You are on page 1of 8

በኢትዮጵያ ፌዴራላ ዊ ዲሞክራሲያዊ ሪ ፐብሊክ

የ ፌዴራል ጠቅላ ይ ፍር ድ ቤት
ሰበር ሰሚችሎት

የሠ/መ/ቁጥር 208197

መጋቢት 26 ቀን 2014 ዓ/ም

ዳኞች ፡-ብርሃኑ አመነዉ


ተሾመ ሽፈራዉ
ሀብታሙ እርቅይሁን
ብርሃኑ መንግሥቱ
ነጻነት ተገኝ

አመልካች ፡- ዓለማየሁ አባተ(ዶ/ር)፡- ጠበቃ ዘፋኒያህ ዓለሙ ቀረቡ


ተጠሪ ፡- ወ/ሮ መፅሄት ዓይነኩሉ፡- አልቀረቡም
መዝገቡ ተመርምሮ ከዚህ የሚከተለዉ የፍርድ ዉሳኔ ተሰጥቷል፡፡

ፍ ር ድ
ጉዳዩ አንደኛዉ ተጋቢ የፈጸሙን የብድር ዉል ሌላኛዉ ተጋቢ አዉቋል ሊባል የሚችልበትን አግባብ
የሚመለከት ነዉ፡፡ ተጠሪ በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአመልካች እና በስር 2ኛ ተከሳሽ ላይ
በመሰረቱት ክስ ከአመልካች ጋር ተጋብተዉ እየኖሩ ቆይተዉ በቀን 03/06/2009ዓ/ም በፌዴራል መጀመሪያ
ደረጃ ፍርድ ቤት በተሰጠ ዉሳኔ ጋብቻዉ ፈርሷል፡፡ አመልካች በጋራ ንብረት ክፍፍል ክርክር መልሳቸው
ላይ በአማራ ክልል ባህር ዳር ከተማ በካርታ ቁጥር 32394/97 በአመልካች ስም ተመዝግቦ የሚገኘው ቤት
የተሰራው ከስር 2ኛ ተከሳሽ በተገኘ ብድር እና እዳውም አልተከፈለም በማለት መልስ የሰጠ ቢሆንም የብድር
ውሉ ተጠሪ ሳያውቁት የተደረገ ነው፡፡ በቤተሰብ ሕግ አንቀፅ 68(1/መ) መሰረት ከብር 500 በላይ ለማበደርም
ሆነ ለመበደር ተጋቢዎች የጋራ ስምምነት ያስፈልጋል፡፡ ተጠሪ የብድር ውል ስለመኖሩ አላውቅም፡፡ በብድር
ተገኘ የተባለውም ገንዘብም ለትዳር ጥቅም አልዋለም፡፡ ውሉ ከቅን ልቦና ውጪ ተጠሪን ለመጉዳት የተደረገ
በመሆኑ የብድር ውሉ ሊፈርስ ይገባል እንዲሁም የብድር ውሉ ተጠሪ ላይ የሚያመጣው ግዴታ የለም
ተብሎ ይወሰንልኝ በማለት ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
አመልካች የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ በማስቀደም ለክሱ በሰጡት መልስ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን የመዳኘት
ሥልጣን የለዉም፡፡ተጠሪ ክስ የመሰረቱበት የብድር ዉል ስለመኖሩ ስለሚያዉቁ ዉሉ መኖሩን ካወቁ
ከስድስት ወር በኋላ ያቀረቡት ክስ በመሆኑ ክስ የማቅረብ መብታቸዉ በይርጋ ቀሪ የሆነ ነዉ በማለት
ተቃዉመዋል፡፡ፍሬ ነገሩን በተመለከተ ባህርዳር ከተማ ያለ ቤት ስሰራ የገንዘብ ችግር ገጥሞኝ ተጠሪ ብድር
ማግኘት ባለመቻሏ የብድር ገንዘብ ፈልገን እኔ እንድበደር ተነጋግረን ተበድሬ ቤቱን ሰርቻለሁ፡፡በዚህ አግባብ
የተገኘዉ ገንዘብ በባህርዳር ከተማ ያለዉን መኖሪያ ቤት መስሪያ መዋሉንና የብድር ዉል መኖሩን ተጠሪ
ታዉቃለች፡፡ከተበደርነዉ ገንዘብ ብር 110,000.00 በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኩል ከፍዬ ብር 340,000.00
እንደሚቀር ተጠሪ ያዉቃሉ፡፡ስለሆነም ተጠሪ የብድር ዉሉ እሷን ለመጉዳት በማስመሰል እንደተደረገ
አድርገዉ ዉሉ እንዲፈርስ ያቀረቡት ክስ በማስረጃ ያልተደገፈ እና የሕግ መሰረት የሌለዉ ስለሆነ ዉድቅ
ይደረግልኝ በማለት ተከራክረዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ በመ/ቁጥር 63059 ላይ በቀን 10/03/2011ዓ/ም የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ አስመልክቶ


በሰጠዉ ብይን ይርጋን በሚመለከት የቀረበዉን መቃወሚያ በተመለከተ ተጠሪ ብድሩ መኖሩን ካወቀች 6
ወር አልፏል የሚለዉን አመልካች ባቀረቡት ማስረጃ በተሻለ ሁኔታ አስረድተዋል፡፡ሆኖም የብድር ዉል
የተደረገዉ በቀን 07/10/2007ዓ/ም ሲሆን ተጠሪ ክስ የመሰረቱት ደግሞ የብድር ዉል ግዴታ ከተገባ ሁለት
አመት ሳይሞላዉ በቀን 28/09/2009ዓ/ም ነዉ፡፡በተሻሻለዉ የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992
አንቀጽ 69/2 ስር በተደነገገዉ የሁለት አመት አማራጭ ይርጋ መሰረት የተጠሪ ክስ የማቅረብ መብት
በይርጋ ቀሪ አልሆነም በሚል በዚህ ረገድ የቀረበዉን መቃወሚያ ዉድቅ በማድረግ ወስኗል፡፡በመቀጠልም
ፍሬ ነገሩን በተመለከተ ምስክሮች ሰምቶና መርምሮ በቀን 17/04/2012ዓ/ም በሰጠዉ ዉሳኔ ተጠሪ በብድሩ
ላይ አልፈረሙም፡፡አመልካች ባቀረቧቸዉ ምስክሮች ብድር ስለመኖሩ እንደተነገራቸዉ ከመመስከራቸዉ ዉጪ
ስለብድሩ እዉቅና ያላቸዉ ስለመሆኑ አላስረዱም፡፡በሌላ በኩል ተጠሪ በምስክርነት ቃላቸዉ ቤቱ የተሰራዉ
ከአመልካች ጋር ባፈሩት የጋራ ገንዘብ መሆኑን አስረድተዋል፡፡በተጨማሪም መንግስታዊ ባልሆነ ድርጅት
እየሰሩ ደመወዝ በወር 80,000.00 ሲከፈላቸዉ እንደነበር ገልጸዉ ቤቱ የተሰራዉ በዚህ ገንዘብ ጭምር
መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የአመልካች ምስክሮች ብድር ስለመኖሩም አመልካች ነግሮናል በማለት ዉሉ
ሲፈጸምም ሆነ አመልካች ብሩን ሲበደሩ እንዳላዩ አስረድተዋል፡፡በመሆኑም አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀጽ
71/ሐ በክሱ ላይ የተደረገዉ ዉል ተጠሪ የማያዉቁትና ገንዘቡም ለትዳር ጥቅም ያልዋለ በመሆኑ
በአመልካችና በስር 2ኛ ተከሳሽ መካከል የተደረገዉ የብድር ዉል በአንቀጽ 69/1 መሰረት ፈርሷል ሲል
ወስኗል፡፡
አመልካች በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱ
በመ/ቁጥር 251127 ላይ ግራ ቀኙን አከራክሮ በቀን 06/06/2013ዓ/ም በሰጠዉ ውሳኔ የአመልካች ምስክሮች
ቃል ላይ እንደተመለከተዉ አመልካች ብድሩን እንደወሰዱ እንደነገራቸዉ እንጂ በእርግጥ የብድር ዉሉ
መኖሩን በግልጽ አላስረዱም፡፡በመሆኑም በቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 69/2 ስር የተመለከተዉን የይርጋ ጥያቄን

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
ለማንሳት ተጠሪ ስለብድሩ እዉቅና እንዳላቸዉ በግልጽ ባልተረጋገጠበት ሁኔታ በ6 ወር ዉስጥ ክሱ
አልቀረበም ብሎ በይርጋ ዉድቅ ማድረግ ተገቢ ስለማይሆን የስር ፍርድ ቤት ከዚህ አንጻር የሰጠዉ ዉሳኔ
ተገቢ ነዉ፡፡እንዲሁም ባህርዳር ከተማ ዉስጥ ያላቸዉ ቤት የተሰራዉ ተጠሪ ገንዘብ እየላኩ በጋራ ገንዘባቸዉ
እንደሆነ ተጠሪ አስረድተዋል፡፡አመልካች ደግሞ ቤቱ የተሰራዉ በግራ ቀኙ የጋራ ገንዘብ እንዳልሆነ
በማስተባበል አላስረዱም፡፡በመሆኑም የብድር ገንዘቡ ለትዳር ጥቅም አልዋለም በማለት የስር ፍርድ ቤት
የብድር ዉሉ እንዲፈርስ የሰጠዉ ዉሳኔ ተገቢ ነዉ ሲል አጽንቷል፡፡

አመልካች በቀን 23/09/2013 ዓ/ም የተጻፈ የሰበር አቤቱታ ያቀረቡትም ከላይ በተመለከተዉ መሰረት በተሰጠ
ዉሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ተፈጽሟል በሚል ሲሆን የአቤቱታቸዉ ይዘት በአጭሩ፡- የብድር ውል
ግዴታ የተገባው በ07/10/2007 ዓ/ም ነዉ፡፡ ተጠሪ በቀን 28/09/2009ዓ/ም ክስ የመሰረቱት ብድሩ መኖሩን
ካወቁ ከስድስት ወር በኋላ መሆኑን አመልካች ከተጠሪ የተሻለ ማስረጃ በማቅረብ አስረድቻለሁ፡፡ የስር
የፌዴራል መጀመሪያ ፍርድ ቤት በቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 69/2 ስር የተደነገገዉ የ6 ወር ይርጋ ራሱን ችሎ
የቆመ ይርጋ እንጅ ከሁለት አመት ፍጹማዊ ይርጋ ጋር ግንኙነት የሌለዉ ሆኖ እያለ ጉዳዩን ከሁለት አመት
ይርጋ አንጻር በማየት የተጠሪ ክስ የማቅረብ መብት በይርጋ አልታገደም በሚል አለአግባብ የአመልካችን
መቃወሚያ ዉድቅ አድርጓል፡፡ይግባኝ ሰሚዉ ፍርድ ቤትም የስር ፍርድ ቤትን ስህተት ማረም ሲገባዉ
አለአግባብ ማስረጃ ምዘና ዉስጥ በመግባት ብድር ዉል ግዴታ መገባቱን ተጠሪ ልታዉቅ አትችልም የሚል
ድምዳሜ ላይ በመድረስ የሰጠዉ ዉሳኔ የክርክር አመራር በተመለከተ በሰ/መ/ቁጥር 36979 የተሰጠዉን
የሕግ ትርጉም የሚቀረን ነዉ፡፡በብድር ዉሉ ላይ በግለጽ ገንዘቡ በብድር የተወሰደዉ በባህር ዳር ከተማ
ለምናስገነባዉ ቤት ለማዋል እንደሆነ ተመልክቷል፡፡በዚህ አግባብ በብድር ዉሉ ላይ ተመልክቶ እያለ
በፍ/ብ/ሕግ ቁጥር 2006/1 ስር የተደነገገዉን በሚቃረን አኳኋን በምስክሮች ለማረጋገጥ የተደረገዉ የክርክር
አመራር ስህተት ቢሆንም አመልካች በምስክሮች ገንዘቡ ለትዳር ጥቅም እንደዋለ አስረድቻለሁ፡፡ተጠሪ ግን
ገንዘብ ለትዳር ጥቅም አለመዋሉን በማስረጃ ማስረዳት አልቻሉም፡፡የስር ፍርድ ቤቶች ተጠሪ የብድር ዉሉ
መኖሩን አታዉቅም የሚል ድምዳሜ ላይ የደረሱት በማስረጃ የተረጋገጡትን ፍሬ ነገሮች ወደጎን በመተዉ
በመሆኑ ገንዘቡ ለጋራ ጥቅም ዉሏል ተብሎ እንዲወስንላቸዉ እና የተጠሪ ክስ የማቅረብ መብት በይርጋ ቀሪ
የሆነ ነዉ ተብሎ የስር ፍርድ ቤቶች ዉሳኔ በመጠየቅ አቤቱታቸውን አቅርበዋል፡፡

የሰበር አጣሪ ችሎት አቤቱታውን መርምሮ አመልካች ከስር 2ኛ ተከሳሽ ጋር ያደረጉት የገንዘብ ብድር ውል
መኖሩን ተጠሪ ካወቁ ከስድስት ወር በኋላ የብድር ውሉ እንዲፈርስ ክስ እንዳቀረቡ የስር ፍርድ ቤት በቀን
10/03/2011 ዓ/ም በሰጠው ብይን ላይ በገለፀበት ሁኔታ አመልካች በስር ፍርድ ቤት ያቀረቡት የይርጋ
መቃወሚያ ውድቅ ተደረገበትን አግባብነት ከቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀፅ 69/2 ጋር
በማገናዘብ ለመመርመር ትዕዛዝ በመስጠቱ ተጠሪ በቀን 07/03/2014 ዓ/ም የተፃፈ መልስ አቅርበዋል፡፡

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
የቀረበውን የይርጋ ክርክር በተመለከተ ግራ ቀኙ በነበራቸው የባልና ሚስት ንብረት ክፍፍል ክስ ወቅት ለዚህ
ክስ መነሻ የሆነውን የብድር ውል አመልካች የባልና የሚስት የጋራ እዳ መሆኑ ተረጋግጦ እንዲወሰንላቸው
ክርክሩን ሲመለከት ለነበረው የስር ፍርድ ቤት በሚያዚያ 18/2009 ዓ/ም አቅርበው ተጠሪም የጋራ እዳ
እንዲባል የቀረበው የብድር ውል ስለመደረጉ የሚያውቁት ነገር ባለመኖሩ ምክንያት ሕጉ በሚፈቅደው
መሰረት የብድር ውል መደረጉን ባወቁ በስድስት ወር ውስጥ ውሉ እንዲፈርስ በመጠየቅ ክስ አቅርበዋል፡፡
የስር ፍርድ ቤቶች ማስረጃ መዝነዉ የብድር ዉል መደረጉን እንደማላዉቅ ድምዳሜ ላይ የደረሰ ስለሆነ
በሰበር ሰሚ ችሎቱ የሚታይ አይደለም፡፡እንዲሁም የብድር ዉል መደረጉን ዉሉ በተደረገ በስድስት ወራት
ዉስጥ አዉቅ እንደነበር አመልካች አላረጋገጡም፡፡ የገንዘብ ብድሩ ለትዳር ጥቅም አለመዋሉ በስር ፍርድ ቤት
በቀረቡት ማስረጃዎች ተረጋግጠዋል፡፡እንዲሁም በቤተሰብ ጉዳይ ችሎት በብድር የተወሰደዉ ገንዘብ የጋራ እዳ
እንዲባልላቸዉ ጠይቀዉ የነበረ ቢሆንም ፍርድ ቤቱ እዳዉ የጋራ እዳ ነዉ ተብሎ የተሰጠ ዉሳኔ የለም፡፡
በዚህ አግባብ ብድሩ ለትዳር ጥቅም የዋለው ነው ተብሎ እንዲወሰንላቸው የጠየቁት ቀባይነት ባላገኘበት
ተጠሪ የብድር ዉሉ እንዲፈርስ ዳኝነት በጠየቁበት መዝገብ ላይ ብድሩ ለትዳር ጥቅም የዋለ ነዉ ተብሎ
እንዲወሰንላቸዉ ያቀረቡት ክርክር ተቀባይነት የለውም በማለት ተከራክሯል፡፡ አመልካችም በቀን
01/04/2014 ዓ/ም የተጻፈ የመልስ መልስ በማቅረብ ተከራክረዋል፡፡

ከዚህ በላይ አጠር ባለመልኩ የተመለከተዉ የግራ ቀኙ ክርክርና በስር ፍርድ ቤቶች የተሰጡ ዉሳኔዎች
ይዘት ሲሆን እኛም የሰበር አጣሪ ችሎት የያዘዉን ማስቀረቢያ ጭብጥ ከግምት በማስገባት በስር ፍርድ
ቤቶች በተሰጠ ዉሳኔ የተፈጸመ መሰረታዊ የሕግ ስህተት መኖር አለመኖሩን አግባብነት ካለዉ ሕግ ጋር
በማገናዘብ እንደሚከተለዉ መርምረናል፡፡

እንደመረመርነዉም በተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀጽ 68/መ ስር


እንደተደነገገዉ በሌላ ሕግ በተለየ ሁኔታ ካልተደነገገ በስተቀር ከብር 500.00(አምስት መቶ ብር) በላይ
ለመበደር ወይም ለማበደር ወይም ለሌላ ሰዉ ዋስ ለመሆን የተጋቢዎቹ ስምምነት ያስፈልጋል፡፡ይህንኑ የሕግ
ግዴታ ባለማክበር አንዱ ተጋቢ የውል ግዴታ ገብቶ የተገኘ እንደሆነም ሌላኛው ተጋቢ ግዴታው እንዲፈርስ
ክስ የማቅረብ መብት ያለው መሆኑን በሕጉ አንቀጽ 69/1 ላይ ተመለክቷል፡፡ የክስ ማቅረቢያ ጊዜም
ግዴታው መገባቱን ከአወቀበት ቀን ጀምሮ በ6 ወር ውስጥ መሆን እንዳለበት ወይም በሌላ በማንናቸውም
ሁኔታ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ያልቀረበ ከሆነ በይርጋ የሚታገድ ስለመሆኑ በአንቀጽ 6 በንዑስ አንቀጽ
2 ላይ ተደንግጎ ይገኛል፡፡በዚህ አንቀጽ ላይ የተመለከተዉ ሁለቱም አይነት የይርጋ ጊዜ ተፈጻሚነቱ
ያለአንደኛዉ ተጋቢ ተሳትፎ በሌላኛዉ ተጋቢ የተገባ ግዴታ እንዲፈርስ በስምምነቱ ተካፋይ ያልሆነዉ ተጋቢ
ሲጠይቅ ነዉ፡፡እንዲሁም በዚህ ድንጋጌ ላይ የተመለከተዉ ሁለት አይነት የይርጋ ጊዜ ሲሆን አንደኛዉ
የስድስት ወር የይርጋ ጊዜ ተፈጻሚነቱ በሕጉ ከአንቀጽ 68(ሀ-መ) ስር የተጋቢዎቹ የጋራ ስምምነት
ያስፈልጋል ተብለዉ በተዘረዘሩት ጉዳዮች ላይ አንዳኛው ተጋቢ የሌላኛው ተጋቢ ስምምነት ሳይኖር የውል
ግዴታ መገባቱን ያወቀ ተጋቢ ዉሉ እንዲፈርስ ክስ ማቅረብ ያለበትን ጊዜ የሚመለከት ነዉ፡፡ ሁለተኛዉ

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
በዚሁ ድንጋጌ የተመለከተዉ የሁለት ዓመት የይርጋ ጊዜ ደግሞ በማንኛዉም ሌላ ምክንያት በሕጉ ከአንቀጽ
68(ሀ-መ) ስር የተጋቢዎቹ የጋራ ስምምነት ያስፈልጋል ተብለዉ በተዘረዘሩት ጉዳዮች ላይ አንዳኛው ተጋቢ
የሌላኛው ተጋቢ ስምምነት ሳይኖር የውል ግዴታ መገባቱን በመቃወም ዉሉ እንዲፈርስ ክስ የሚያቀርብበትን
ፍጹማዊ(absolute) የሆነ የይርጋ ጊዜ የሚመለከት ነዉ፡፡በዚህ አግባብ የይርጋ ጊዜያትና ለእያንዳንዱ የይርጋ
ጊዜ መሰረት ሊሆኑ የሚችሉ አመላካች ምክንያቶች ተለይቶ በፍ/ብ/ሕግ ቁጥር 1845 ስር ከተመለከተዉ
በተለየ ሁኔታ የተደነገገበት ምክንያት የተጋቢዎችን ልዩ ሁኔታ ታሳቢ ባደረገ መልኩ ጥቅማቸዉን
ለማስከበር እና በዉል ግንኙነት ለተፈጠረዉ ግብይት ጥበቃ (security of transaction) በማድረግ ተወዳዳሪ
ጥቅሞችን ለማስከበር ነዉ፡፡

ሌላዉ የዚህን ችሎት ትርጉም የሚሻዉ ነጥብ በአንደኛዉ ተጋቢ የዉል ግዴታ ሲገባ ተካፋይ ያልሆነ ተጋቢ
ግዴታዉ መገባቱን አወቀ የሚባለዉ መቼ ነዉ? የሚለዉን የሚመለከት ነዉ፡፡ ከላይ እንደተመለከተዉ
የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 69/2 ስር የተጠቀሰዉ የ6 ወር የይርጋ ጊዜ ተፈጻሚ የሚሆነዉ የዉል ግዴታ
በአንደኛዉ ተገቢ መገባቱን ለሚያዉቅ ተገቢ ነዉ፡፡ ጊዜዉም ያጠረበት ምክንያትም ያለእሱ ተሳትፎ ግዴታ
መገባቱን እስካወቀ ድረስ ሁለት ዓመት እስኪሆን መጠበቅ ሳያስፈልግ ግዴታ ያመጣዉ ዉል እንዲፈርስ
መጠየቅ ይችላል በሚል እምነት ነዉ፡፡እንግዲህ ይህ ይርጋ ዉል ይፍረስልኝ በሚል ክስ የማቅረብ መብት
ቀሪ የሚያደርግ እስከሆነ ድረስ በስምምነቱ ተሳታፊ ያልሆነ[ዉ]ችዉ ተጋቢ ዉል ይፍረስልኝ ክስ ለማቅረብ
በሚያስችል ልክ ስለዉሉ መኖር የተሟላ እዉቀት ሊኖረዉ(ልኖራት) ይገባል፡፡በዚህ መሰረት በአንደኛዉ
ተጋቢ የተደረገ የገንዘብ ብድር ዉል መኖሩን ሌላዉ/ዋ ተጋቢ አወቀ/አወቀች ሊባል/ልትባል
የሚችለዉ/የምትችለዉ ቢያንስ የገንዘብ ብድር ዉሉ ከማን ጋር እንደተደረገ፣ የምን ያህል ገንዘብ ብድር ዉል
እንደሆነ፣ መቼ የተደረገ የብድር ዉል እንደሆነ ማወቅ ሲችል/ስትችል ነዉ፡፡እነዚህን ፍሬ ነገሮች ያላወቀ
ተጋቢ የገንዘብ ብድር ዉሉ ይፍረስልኝ ክስ አዘጋጅቶ ለማቅረብ ይቸገራል፡፡ምክንያቱም የገንዘብ ብድር ዉል
ይፍረስልኝ ዳኝነት በመጠየቅ ክስ የሚያቀርበዉ ተጋቢ በሌላኛዉ ተጋቢ የብድር ዉል ግዴታ መገባቱን
በጥቅሉ ከማወቅ ባለፈ የፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕጉ በቁጥር 33(2 እና 3) ፣ 80(2-4)፣85 እና 222/1
እንደተደነገገዉ የተከሳሹን ማንነት እና የክሱን ምክንያት (ለክሱ አስፈላጊ የሆኑ ፍሬ ነገሮችን) በክሱ
እንዲገልጽ ሕጉ ስለሚያስገድደዉ ሌላኛዉ ተጋቢ ከማን ጋር የምን ያህል ገንዘብ ብድር ዉል እንደተዋዋለ
እና የብድር ዉሉ መቼ እንደተደረገ ማወቅና በክስ አቤቱታዉ ላይ በፍሬ ነገር ደረጃ መግለጽ ስለሚኖርበት
እና ሥልጣን ያለዉን ፍርድ ቤት ከብድሩ ገንዘብ መጠን አንጻር ለይቶ ገልጾ ክሱን ማቅረብ ስለሚኖርበት
ነዉ፡፡

እንዲሁም አንድን ፍሬ ነገር ማስረጃ አቅርቦ የማስረዳት ሸክምን ከሚመለከተዉ መሠረታዊዉ መርህ (Basic
Principle of Burden of Proof) መረዳት እንደሚቻለዉ አንድ አከራካሪ ፍሬ ነገር አለ ብሎ የሚከራከር ሰዉ
ፍሬ ነገሩ መኖሩን በማስረጃ የማስረዳት ሸክም(ግዴታ) አለበት፡፡ (የፍ/ብ/ስ/ስ/ሕግ ቁጥር 258-260 እና
የፍ/ብ/ሕግ ቁጥር 2001/1 ይመለከቷል)፡፡በዚህ መሰረት ግዴታ መገባቱን አዉቋል ብሎ በቤተሰብ ሕጉ

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
አንቀጽ 69/2 ስር የተደነገገዉን የ6 ወር የይርጋ ጊዜ አንስቶ የሚከራከር ተከራካሪ (ተጋቢ) ሌላኛዉ ተጋቢ
ግዴታዉ መገባቱን እነዴትና መቼ እንዳወቀ ማስረዳት ይኖርበታል፡፡

በያዝነዉ ጉዳይ ተጠሪ ይፈርስ ዘንድ ዳኝነት በመጠየቅ በስር ፍርድ ቤት በአሁን አመልካች እና በስር 2ኛ
ተከሳሽ ላይ ክስ የመሰረቱበት የገንዘብ ብድር ዉል አመልካች ከተጠሪ ጋር በጋብቻ ዉስጥ ተሳስረዉ
በነበሩበት ጊዜ ከስር 2ኛ ተከሳሽ ጋር ተዋዉለዋል የተባለዉን ዉል ነዉ፡፡በዚህ የብድር ዉል ላይ ተጠሪ
በተዋዋይነት አለመሳተፋቸዉ እና ከክርክሩ እንደተገነዘብነዉም የብድር ግዴታ የተገባበት የገንዘብ መጠን ብር
450,000.00 መሆኑ የተረጋገጠ ፍሬ ነገር ነዉ፡፡ አመልካች የገንዘብ ብድር ዉል ግዴታ መገባቱን ተጠሪ
ክሱ ከመቅረቡ ከ6 ወር በፊት ታዉቅ ነበር ያሉትን ለማስረዳት ያቀረቧቸዉ ምስክሮች የሰጡት ምስክርነት
ቃል አመልካች ለክርክሩ መነሻ የሆነዉን ብድር እንደተበደሩ ለተጠሪ ነግረዋቸዋል የሚል እንደነበር የስር
ፍርድ ቤቶች በሕግ የተሰጣቸዉን የምስክሮችን ቃል የመመዘን ሥልጣን በመጠቀም ያረጋገጡት ፍሬ ነገር
ነዉ፡፡ በዚህ መልኩ አመልካች በምስክሮቻቸዉ በጥቅሉ ያስረዱት አመልካች ከማን ጋር ምን ያህል ገንዘብ
ለመበደር መቼ በተደረገ የብድር ዉል እንደተዋዋሉ ተጠሪ ዉል ይፍረስልኝ ክስ ለመመስረት በሚያስችላቸዉ
በተሟላ መልኩ አዉቀዋል የሚያሰኝ ማስረጃ ወይም ምስክርነት ቃል አይደለም፡፡

እንደሚታወቀዉ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀጽ 80(3/ሀ) ስር እንደተመለከተዉ ለዚህ ሰበር ሰሚ ችሎት


የተሰጠዉ ሥልጣን መሠረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበትን የመጨረሻ ዉሳኔ እንዲያርም ነዉ፡፡ ችሎቱ
በዚህ ሥልጣኑ ተከራካሪ ወገኖች ማስረጃ ለመቀበል፣ ለመስማትና ለመመዘን ሥልጣን ለተሰጣቸዉ የስር
ፍርድ ቤቶች ያቀረቡትን ማስረጃዎች የመመዘን ጉዳይ ዉስጥ በመግባት ማስረጃዎችን በመመርመርና
በመመዘን አከራካሪ የሆነዉ የፍሬ ነገር ጭብጥ መኖር አለመኖሩን ለማረጋገጥ የሚያስችል ሥልጣን ለችሎቱ
አልተሰጠዉም ፡፡ሆኖም የማስረጃ አቀራረብን፣ አግባብነትን፣ ተቀባይነትን እና ማስረጃ አቅርቦ አንድን ፍሬ
ነገር የማስረዳት ሸክም መርህ (Production, relevancy, admissibility and burden of proof of
evidence)እንዲሁም የማስረጃ ምዘናን ወይም የማስረዳት ደረጃን (standard of proof or weight of evidence)
የሚመለከቱ መሰረታዊ መርሆዎች ተጥሶ የተሰጠ የመጨረሻ ዉሳኔ ሲኖር መሰረታዊ የሕግ ስህተት
ስለሚሆን በሰበር ሰሚ ችሎት የሚታረም ይሆናል፡፡ በዚህ በያዝነዉ ጉዳይ ከላይ እንደተመለከተዉ ጉዳዩን
በይግባኝ የተመለከተዉ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በሕግ የተሰጠዉን ማስረጃ የመመርመርና የመመዘን
ሥልጣን በመጠቀም የግራ ቀኙን ማስረጃዎች መዝኖ አመልካች በምስክሮቻቸዉ ቃል ብድሩን እንደወሰዱ
ለተጠሪ እንደነገራቸዉ እንጂ በእርግጥ የብድር ዉሉ መኖሩን በግልጽ ለተጠሪ አላስረዱም በማለት የደረሰበት
የፍሬ ነገር ድምዳሜ ከማስረጃ ምዘና መሰረታዊ መርህ አተገባበር አንጻር ጉድለት ያለበት አይደለም፡፡
አንደኛዉ ተገቢ ገንዘብ ተበድሬያለሁ ብሎ ለሌላኛዉ ተጋቢ ተናግሯል መባሉ ብቻ መብት ለማስከበር
በሚያስችል ሁኔታ የብድር ዉል ግዴታ መገባቱን ሌላኛዉ ተጋቢ አዉቋል ብሎ ለመደምደም አያስችልም፡፡

በሌላ በኩል የስር ፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተጠሪ ክስ የማቅረብ መብት በይርጋ ቀሪ
አልሆነም ሲል የደረሰበት ደምዳሜ ከዉጤት አንጻር ተገቢ ቢሆንም ተጠሪ የብድር ዉል መገባቱን ከ6 ወር

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
በፊት እንደሚያዉቁ አመልካች በማስረጃ አስረድተዋል ካለ በኋላ በቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 69/2 መሰረት የ2
ዓመት የይርጋ ጊዜን እንደአማራጭ ይርጋ ጊዜ በመቁጠር የአመልካች ክስ የማቅረብ መብት በይርጋ
አልታገደም ሲል የደረሰበት ድምዳሜ በድንጋጌዉ የተመለከተዉን የይርጋ ጊዜያት ትክክለኛ አፈጻጸም
ያላገናዘበ ሆኖ እያለ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በዚህ ረገድ የታየዉን የይርጋ ጊዜያት አተገባበር ጉድለት
አለማረሙ ስህተት ነዉ፡፡ እንዲሁም በቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 68/መ እና 69/1 መሰረት የገንዘብ ብድር ዉል
ሲደረግ ያልተሳተፈ ተጋቢ የብድር ዉሉ እንዲፈርስ ለመጠየቅ ምክንያት ሊያደርግ የሚገባዉና ዉሉ
እንዲፈርስ ከመወሰኑ በፊት በፍሬ ነገር ደረጃ ሊረጋገጥ የሚገባዉ በገንዘብ ብድር ዉል ግዴታዉ
በተዋዋይነት አለመሳተፉን ብቻ ነዉ፡፡ከዚህ ዉጭ ዉል ይፍረስልኝ በሚል ከሚቀርብ ክስ ጋር በተያያዘ
በብድር ተገኘ የተባለዉ ገንዘብ ለትዳር ጥቅም ዉሏል ወይስ አልዋለም በሚለዉ ጭብጥ ላይ ማከራከርና
ዉሳኔ መስጠት አይቻልም፡፡ይህ አይነት ክርክር ሊቀርብ የሚገባዉ የጋብቻ ፍቺ ተከትሎ በሚደረገዉ የባልና
ሚስት ንብረት ክፍፍል ጊዜ ነዉ፡፡ስለሆነም የስር ፍርድ ቤቶች የብድር ዉል ይፍረስልኝ ተብሎ በቀረበ ክስ
ክርክር ላይ ለክርክሩ መነሻ የሆነዉ በብድር ተገኘ የተባለዉ ገንዘብ ለትዳር ጥቅም ዉሏል ወይስ አልዋለም
የሚለዉን ጭብጥ ላይ ግራ ቀኙን አከራክረዉ መወሰናቸዉ ሊታረም የሚገባዉ የክርክር አመራር ጉድለት
ነዉ ብለናል፡፡

ሲጠቃለል ለክሱ መነሻ የሆነዉ የገንዘብ ብድር ዉል የተደረገዉ በቀን 07/10/2007ዓ/ም ሲሆን ተጠሪ ክስ
የመሰረቱት ደግሞ የብድር ዉል ግዴታ ከተገባ ሁለት አመት ሳይሞላዉ በቀን 28/09/2009ዓ/ም
ነዉ፡፡አመልካች ከስር 2ኛ ተከሳሽ ጋር የገንዘብ ብድር ዉል ሲያደርጉ ተጠሪ በተዋዋይነት እንዳልተሳተፉ
ከመረጋገጡም በተጨማሪ ተጠሪ ክስ ከማቅረባቸዉ ከ6 ወር በፊት የገንዘብ ብድር ዉል ግዴታ መገባቱን
ተጠሪ ከላይ በተመለከተዉ አግባብ በተሟላ መልኩ እንደሚያዉቁ አመልካች አለማስረዳታቸዉ ተረጋግጧል፡፡
ስለሆነም የ6 ወር ይርጋ ለዚህ ጉዳይ ተፈጻሚነት የለዉም፡፡ በመሆኑም ከላይ እንደተመለከተዉ የስር ፍርድ
ቤቶች ዉሳኔ ላይ የተለያዩ ጉድለቶች ቢኖሩም ተጠሪ ክስ የመሰረቱት በተዋዋይነት ያልተሳተፉት ወይም
ፈቃዳቸዉን ያልገለጹበት ዉል እንዲፈርስላቸዉ ከመሆኑ አንጻር ሲታይ እና በቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 69/2
መሰረት የ2 ዓመት የይርጋ ጊዜ መሰረት በማድረግ ሲታይ የተጠሪ ክስ የማቅረብ መብት በይርጋ ቀሪ
አልሆነም በማለት በሰጡት ዉሳኔም ሆነ ከተጠሪ አንጻር የብድር ዉሉ እንዲፈርስ (ተጠሪን
አይመለከታቸዉም ሲሉ) በሰጡት ዉሳኔ ከዉጤት አንጻር ሲታይ በዚህ ችሎት ደረጃ ሊታረም የሚችል
የተፈጸ ስህተት ባለመኖሩ ተከታዩን ወስነናል፡፡

ዉ ሳ ኔ
1. የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 63059 ላይ በቀን 10/03/2011ዓ/ም የሰጠዉ
ብይን እና በቀን 17/04/2012ዓ/ም የሰጠዉ ዉሳኔ እንዲሁም የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ
ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 251127 ላይ በቀን 06/06/2013ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ስ/ስ/ሕግ ቁጥር
348/1 መሰረት ፀንተዋል፡፡
2. ግራ ቀኝ በዚህ ችሎት ያወጡትን ወጭ የየራሳቸዉን እንዲችሉ ተወስኗል፡፡

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም
ት እ ዛ ዝ
1. የዉሳኔዉ ግልባጭ ለሥር ፍርድ ቤት ይተላለፍ፡፡ ግራ ቀኙ ሲጠይቁም ግልባጩ ይሰጣቸዉ፡፡
2. በመዝገቡ ላይ የተሰጠ እግድ ካለ ተነስቷል፡፡ይጻፍ፡፡
3. መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡
የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት
ሠ/ኃ

ማስታወሻ፡ - ይህ የ ሰበር ችሎት ውሳኔ ሰነ ድ ለጥና ትና ምር ምር ሥራ ወይም ለግንዛ ቤ እ ንጂ


ለፍር ድ አ ፈጻ ጸ ም ዓላማ አ ያገ ለግልም

You might also like