለው ሥጋ በሆነው ቃል እንጂ፤ በሥጋ ለባሽ ቃል አይደለም። እነርሱ ግን “እኔ ቃል
እናገራለሁ” እንድንል ያደፋፍሩናል።
(3) በመጨረሻ ሌላው የዚህ እንቅስቃሴ ጽንፈኝነት እግዚአብሔር የሰጣቸው ተስፋ ቃሎች በሙሉ አሁን
በሙሉ ይሆናሉ ባዮች ናቸው። ከላይ እንዳየነው ለነዚህ ሰዎች ገና ሊገለጥ ባለው መዳን ላይ አላተኮሩም። ልክ
በሽሽት ላይ ያለችው ቤተክርስቲያን አሁን የተመረቀውን መዳን ጆሮ ዳባ ብላ ገና የሚመጣውን ብቻ
እንዳጎላች፤ ይህች ደግሞ በአንጻሩ ሊገለጥ ያለውን ታላቅ መዳን ችላ ብላ አይኗን ያተኮረችው አሁን
በሚሆነው ነገር ላይ ነው። እግዚአብሔር በዚህች ምድር ሳለን ሁሉ እንዲኖረን ይፈልጋል የሚለው
መፎክራቸው ይህንኑ ጽንፈኝነታቸውን ያረጋግጥልናል። ለነርሱ ሰው ሁሉ ሐብታም መሆን ይችላል…ይህንም
ከቅዱስ ቃሉ ጥቅስ ይፈልጋሉ….ሁላችን እንፈወሳለን….ሁላችን ጥሩ ትሩ ቤቶችና ሥራዎች እንይዛለን።
ለምሳሌ ከ ዘዳ 28 ወስደው የሚሰብኩት በረከትና መርገም በትንሹ ብሉይ ኪዳናዊ አሊያም አዲስ ኪዳንን
ጨርሶ ያልተረዳ እምነት ነው፡፡ (One of the most respected pentecostal, biblical scholar and assembly of God
ordained minister, Gordon D. Fee, whom I respect so much and from whom learned a lot comments on
this movement that the movement hardly understand the New testament to begin with. I fully concur with
his comment. The problem is that many Christians who follow their teachings do not know at all that this
movement is not a historic Christianity to begin with leave alone, to be biblical and are not acknowledged
as such.)
የነዚህ የሁለቱን አይነት ቤተክርስቲያን ጽንፈኝነት አስወግደን የፊልጵስዩስ አይነቷን እንድንሆን እግዚአብሄር
ይርዳን። ይህም ለክርስቶስ ወንጌል ታማኞችና ሕይወታቸው ከወንጌሉ አንጻር የሚኖሩ እንሆን ዘንድ ነው።
ይህ ይቀረኛል። ይህንን እጠማለሁ። በዚህ ልገሰጽና ልመከር፤ እወዳለሁ። የማንንም አይነት ሞዴል
ቤተክርስቲያን አንድንከተል አልተጠራንም። ወንጌልን የምታንጸባርቅ ቤተክርስቲያን ያቺ የአዲስ ኪዳን
ቤተክርስቲያን ናት
“ይሁን እንጂ፥ መጥቼ ባያችሁ ወይም ብርቅ፥ በአንድ ልብ ስለ ወንጌል ሃይማኖት አብራችሁ እየተጋደላችሁ፥
በአንድ መንፈስ እንድትቆሙ ስለ ኑሮአችሁ እሰማ ዘንድ፥ ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ። በአንድም ነገር
እንኳ በተቃዋሚዎች አትደንግጡ፤ ይህም ለእነርሱ የጥፋት፥ ለእናንተ ግን የመዳን ምልክት ነው፥ ይህም
ከእግዚአብሔር ነው፤ ይህ ስለ ክርስቶስ ተሰጥቶአችኋልና፤ ስለ እርሱ መከራ ደግሞ ልትቀበሉ እንጂ በእርሱ
ልታምኑ ብቻ አይደለም፤ በእኔ ያያችሁት አሁንም በእኔ እንዳለ የምትሰሙት፥ ያው መጋደል ደርሶባችኋልና።
(Php 1:27–30 .)
“አብረንም እየሠራን የእግዚአብሔርን ጸጋ በከንቱ እንዳትቀበሉ ደግሞ እንለምናለን፤ በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም
ቀን ረዳሁህ ይላልና፤ እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው። አገልግሎታችንም
እንዳይነቀፍ በአንዳች ነገር ማሰናከያ ከቶ አንሰጥም። ነገር ግን በሁሉ እንደ እግዚአብሔር አገልጋዮች ራሳችንን
እናማጥናለን፤ በብዙ መጽናት፥ በመከራ፥ በችግር፥ በጭንቀት፥ በመገረፍ፥ በወኅኒ፥ በሁከት፥ በድካም፥ እንቅልፍ
በማጣት፥ በመጦም፥ በንጽህና፥ በእውቀት፥ በትዕግሥት፥ በቸርነት፥ በመንፈስ ቅዱስ፥ ግብዝነት በሌለው ፍቅር፥
በእውነት ቃል፥ በእግዚአብሔር ኃይል፥ ለቀኝና ለግራ በሚሆን በጽድቅ የጦር ዕቃ፥ በክብርና በውርደት፥ በክፉ ወሬና
በመልካም ወሬ ራሳችንን እናማጥናለን፤ አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን፤ ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፤ የምንሞት
ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፤ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፤ ኀዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል፤ ድሆች ስንሆን
ብዙዎችን ባለ ጠጎች እናደርጋለን፤ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው” (2 ቆሮ 6:1–10)
“ነገር ግን የኃይሉ ታላቅነት ከእግዚአብሔር እንጂ ከእኛ እንዳይሆን ይህ መዝገብ በሸክላ ዕቃ ውስጥ አለን፤ በሁሉ
እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም፤ እንሰደዳለን እንጂ አንጣልም፤ እንወድቃለን እንጂ
አንጠፋም፤ የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ ሁልጊዜ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን
እንዞራለን። የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሚሞት ሥጋችን ይገለጥ ዘንድ እኛ ሕያዋን የሆንን ከኢየሱስ የተነሣ ዘወትር
ለሞት አልፈን እንሰጣለንና። ስለዚህ ሞቱ በእኛ ሕይወቱም በእናንተ ይሠራል። ነገር ግን። አመንሁ ስለዚህም ተናገርሁ
ተብሎ እንደ ተጻፈ ያው አንዱ የእምነት መንፈስ ስላለን፥ እኛ ደግሞ እናምናለን ስለዚህም እንናገራለን፤ ጌታን
ኢየሱስን ያስነሣው እኛን ደግሞ ከኢየሱስ ጋር እንዲያስነሣን ከእናንተም ጋር እንዲያቀርበን እናውቃለንና። በብዙዎች
በኩል የተትረፈረፈው ጸጋ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋናን ያበዛ ዘንድ፥ ሁሉ ስለ እናንተ ነውና። ስለዚህም አንታክትም፥
ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል። የማይታየውን እንጂ
የሚታየውን ባንመለከት፥ ቀላል የሆነ የጊዜው መከራችን የክብርን የዘላለም ብዛት ከሁሉ መጠን ይልቅ ያደርግልናልና፤
የሚታየው የጊዜው ነውና፥ የማይታየው ግን የዘላለም ነው” (2 ቆሮ 4:7–18)
ይህንን ስል አንድ ነገር ግን ለአንባቢዬ ግልጽ እንዲሆን እወዳለሁ። አሁን በዚህች ምድር ስንኖር የእግዚአብሔር
መለኮታዊ ሐይል አይሰራም እያልኩ አለመሆኔን እንድታስተውሉ ነው። ጌታ በድንቅ በዓለማችን በሥራ ላይ
ነው። በመንፈሳዊ ሥጦታዎች ሙሉ በሙሉ መሥራት አምናለሁ! በርግጥ መንፈስ ቅዱስ የሰጠንን ሥጦታ
ከማርገብገብ ወደ ኋላ እንድንል ለአፍታ አልወድም፤ ከማንም እነዚህ ሥጦታዎች ከመፋፋም እንዲቀዘቅዝ
ምኞቴም አይደለም። ራሴን እንደ ካሪዝማቲክ አማኝ እቆጥራለሁና (ካሪዝማታ – በአዲስ ኪዳን ግሪክ ጸጋ
ከሚለው ቃል የተወረሰ ሲሆን፤ የፕኑማቲኳን ትርጉሙን ከላይ ጠቅሼያለሁ)። ጌታ በፈውስ ስጦታ አሁን
ይሠራል፤ በትንቢት ሥጦታ ምሪትን ይሠጣል (ምሪት የሚለው ይሰመርልኝ)፤ አንዱ መንፈስ የጥበብን ቃል፤
የእውቀትን ቃል፤ ታምራት ማድረግን፤ መናፍስት መለየትን፤ የጸሎት ልሳናትን መንፈስ ቅዱስ እንደፈቀደ
ለአንዳንዶቻችን ያድለናል። (የማይተረጎመው የጸሎት-ልሳን ከሌሎች ሥጦታዎች ለየት የሚያደርገው፤
ዓላማው ጉባኤን ለማነጽ ስላልሆነ፤ በጉባኤ መካከል ያለአንዳች ገደብ አማኙ እንዲጠቀመው በግልጽ መጽሐፍ
ቅዱስ ይከለክላል (1 ቆሮ 14:4-28 – የሚተረጉም ባይኖር ግን በማኅበር መካከል ዝም ይበልና ለራሱና
ለእግዚአብሔር ይናገር)። በልሳናት የሚጸልይ ራሱን ብቻ ያንጻልና…ትንቢት የሚናገር ወይም አምስት
ትርጉም የሚሰጥ ቃላት በጉባኤ የሚናገር ግን አካሉን ያንጻል። እናስታውስ ስጦታ በአካል ውስጥ የራስ ጥቅም
መሙያ አይደለም (ጴጥ 4፡ 10-11)) መንፈስ ቅዱስ በመካከላችን ወልድን እንድንመስል በሐይል በሥራ ላይ ነው።
ሆኖም ግን እነዚህ ስጦታዎች አማኙ ሲፈልግ መዘዝ እያደረገ ዘራፍ የሚልበት አለመሆኑንና አማኙ መከራንና
መስቀሉን ከመሸከም ሕይወት፤ እንዲሁም በተለያዩ መከራዎችና ሥቃዮች እንዳያልፍ መታወቂያ ካርድ
አይደለም። ሐዋርያው ጳውሎስ በታላቅ ሕመም እንደነበር ለገላትያ ቤተክርስቲያን ነግሮአቸው እንደነበር
ለናሙና ያህል ማየት እንችላለን። መንፈሳዊ ሥጦታዎች መንፈስ ቅዱስ በመካከላችን እርስ በርስ
እንድንተናነጽና እንድናድግ የሚጠቀምበት መሳሪያዎች ናቸው እንጂ የቅዱሳት መጻሕፍት ምትክ አይደሉም።
ለምሳሌ ያህል በክርስቶስ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ያልተገለጠ መለኮታዊ ባህርይ ተገለጠልኝ የሚል ነብይ
ቢነሳ ያንን የአዲስ ኪዳን ነብይ ጥሪ አለመሆኑን አበክረን መናገር ይኖርብናል። የመለኮት ሙላት ሁሉ በክርስቶስ
ተገልጧልና; ዛሬ በክርስቶስ ያልተገለጠ ማንነት ተገለጠ ቢል፤ ወይ እግዚአብሔር አይለወጥም የሚለውን ቀደን
መጣል አለብን አሊያም ኢየሱስ ጌታ ነው የሚለውን መፎክር መተው አለብን። ምክኒያቱም እግዚአብሔርን
ያለክርስቶስ ማወቅ፤ የክርስቶስን ሙላት መካድ ነውና። ሆኖም ግን በአዲስ ኪዳን ገጾች የነብያትን አገግሎት
ከሐዋርያት-ሥራ እንደዚሁም ከሌሎች ክፍሎች ሥንቃኝ፤ የነብይ ቃል ለአማኖች ምሪትን፤ ለቤተክርስቲያን
አቅጣጫን ለመስጠት እንጂ ከዚህ በፊት ያልተገለጠ ትምህርትና እግዚአብሔር ማን እንደሆነ መተረኪያ
አልነበረም;። የአጋቦስ ትንቢት፤ ለአንጾኪያ ቤተክርስቲያን እርዳታ ትሰበስብና በኢየስሩሳሌም ላሉት ቅዱሳን
ርዳት እንዲልኩ ምሪትን ለመስጠት ነበር። ለሀዋርያው፡ጳውሎስ የመጡለት ትንቢቶችና ራዕዮች ሁሉም
ለአሕዛብ ሚሽንና እስከ ሮም ድረስ ላለው ክርስቶስን የመመስከር ተግዳሮቱ ምሪት እንጂ ትንቢቶች አዳዲስ
አስተምሕሮት መቀበያ አልነበረም። የቆላስያስ ቤተክርስቲያን የገባችበት አደጋ፤ ራዕይ አየሁና መልአክ
ተገለጠልን እያሉ አማኞችን በክርስቶስ ከመጣው-መገለጥና ለመዳን እንዲሁም ለመለወጥ የክርስቶስን በነጠላ
በቂነት ጥያቄ ውስጥ በማስገባት አይናቸውን ዘወር ስላደረጉ በታላቅ ግሳጼ ሲጽፍላቸው፤
መልዕክቱ ግልጽ ነው፤ መንፈሳዊ ሥጦታ ማለት በክርስቶስ ከመጣው የወንጌል ሙላት አይኖችን ዘወር
የሚያደርግ ከሆነ፤ ይህ አዲስ ኪዳን የማያውቀው ስጦታ ነው። እንዲህ አይነት አቋም ቤተክርስቲያን ካልያዘች
ወንጌል፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ የማናውቀው ገጽታ ይዞ እናገኛለን። የሞርሞን መስራች ለምን ይመስላችኋል
የሳተው? የጆሴፍ ስሚዝ መፎክር “ወደ ጥንታዊቱ የአዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን እንመለስ” ባይ ነበር። በሞተ
ጊዜ ትምሕርተ እግዚአብሄርን፤ ትምሕርተ ክርስቶስን፤ ትምሕርተ ሥነ-ፍጥረትን፤ ትምሕርተ-
ቤተክርስቲያንን፤ የቤተሰብ መዋቅር…በሙሉ አዲስ በተቀበለው መገለጦችና ራዕያት ከመበራረዛቸው የተነሳ
የሞርሞን ኢየሱስ የኛ ጌታ አይደለም። ተቀበልሁ ብሎ የጻፋቸውን መገለጦች አትመው አሁን እርሱ ታላቅ
ነብይ በመባል፤ ጹሑፉም ከመጽሐፍ ቅዱስ በላይ ሥልጣን ያለው ሆኗል። ታድያ እኛስ መንፈሳዊ ሥጦታዎች
በምን ረገድ እንደሚሰሩና ምንነታቸውን ካልተረዳን ሞርሞን የወደቁበት ሥህተት የእኛ የማይሆንበት ምን
ምክኒያት አለ? እኛስ ሰዎች አይደለንምን? ከወዴት እንደወደቅን ማሰብስ መንፈሳዊነት አይደለምን? አሠራሩ
ያው ነውና። በተጨማሪ ከዚህ ቀደም በትምህርቴ ላይ እንዳሰፈርሁት መንፈሳዊ ሥጦታዎች አሁን ክርስቶስ
ሃይላትንና ሥልጣናትን ድል አድርጎ በአባቱ ቀኝ ድል አድራጊ ሆኖ መቀመጡን፤ መንግሥቱ በሓይል መመረቋን፤
ማወጂያ መሳሪያ መሆኑን ከኤፌ 4 ላይ አይተናል “ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ
ይላል። እርሱም አንዳንዶቹን…አድርጎ ሠጠ“
ስለዚህ ትንቢት ተናጋሪው ሲናገር፤ ትንቢቱ በምሪት መስጠት ላይ ይወሰን እንጂ በትንቢት በክርስቶስ
የተሰጠውን አስተርዕዮ አይጋፋ። በመንፈስ ቅዱስ የጥበብ ቃል የሚናገር፤ በበሰሉት መካከል የምንናገረው
ጥበብ ከሰማይ ዱብ ያለ ሳይሆን አግዚአብሄር አስቀድሞ ለክብራችን የወሰነውን የክርስቶስን ሚስጢር ምን
እንደሆነ አስቀድሞ ይማር። በፈውስ ሥጦታ የሚያገለግል ደግሞ አካሉን ያገልግል፤ በመካከላችን በህመም
ለሚማቅቁ መለኮታዊ ጉብኝት ያግኙ እንጂ ይህንን ስጦታ አስተማሪ ለመሆን በመሞከር አያዳፍን።
ምክኒያቱም አስተማሪዎች ከሁሉ በላይ በልዩ አለንጋ ይገረፋሉና ነው። አስተማሪ ከመሆን በፊት ጥሩ ተማሪ/
ደ/መዝሙር መሆን ምርጫ የለወም። ኢየሱስ ለሦስት ዓመት ተኩል ያሕል ደቀመዛሙርቱን ለሊት-ተቀን
አስተምሮ፤ ከዚያም ለ 40 ቀናት እያለፈ እያለፈ ከትንሳኤው በኋላ ተገልጦ ይልቅ ካስተማራቸው፤ እኔ ማን
ነኝ ታድያ ሳልማር ለማስተማር መሞከር ያለብኝ? ትውስ አይላችሁም ፈሪሳውያን “እነዚህ ሳይማሩ
መጽሐፍትን እንዴት አወቁ?”…ጥያቄያቸውንም ራሳቸው በራሳችው ሲመልሱ “ከኢየሱስም ጋር እንደ ነበሩ
አወቁአቸው!” ብለዋል። ሳይማሩ ማለታቸው ከፈሪሳውያን ትምህርት ቤት በዶክትሬት ያልተመረቁ
ማለታቸው ሲሆን ከኢየሱስ ጋር መሆናቸውን መጦቆማቸው ደግሞ፤ ያ አሳች ብለን የሰቀልነው እርሱ
አስተምሯቸዋልና ነው። ምንም እንኳ ከፈሪሳውያን ትምሕርት ቤት ባይመረቁም፤ በክርስቶስ እውነተኛው
መምህር እግር ሥር ግን ለሶስት ዓመት ሠልጥነው ተመርቀዋል። በአንጻሩ ደግሞ ቅዱስ ቃሉን ለማስተማር ጸጋ
የሰጠን አንዳንዶች ደግሞ ትንቢትና የመገለጥን ቃል ለመናገር ያልተሰጠንን ለመውሰድ ስንሞክር ከቅዱስ ቃሉ
እንዳንወጣ በተሰጠን እናገልግል። አሁንም አላማው ሌላውን ለማገልገል እንጂ ታዋቂ ለመሆን አይደለም።
ሆኖም ግን ይህ ሁሉ ሥርዓት ይዞ ቅደም ተከተሉን ጠብቆ መሰማራት ይችል ዘንድ በክርስቶስ የመጣው
በቅዱሳት መሳሕፍት ጠጠርዞ የቀረበልን የወንጌል አስተርዕዮ በመካከላችን አዛዥ ይሁን!
ስለዚህ እነዚህን ጽንፈኝነቶች አስወግደን በመስቀልና በዙፋን መካከል ቆመን እርስ በርሳችን እየተመካከርን፤ እየተናነጽን፤
እየተገሳሰስን የምንሰብከው ክርስቶስን ይሁን (ቆላ 1፡ 28-29)። በዚህ ዘመን ያለች በቤተክርስቲያን ሊሰበክላት
የሚያስፈልገው “ፍጻሜ ገንዘቧ” መሆኑን ነው።፡በርግጥ አይናችን ለዘላለማዊ ርስታችን ታውሯልና ሐዋርያው ለኤፌሶን
የጸለየላት ያ ታላቅ ጸሎት ለእኛም ያስፈልገናል “ይህም የልባችሁ ዓይኖች ሲበሩ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንዲሆን
በቅዱሳንም ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለ ጠግነት ምን እንዲሆን ለምናምን ከሁሉ የሚበልጥ የኃይሉ ታላቅነት ምን
እንዲሆን ታውቁ ዘንድ ነው” ብድራታችንን ትኩር ብለን ማየት ተስኖናል። ተስፋችን በሚገለጠው ክብር ላይ ሳይሆን
ተስፋችን አሁን እግዚአብሄር በሚያደርገው ጊዜያዊ ትርፍ ነገር ላይ አርፎብናል። በእርግጥ ከላይ የጠቀስኳቸውን ሁሉ
ለማስተካከል ታጥቀው የተነሱትን እያንጓጠጥን ‘የሥህተት አስተማሪ’ የሚል ስያሜ ብንሰጣቸውም፤ እውነት ግን
በልጆቿዋ ትጸድቃለች። ሆኖም ግን ጴጥሮስስ እንዲህ አላለምን “ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና በመጠን
ኖራችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ“ (1 Pe 1:13 ) ኧረ የቤተክርስቲያን
የ 2000 ዓመት ቆይታዋንም መመልከት በራሳችን ዓይን ጠቢባን እንዳንሆን ትህትናን ያላብሰናል…ታሪክም ይዳኛልና!
“ብዙዎች ለክርስቶስ መስቀል ጠላቶቹ ሆነው ይመላለሳሉና፤ ብዙ ጊዜ ስለ እነርሱ አልኋችሁ፥ አሁንም እንኳ
እያለቀስሁ እላለሁ። መጨረሻቸው ጥፋት ነው፥ ሆዳቸው አምላካቸው ነው፥ ክብራቸው በነውራቸው ነው፥
አሳባቸው ምድራዊ ነው። እኛ አገራችን በሰማይ ነውና፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም
ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤ እርሱም ሁሉን እንኳ ለራሱ ሊያስገዛ እንደሚችልበት አሠራር፥
ክቡር ሥጋውን እንዲመስል የተዋረደውን ሥጋችንን ይለውጣል” (2 Peter 3:9–14 )”ለአንዳንዶች የሚዘገይ
እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም
እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል። የጌታው ቀን ግን እንደ ሌባ ሆኖ ይመጣል፤ በዚያም ቀን ሰማያት
በታላቅ ድምፅ ያልፋሉ፥ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይቀልጣል፥ ምድርም በእርስዋም ላይ የተደረገው
ሁሉ ይቃጠላል። ይህ ሁሉ እንዲህ የሚቀልጥ ከሆነ፥ የእግዚአብሔርን ቀን መምጣት እየጠበቃችሁና
እያስቸኰላችሁ፥ በቅዱስ ኑሮ እግዚአብሔርንም በመምሰል እንደ ምን ልትሆኑ ይገባችኋል? ስለዚያ ቀን
ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይፈታል፤ ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን
አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን። ስለዚህ፥ ወዳጆች ሆይ፥ ይህን እየጠበቃችሁ ያለ
ነውርና ያለ ነቀፋ ሆናችሁ በሰላም በእርሱ እንድትገኙ ትጉ” (2 Peter 3:9–14 )