You are on page 1of 2

+ ቅዱስ አጠራር +

ቅዱስ ጳውሎስ ፦ ያዳነን በቅዱስም አጠራር የጠራን እግዚአብሔር ነውና፥ ይህም እንደ ራሱ አሳብና ጸጋ መጠን ነው
እንጂ እንደ ሥራችን መጠን አይደለም ሲል ተናገረ፡፡ /2 ጢሞ 1፡9/

መጠራራትን ሁላችንም ተጠራርተን እናውቃለን፡፡ በጩኸትም በፉጨትም በእጅ ምልክትም በጥሪ ወረቀትም በስልክም
ተጠራርተን እናውቃለን:: ቅዱስ አጠራር ግን እንደምን ያለ ነው? እግዚአብሔር ቅዱስ ነውና እርሱ ሰውን የሚጠራበት
ጥሪም የተቀደሰ ነው፡፡ ይህ ጥሪ እንደምን ያለ ነው? ቅዱስ ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ጥሪ ለምን ቅዱስ አጠራር አለው?

እርሱ ራሱ ከተጠራበት አጠራር እንጀምር ይሆን? ሳውል/ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ሊያስርና ሊያሰቃይ ከበላይ አካል
ደብዳቤን ተቀብሎ በደስታ እየቸኮለ ሲሔድ የበላዮች በላይ ደማስቆ ላይ አስቆመውና ጠራው፡፡ ለብዙዎች ሞት ፈቃድ
ተቀብሎ ተሹሞ ሲመጣ ጌታ ከመንገድ አስቁሞ ለብዙዎች መዳንን እንዲሰብክ ፈቃድ ሠጠው፡፡ የጦር ዕቃ ጭኖ እየዛተ
ሲመለስ ጦርና ጋሻውን አስጥሎ ራሱን ምርጥ ዕቃ አደረገው፡፡ በቅዱስ አጠራር የጠራው እግዚአብሔር ነውና!

ስለ ጴጥሮስ አጠራርስ ምን እንናገር? የሃምሳ አምስት ዓመቱ ዓሣ አጥማጅ ጎልማሳ ፣ ሌሊቱን ሙሉ መረቡን ጥሎ
የሚያድረው ትዕግሥተኛ እንዴት እንደተጠራ ልብ በሉ፡፡ ለእርሱ ብዙ ዓሣ ከመያዝ በቀር ምንም ሕልም አልነበረውም፡፡
የታንኳዎቹን ቁጥር ከማብዛት የዓሣዎቹን ገበያ ከማስፋፋት በቀር በጎልማሳ ዕድሜው አዲስ ሕልም አልነበረውም፡፡

የመጦሪያ ዘመኑን እንዴት እንደሚያሳልፍና የዕድሜ ፀሐዩ ስትጠልቅ መረቡን አጥምዶ ለመመልከት ዝግጁ ከመሆን በቀር
ምንም አዲስ ዕቅድ አልነበረውም:: ጀልባው ላይ ተሳፍሮ ደግ ደጉን የሚያወራው ናዝራዊ ግን ድንገት መጥቶ
ጎልማሳነቱን እንደ ንሥር አደሰው፡፡ ሕይወቱን እንደ አዲስ አሁን እንደተወለደ ሕፃን ከሃምሳ ዓምስት ዓመቱ
አስጀመረው፡፡ በዚያ ዕድሜው የሦስት ዓመት መንፈሳዊ ኮሌጅ ገብቶ በእሳትና በነፋስ ታጅቦ ተመርቆ : በሰባ ሁለት ቋንቋ
እንደ አዲስ አፉን ፈትቶ እንዲያወራና ዓሣ ማስገሩን እርግፍ አድርጎ ትቶ በወንጌል መረብ ሰውን አጥማጅ እንዲሆን
አደረገው፡፡ በድንቅ አጠራሩ የጠራው እግዚአብሔር ነውና!

ስለ ሐዋርያው ናትናኤልስ እንናገር ይሆን? ጓደኛው ፊልጶስ "የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘነው" ብሎ ሲጠራው ብዙም ደስ
አላለውም ነበር፡፡ የናዝሬቱ መሲሕ የሚል ቃል ሲስማ ከይሁዳ ቤተልሔም መሲህ እንደሚመጣ ከሚያውቀው ትንቢት
ጋር አልገጥም ብሎት ‘ደግሞ ከናዝሬት መሲህ ይነሣል እንዴ?’ እያለ በምሁራዊ ትዝብት ተውጦ እስቲ ልየው በሚል
ንቀት ሳይዋጥለት ነበር የመጣው፡፡ እስቲ ልየው ብሎ ያገኘው ናዝራዊ ግን ራሱን ልቡ ድረስ ተመለከተው፡፡ ሳያውቅ
የጠቀሰውን ጥቅስ አስጥሎ የሚያውቀውን የራሱን የተሸሸገ ማንነት ሲነግረው መቋቋም አልቻለም፡፡ አንተ
የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ብሎ መሰከረ፡፡ እርሱ እንደመሰለው የጠራው ጓደኛው ፊልጶስ አልነበረም ፤ በቅዱስ አጠራሩ
የጠራው እግዚአብሔር ነውና!
የቀሬናዊው ስምዖን አጠራር ግን ከሁሉ የባሰ ነበር ፤ እርሱ መንገደኛ ነበረ ፤ መንገድ አላፊ እንደሚጣደፍ እየተጣደፈ
ነው፡፡ ሰንበት ሳይገባበት ለመጓዝ ከኢየሩሳሌም እየቸኮለ ሲወጣ አንድ ብዙ ሕዝብ አጅቦት ግማሹ በማዘን የሚጮኽለትና
ግማሹ በጥላቻ የሚጮኽበት የሕማም ሰው ሲንገላታ ተመለከተ::

መንገዱን ገታ አድርጎ ትንሽ ሊመለከት እንጂ ሊቆይ ሃሳብ አልነበረውም:: ነገር ግን ወታደሮች ግድ አሉት:: ሳያስበው
የጌታ የሕማሙ ተካፋይ የመስቀሉ ተከታይ ሆነ:: ዓለም የዳነበትና የጌታ ደምና ወዝ የፈሰሰበትን ቅዱስ መስቀል ተሸክሞ
አንድ ምዕራፍ ተጉዋዘ:: ያገዝነው ሲመስለን የሚያግዘንን ያገለገልነው ሲመስለን የሚያከብረንን ክርስቶስን ተጠግቶ
መቼም የማይገኝ ክብርን ተጎናጸፈ:: በዚያች ዕለት መስቀሉን ተሸከም ብለው የጠሩት እንደመሰለው ሮማውያን
ወታደሮች አልነበሩም:: በቅዱስ አጠራር የጠራው እግዚአብሔር ነውና!

ጌታ ሆይ እኔ ባሪያህን የጠራህበት ቅዱስ አጠራር እንዴት ያለ ይሆን? ስንቴ ጠርተኸኝ እንዳልሰማ ጥዬ ሔጄ ይሆን?
የአንተን ጥሪ ገፍቼ ለዓለም ጥሪ ጉዋጉቼ ስንቴ ሔጄ ይሆን? "አብዝቼ ብጠራቸው አጥብቀው ከፊቴ ራቁ" ካልካቸው
መካከል እሆን ይሆን?

እባክህን ባልሰማህም ጥራኝ : ባልመጣም ጥራኝ : ጴጥሮስ በባሕር ላይ እንደለመነህ "ወደ አንተ እመጣ ዘንድ እዘዘኝ" :
እንደ አልዓዛር "ውጣ" ብለህ በቅዱስ አጠራር ጥራኝ:: እንደ ማቴዎስ ከቀራጭነት ገበታዬ ላይ : እንደ ዘኬዎስ ከዛፍ ላይ :
እንደ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ በሰረገላዬ ላይ ብቻ ባገኘኸኝ ቦታ ጥራኝ::

ሙት በሚቀሰቅስ ማዕበል በሚገሥፅ ድምፅህ ባልሰማህም ጥራኝ : ጆሮዬ አልሰማ ካለህ እንደ ማልኮስ ጆሮ ሠጥተህ
አንተን ብቻ በሚሠሙ ጆሮዎች ፈውሰኝና ጥራኝ:: ዓይኔ ዓላይ ካለህ ከአፈር በምራቅህ ለውሰህ እያየሁ እንድመጣ
አድርገህም ቢሆን ጥራኝ:: አሁን በቅዱስ አጠራርህ ስትጠራኝ ካልሰማሁህ በኁዋላ ልትፈርድ ስትመጣ "እናንተ የአባቴ
ቡሩካን ወደ እኔ ኑ" የሚለው ቅዱስ አጠራርህንም ሳልሰማ መቅረቴ አይደል? አሁን ጥሪህን ካልሰማሁ በኁዋላ ቃለ
ሕይወትን አልሰማምና እንደ ሥራዬ ሳይሆን እንደ አንተ አሳብና ጸጋ መጠን ጥራኝ!

"ያዳነን በቅዱስም አጠራር የጠራን እግዚአብሔር ነውና፥ ይህም እንደ ራሱ አሳብና ጸጋ መጠን ነው እንጂ እንደ ሥራችን
መጠን አይደለም"

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

የካቲት 5 2013 ዓ.ም.

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

You might also like