Professional Documents
Culture Documents
|ወደ አሜሪካ ለመብረር ከመነሣቴ ከአራት ሰዓታት በፊት ሦስት ጓደኛሞች በምናዘወትረው የአራት ኪሎው ማለዳ ካፌ ቁጭ
ብለናል፡፡ አንዱ ወዳጃችን ታድያ «ሰውኮ እህህ» የሚል የስሙኒ ጥቅስ አምጥቶ ይንጨረጨራል፡፡ «እገሌ እንዴት እንዲህ
ይሆናል፡፡ እገሌስ እንዴት ይህንን ያህል ይወርዳል፡፡ እገሌስ ቢሆን ንግግሩ እንዲህ መሆን የጀመረው መቼ ነው፡፡ ደግሞ
የእገሊት ይግረም» አያለ ይብሰከሰካል፡፡
እየደጋገመ «ለካስ ሰው ባስቀመጡት ቦታ አይገኝም» ይላል፡፡ ሁለተኛው ወዳጃችን እስኪጨርስ ታገሠውና «ግን ችግሩ ያለው
ከእነርሱ ነው ወይስ ካንተ?» የሚል ያልተጠበቀ ጥያቄ አመጣ፡፡ እኔ ራሴ በጥያቄው አዘንኩም ተገረምኩም፡፡ ሰዎቹ ያደረጉትን
ነገር እየዘረዘረለት እንዴት ተበዳዩን ችግሩ ካንተ ሊሆን ቢችልስ ይለዋል ብዬ ተቀየምኩት፡፡
«አንድ ነገር እስኪ ልጠይቃችሁ» አለን፡፡
«ምን?» አልነው በጋራ፡፡
አንድ ሰው የነብር ግልገል ከዱር አምጥቶ ቤት ውስጥ ከድመቶቹ ጋር አብሮ አለመደው፡፡ ነብሩ ለመደና ለአቅመ ጎልማሳ
ደረሰ፡፡ ሰውዬውም የነብሩን ነብርነት ዘነጋው፡፡ እንደ ድመትም ቆጠረው፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን ነብሩ ጓዳ ውስጥ የተቀመጠ
ሥጋ ከድመቶቹ ጋር ተባብሮ ሰረቀ፡፡ ሰውዬው በዚህ ተናደደና ድመቶቹን እና ነብሩን በአለንጋ እያሯሯጠ መግረፍ ጀመረ፡፡
ድመቶቹ መጀመሪያ ላይ ለመበሳጨት ቢሞክሩም ወደ ኋላ ሲብስባቸው እየሮጡ አመለጡ፡፡
ነብሩ ግን እምምምም አለ፡፡ ፀጉሩን አቆመ፡፡ ጥፍሩን ሳበ፡፡ አንገቱን አሰገገ፡፡ ከዚያም ተወረወረና ባሳዳጊው አናት ላይ ተቆነሰ፡፡
ፍጻሜውም ሳያምር ቀረ፡፡ አሁን ለተፈጠረው አሳዛኝ ነገር ተጠያቂው ማነው? አለ ወዳጃችን፡፡
ጓደኛዬ አየው፡፡ እኔም አየሁት፡፡
ሰውዬው ነብር ማሳደጉን ረሳው፡፡ ነብሩ ግን ነብርነቱን አልረሳም፡፡ ምንም ከድመት ጋር ቢያድግ ነብር ነብር ነው፡፡ ነብርን
ብትወድደው እንኳን ነብርነቱ እንደተጠበቀ መሆን ነበረበት፡፡ ነብርነቱን መዘንጋት አልነበረበትም፡፡ ትልቁ ችግር በሰውዬው
ኅሊና ውስጥ ያለው ነብር እና እውነተኛው ነብር መለያየቱ ነው፡፡
በሰውዬው ኅሊና ውስጥ ታዛዥ፣ ለማዳ፣ ሰው አክባሪ፣ ትኁት፣ የተገራ ነብር ነበረ፡፡ እውነተኛው ነብር ግን ቁጡ፣ ደመ ሞቃት፣
ሲመረው ርምጃ የሚወስድ ነው፡፡ እናም ጥፋቱ የሰውዬው ነበር፡፡
እኛም ከሰዎች ጋር በሚኖረን ግንኙነት የነብሩ እና የሰውዬው ዓይነት ነገር ይገጥመናል፡፡ እኛ በኅሊናችን የምናውቃቸው እና
በዓለም ላይ ያሉን ወዳጆች ሊለያዩ ይችላሉ፡፡ እኛ አንዳንድ ጊዜ በእውኑ ዓለም ያሉትን ወዳጆቻችንን ረስተናቸው በኅሊናችን
ካሉት ወዳጆቻችን ጋር ለብዙ ዘመናት እንኖራለን፡፡ እንዲሆኑ ከምንፈልገው ጋር እንጂ ከሆኑት ጋር አንተዋወቅም፡፡
ሰዎቹ በእውኑ ዓለም ሳይለወጡ በእኛ ኅሊና ውስጥ ግን እንለውጣቸዋለን፡፡ ጥሩ ጥሩውን ወይንም መጥፎ መጥፎውን
እንሰጣቸዋለን፡፡ ቢሆኑ ብለን የምናስበውን እንደሆኑ አድርጎ ኅሊናችን ማሰብ ይጀምራል፡፡ ታድያ አንድ ቀን በኅሊናችን ያሉትን
ወዳጆቻችንን አጥተን በእውን ያሉትን ስናገኝ ተቀየሩ፣ ተበላሹ እንላለን፡፡ እነርሱ ጥንትም እንዲሁ ነበሩ፡፡ ያንተም ችግር ይኼ
ቢሆንስ?»አለና ጓደኛዬን ሞገተው፡፡
«እኔ ሳውቃቸው እንዲህ አልነበሩም፡፡ የተማሩ፣ ብዙ የሚያውቁ፣ በሃይማኖታቸው የበሰሉ፣ የተከበሩ፣ ከትልልቅ ቤተሰቦች
የተገኙ፣ ብዙ ነገር የሠሩ እኮ ናቸው፡፡ በኋላ ነው የተቀየሩት፤ ከጊዜ በኋላ መሆን አለበት የተለወጡት፡፡» ጓደኛዬ ተከራከረ፡፡
ይህኮ ያንተ ግምት ቢሆንስ? አንዳንድ ጊዜ ከመጻሕፍት፣ ከተረቶች፣ ከፍላጎታችን፣ ከፊልሞች፣ ከትምህርቶች፣ ከሙዚቃዎች፣
ከአባባሎች፣ ከሰዎች ታሪኮች ወዘተ ተነሥተን በኅሊናችን የምንስላቸው ሥዕሎች አሉ፡፡ የኔ ሚስት፣ የኔ ባል፣ የኔ ጓደኛ፣ የኔ
አለቃ፣ የኔ ልጅ፣ የኔ ጎረቤት፣ የኔ የሥራ ባልደረባ፣ እንዲህ ቢሆን ደስ ይለኛል እያልን የምንስላቸው ሥዕሎች፡፡
እነዚህ ሥዕሎችን መቶ በመቶ የሚያሟላ ሰው አይገኝም፡፡ ምክንያቱም እኛም ሥዕሎቹን የቀረጽናቸው ከተለያዩ ሰዎች ወስደን
ነውና፡፡ ታድያ ከሥዕሎቹ ክፍሎች ውስጥ በጣም የተመሰጥንበትን የያዘ ሰው ስናገኝ እንደሰታለን፡፡ ሁሉን ያሟላ አድርገንም
እንቀበለዋለን፡፡ ሰውዬው ሁሉን ስላሟላ ሳይሆን እኛ በአካል የሌለውን በኅሊናችን ሞልተንለት ነው፡፡ ይኼኔ እግዜር የፈጠረው
እና እኛ የፈጠርነው ወዳጃችን እንለያያለን፡፡
ለዚህ እኮ ነው ሽር ብትን ብለው የተጋቡ ባል እና ሚስት «እንዲህ መሆንሽን ባውቅ ኖሮ አላገባሽም፣ እንዲህ መሆንህን ባውቅ
ኖሮ አላገባህም ነበር» እስከ መባባል የሚደርሱት፡፡ አንዳንዶቻችን ያገባነው እግዜር የፈጠረውን ባል ወይንም እግዜር
የፈጠራትን ሚስት አይደለም፡፡ ራሳችን የፈጠርናትን ነው፡፡ ታድያ አንድ ቀን በኅሊናችን የሳልነውን ሰው እናጣውና
እውነተኛውን ሰው ስናገኘው ተለወጠ እንላለን፡፡ የተለወጥነው ግን እኛ ነን፡፡
«በዚህ ዓይነት ደኅና ሰው የለም እያልከን እኮ ነው?» አልኩት፡፡
ደኅና ሰውነት አንፃራዊ ነው፡፡ እንደ ዐፄ ዮሐንስ ሃይማኖት፣ እንደ ዐፄ ቴዎድሮስ ጀግንነት፣ እንደ ዐፄ ምኒሊክ ጥበብ የተሰጠው
መሪ ይኖራል፡፡ ይህ እንግዲህ በእውኑ ዓለም ሲሆን ነው፡፡ የኛ ችግር ግን የዮሐንስንም ሃይማኖት፣ የቴዎድሮስንም ጀግንነት፣
የምኒሊክንም ጥበብ የያዘ አንድ መሪ በኅሊናችን እንፈጥራለን፡፡ ከሦስት ሰዎች ጥሩ ጥሩ የተባለውን ወስደን አንድ ሰው
እንሠራለን፡፡ ምኒሊክን ስናገኘው የቴዎድሮስን ጠባይ እናጣበትና ተለወጠ እንላለን፡፡ ቴዎድሮስንም ስናገኝ የምኒሊክን ጠባይ
እናጣበትና ተለወጠ እንላለን፡፡ ያ ግን መጀመርያም ያልነበረ ነው፡፡
«እና አንተ ሁሉን ያሟላ ሰው አይገኝም እያልክ ነው?» ወዳጄ ተበሳጨና ጠየቀ፡፡
ሁሉን ወደ ማሟላት የሚጠጋ እንጂ ሁሉን የሚያሟላ ሰው አይገኝም፡፡ እኛ ግን መጀመርያውኑ ሰውዬው ሁሉ አለው ብለን
ስለምናስብ እንዲያሟላ ሳንረዳው እንቀራለን፡፡ ከማንፈልገው ተነሥተን ወደምንፈልገው ከመሄድ ይልቅ ከምንፈልገው
ተነሥተን ወደማንፈልገው እንሄዳለን፡፡
«አሁን አንተ የምትለው ከእኔ ጋር አይገናኝምኮ፡፡ እኔኮ ዐውቃቸዋለሁ፡፡ እንደዚህ አልነበሩም፡፡ በጣም ደግ እና ትኁታን
ነበሩ፡፡ እንዲህ ዓይነት የማፍያ ሥራ የሚሠሩ አልነበሩም፡፡»
ምን ያህል ርግጠኛ ነህ? እነዚህን ሰዎች የምታውቃቸውኮ ከአንተ ጋር ሲሆኑ ምን ዓይነት ሰዎች እንደሚሆኑ እንጂ በኑሮአቸው
ሁሉ ምን ዓይነት እንደሆኑ አይደለም፡፡ የአንድን ሰው ሙሉ ጠባይ ለማወቅኮ በተለያየ ጊዜ፣ በተለያየ ሁኔታ፣ በተለያየ
ግንኙነት፣ በተለያየ ደረጃ፣ በተለያየ ዐቅም፣ ከተለያዩ ሰዎች ጋር፣ በተለያየ ደስታ እና ችግር ውስጥ፣ ማየት ይኖርብሃል፡፡ አንተ
ጠባቂ መልአኩ አይደለህ በዚህ ሁሉ አብረኸው የምትሆን? ታድያ እንዴት ርግጠኛ ሆነህ ትናገራለህ? «እኔ የማውቀው ይህንን
ያህል ነው» በል እንጂ እገሌ እንደዚህ ነው አትበል፡፡
በመካከል ጣልቃ ገባሁና «ታድያ በዚህ ዓይነት ከሰው ጋር መኖር እንዴት ይቻላል? የግድኮ ተጠራጣሪ ልትሆን ነው ማለት
ነው? መተማመን ጠፋ በለኛ» አልኩት፡፡
እንዲያውም መተማመንን የሚያጠፋው የእናንተ አካኼድ ነው፡፡ አለ ወንበሩ ላይ እየተደላደለ፡፡
መተማመን እውነታውን ከመቀበል ነው የሚመጣው፡፡ እውነታው ምንድን ነው? ሰውን ሙሉ በሙሉ ማወቅ አይቻልም፤
እንደ ገናም ሰው የተሟላ አይደለም፡፡ ይህ ነው እውነታው፡፡ ስለ አንድ ሰው ዛሬ የማታውቀው ነገ የምታውቀው ነገር ሊኖር
እንደሚችል፤ ከዚያም አልፎ ሳታውቀው እስከ መጨረሻው ልትቀር የምትችል ነገር ሊኖር እንደ ሚችል፤ አንድ ሰው ዛሬ
የሌለውን ነገ ሊኖረው እንደሚችል፤ ዛሬ ያልሆነውን ነገ ሊሆነው እንደሚችል ርግጡን ማመን አለብህ፡፡
እውነታውን መቀበሉ ሁለት ነገሮችን እንድታደርግ ይረዳሃል፡፡ የመጀመርያው ሰውዬውን እንድትረዳው፡፡ አለው ብለህ
ከምትቀመጥ እንዲኖረው ትረዳዋለህ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ወዳጅነትህ በምትግባቡበት ነገር ላይ ብቻ እንዲመሠረት
ታደርገዋለህ፡፡
ለምሳሌ ሚስትህ የሌላትን ስንደዶ አፍንጫ ፍለጋ በኅሊናህ ከምትኳትን ያላትን ዞማ ፀጉር ለምን አትወድላትም? ሚስትህም
ብትሆን የሌለህን ጀግንነት በኅሊናዋ እየሳለች ፍለጋ ከምትንከራተት ያለህን ደግነት ለምን አትወድደውም፡፡ አንዳንድ ጊዜ
ወዳጅነቶቻችን በሌሉን ነገሮች ላይ ይመሠረታሉ፡፡ እነዚያን የሌሉ ነገሮች አለመኖራቸውን አንድ ቀን ስናውቅ ጥርጣሬ
ያድርብናል፡፡ መተማመንም ይጠፋል፡፡
ታስታውሱ እንደሆነ ልጅ ሆነን የተሠራ ሕንፃ፣ የተገነባ መንገድ፣ የተገደበ ግድብ፣ የተጠቀጠቀ ጫካ፣ የፈሰሰ ወንዝ፣ ከፍ ያለ
ተራራ የተኮለኮለ ገበያ፣ የተከፈተ ሆቴል፣ የታነፀ ቤተ ክርስቲያን፣ የተሠራ መስጊድ ሁሉ ከዓለም አንደኛ ከአፍሪካ ሁለተኛ ነው
እየተባለ ይነገረን ነበር፡፡ በዚህ የተነሣ በኛ ኅሊና ውስጥ ያለቺው ኢትዮጵያ እና በአፍሪካ ቀንድ ያለቺው ኢትዮጵያ ትለያይ
ነበር፡፡ ዓለም ሁሉ ስለኛ የሚያውቅ እና የሚያወራ ነበር የሚመስለን፡፡
በኋላ ከፍ እያልን ስንሄድ መደንገጥ ጀመርን፡፡ በኅሊናችን የተሳለቺውን ኢትዮጵያ አጣናት፡፡ እውነተኛዋ ኢትዮጵያ «እማማ
ኢትዮጵያ» ብለን ከዘፈንላት ኢትዮጵያ የተለየች ሆነቺብን፡፡ የዳቦ ቅርጫት ናት ያልናት ሀገራችን ለዳቦ ተሰልፋ አገኘናት፡፡
ኩሩው ሕዝባችን ርዳታ ሲለምን አገኘነው፡፡ ያን ጊዜ ደነገጥን፡፡ አየህ በእውኑ ዓለም ያለቺውን ኢትዮጵያን ተቀብለን
ወደምንፈልጋት ኢትዮጵያ ከመለወጥ ይልቅ፤ በአካል የሌለቺውን እና በኅሊናችን የተሳለቺውን ኢትዮጵያ ተቀብለን ስንኮፈስ
ኖርን፡፡ መጨረሻ ግን እውነቱን እየመረረንም ቢሆን ዋጥነው፡፡
ሕዝባችን ስለየቤተ እምነቱ እና ስለ እምነት አባቶቹ የሳለው ሥዕልኮ በእውኑ ዓለም የሌለ ነው፡፡ በእርሱ ኅሊና ያለው
በትምህርት የሰማው፣ በመጽሐፍ ያነበበው እና በታሪክ የተማረው ነው፡፡ አሁን በገሐዱ ዓለም ያለውን አያውቀውም፡፡
እውነቱን ዐውቆ የሚፈልገውን ለማምጣት ከመሥራት ይልቅ በኅሊናው ያለውን ተቀብሎ መኖርን ይመርጣል፡፡ ያልሆነውን
እንደሆነ አድርጎ ተቀብሎ መኖር ይወድዳል፡፡ ታድያ አንድ ቀን ከእውነቱ ጋር ሲላተም ይደነግጣል፡፡ ይጠራጠራል፡፡ ያኔ ታድያ
እንደ አንተ ነገሮች ተለወጡ ይላል፡፡ የተለወጠው ግን እርሱ ነው፡፡ ለውጡ እውነቱን ማወቁ ነው፡፡
በአማዞን ደን ውስጥ በቅርቡ ከዘመናዊው ዓለም ርቀው የሚኖሩ ሕዝቦች «ተገኙ»፡፡ የዓለም ማኅበረሰብ ቁጥር በአንድ
ጨመረ፡፡ ታድያ የዓለም ማኅበረሰብ ቁጥር በአንድ ስለ ጨመረ ቀድሞ የነበረው እውነት ነው እንዴ የተቀየረው? ፈጽሞ፡፡
ቀድሞም አሁን የደረስንበት የዓለም ማኅበረሰብ ቁጥር ነበር፡፡ ችግሩ እኛ አናውቀውም፡፡ አሁን ይበልጥ ወደ እውነቱ ተጠጋን፡፡
እነዚህን ሰዎች ካለመኖር ወደ መኖር አላመጣናቸውምኮ፡፡ መኖራቸውን ዐወቅን እንጂ፡፡
ለውጥ ያለው ኅሊና ውስጥ ነው፡፡ የኛ ሥዕሎች ናቸው በየጊዜው የሚለወጡት፡፡ ሥዕሎቹን የሚቀይራቸው ደግሞ
እውነታዎችን እያወቅን መሄዳችን ነው፡፡ እነዚህ ሥዕሎች ከምናውቀው ተነሥተን የማናውቀውን በራሳችን ሞልተን የሳልናቸው
ናቸው፡፡ ይበልጥ እውነቱን ስናውቅ ይበልጥ ሥዕሎቻችን ይቀየራሉ፡፡ ታድያ ያንጊዜ ሰዎች የተቀየሩ ይመስለናል፡፡
«እና ጥፋተኛው እኔ ነኝ በለኛ» አለ ጓደኛዬ፡፡
በገጠር መንደር ውስጥ ከፍ ያለ ጎጆ ሠርቶ «በዓለም አንደኛ ቤት» እያለ እድሜውን በሙሉ ሲመካ የኖረን ሰው ሲንጋፖርን
አሳይተህ ብታመጣው ቤቱን መናቅ ይጀምራል፡፡ ቤቱ ታንስበታለች፣ ኋላ ቀር ትሆንበታለች፣ ተራ ትሆንበታለች፡፡ እርሱ
አላወቀም እንጂ ቤቱኮ እንዲሁ ነበረች፡፡ የተለወጠችው ቤቱ ሳትሆን እርሱ ነው፡፡ ችግሩ ስለ ቤቱ ከሳለው ሥዕል የመጣ እንጂ
ከቤቱ አይደለም፡፡
አሁንም ችግሩ ካንተ ነው፡፡ የኖርከው ካልነበሩ ሰዎች ጋር ነበርና፡፡
ሂሳባችንን ከፍለን ተለያየን፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በረራ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ
Email This HYPERLINK "http://www.blogger.com/share-post.g?
blogID=4505965735890921949&postID=8860223701829100836&target=blog"BlogThis!
HYPERLINK "http://www.blogger.com/share-post.g?
blogID=4505965735890921949&postID=8860223701829100836&target=twitter"Share to
Twitter HYPERLINK "http://www.blogger.com/share-post.g?
blogID=4505965735890921949&postID=8860223701829100836&target=facebook"Share to
Facebook
Posted by ዳንኤል ክብረት
55 comments:
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 8:18 AM
dani min libelih egiziabher ke betesebochi gar be selam yitebikih digil mariam ke fit ke
huala kelela tihunih
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 8:52 AM
Dn. Dani arif tsihuf new . Keep it up !!! "ከዓለም አንደኛ ከአፍሪካ ሁለተኛ ነው እየተባለ ይነገረን
ነበር፡፡"please correct this to "ከአፍሪካ አንደኛ ከዓለም ሁለተኛ ነው እየተባለ ይነገረን ነበር፡፡". Beside
that "ሕዝባችን ስለየቤተ እምነቱ እና ስለ እምነት አባቶቹ የሳለው ሥዕልኮ በእውኑ ዓለም የሌለ ነው፡፡" Daniye
Esti liteyikihi፤ሕዝባችን ስለየቤተ እምነቱ እና ስለ አንተ የሳለው ሥዕል በእውኑ ዓለም ያለ ነውን???
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 9:06 AM
እግዚአብሄር ይባርክህ ዲ/ን ዳንኤል፡፡ እግዚአብሄር ሁላችንንም ከማንፈልገው ተነሥተን ወደምንፈልገው እንድንሄድ
ይርዳን፡፡
Amen.
H from Addis
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 10:20 AM
first of all let me introduce myself; i am wasihun from addis abeba.this is my first
comment but i read each 2010 and 2011 articles.i am so wendering and excited about all
articles.pleas dani try to write about the current situation mahiber kidusan.God bless
u.thank u.
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 10:45 AM
"ለውጥ ያለው ኅሊና ውስጥ ነው፡፡ የኛ ሥዕሎች ናቸው በየጊዜው የሚለወጡት፡፡ ሥዕሎቹን የሚቀይራቸው ደግሞ
እውነታዎችን እያወቅን መሄዳችን ነው፡፡ እነዚህ ሥዕሎች ከምናውቀው ተነሥተን የማናውቀውን በራሳችን ሞልተን
የሳልናቸው ናቸው፡፡ ይበልጥ እውነቱን ስናውቅ ይበልጥ ሥዕሎቻችን ይቀየራሉ፡፡ ታድያ ያንጊዜ ሰዎች የተቀየሩ
ይመስለናል፡፡"
ዲ/ን ዳንኤል ቃለ ሕይወት ያሰማንል፡፡ ይህ ለእኔ ትልቅ መንፈሳዊ ስብከት ነው፡፡ እይታወችህ ሁሉ በጣም ግሩምና
ልብን የሚነኩ እንዲሁም ሕይወትን የሚለውጡ ናቸው፡፡ ከዚያም አልፎ ተርፎ አመለካከትን የሚቀይሩ ከክፋት ወደ
ደግነት የሚመልሱ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር አብዝቶ ጸጋውን ያድልህ፡፡ አንተ ከእግዚአብሔር በተሰጠህ የማስተማር
ጸጋ አስተምረን እኛም በተሰጠን የመማር ጸጋ እንማራለን፤ ማስተማርም መማርም ጸጋ ነውና፡፡
መጣዓለም አ.
ኮምቦልቻ ወሎ
Reply
•
Gebre Z CapeAugust 12, 2011 at 10:50 AM
Great Dani, you are a star!!
"በኋላ ከፍ እያልን ስንሄድ መደንገጥ ጀመርን፡፡ በኅሊናችን የተሳለቺውን ኢትዮጵያ አጣናት፡፡ እውነተኛዋ ኢትዮጵያ
«እማማ ኢትዮጵያ» ብለን ከዘፈንላት ኢትዮጵያ የተለየች ሆነቺብን፡፡ የዳቦ ቅርጫት ናት ያልናት ሀገራችን ለዳቦ
ተሰልፋ አገኘናት፡፡ ኩሩው ሕዝባችን ርዳታ ሲለምን አገኘነው፡፡ ያን ጊዜ ደነገጥን፡፡ አየህ በእውኑ ዓለም ያለቺውን
ኢትዮጵያን ተቀብለን ወደምንፈልጋት ኢትዮጵያ ከመለወጥ ይልቅ፤ በአካል የሌለቺውን እና በኅሊናችን የተሳለቺውን
ኢትዮጵያ ተቀብለን ስንኮፈስ ኖርን፡፡ መጨረሻ ግን እውነቱን እየመረረንም ቢሆን ዋጥነው፡፡"
The thing is, we/figures try to draw a picture that we want ourselve to be in the others
mind before we are really there. Here comes the problem, the mismatch between the
demand and supply.
I think it is better to draw a picture that is at least equal to our size,
We better speak that at least something that we can try it.
Here, you see we can easily make corrections when there is of our mistake,because we
know who we are.
And I am afraid that the resemblance of the 'nebir' nature with that of our weaknesses is a
bit exaggerated, as weaknesses can be improved and be changed.
Than you
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 2:03 PM
ዝም ነዉ እንጅ ሌላ ምን ይባላል!!!!!!!!!!!!!!!!
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 2:08 PM
Dani i don't know what to say about this issus but thanks a lot because you write what i
am thinking bout myself, Thanks again Egziabher Yibarke
Reply
•
Eyob G.August 12, 2011 at 2:13 PM
ሸጋ ነው! ... ይህ እውነትነቱ እንዳለ ሆኖ ... የኅሊና ሥዕሎቻችን፦ እንዲያምሩልን በፈቀድነው መጠን ፤
እንዲያስጠሉም በፈለግነው ልክ በኅሊናችን የሚሳሉ ብቻ ሳይሆኑ ፤ አንዳንዴም በገሃዱ ዓለም ያሉ ሀቆች ፤ ካርቦን
ኮፒዎችም ናቸው ፤ ችግሩ በገሃዱ ዓለም ያለውን ኦሪጅናሌ ስዕል ሰዓሊው በወደደ ጊዜ ሲያሳምረው ፤( በሂደትም
አለቅጥ ቀለም ሲያበዛበት ) ፣ የማይረባ ስፍራም ሲጥለውና አለመጠን መልኩ ሲደበዝዝ ፤ እንዲያም ሲል በየቦታው
ሲሸራረፍ ፤ በእኛ ኅሊና ውስጥ ያለው ስዕል ፤ የቀድሞው ስዕል ካርቦን ኮፒ መሆኑ ነው። ... በመሆኑም ከዚህ
መለያየት የተነሳ መገረሙና መደነቁ ፤ መደሰቱና ማዘኑ ይከሰታል። ( ... ይህም ኅሊናችን ፦ አንድም መሬት ላይ
ስላለው ስዕል ወቅታዊ የሆነ የተሟላ መረጃ የለውም ፤ አንድም ሰዓሊው የራሱን ስዕል እንዳሻው ሊያደርገው
የሚችልበትን መብቱን በመጋፋት ፤ ቀድሞ የሳልከው ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ እያለ ነው ማለት ነው። ) ... ይህም ሆኖ
... ውበት እንደተመልካቹ ቢሆንም ፤ ‘ማሕበረሰባዊ ውበት’ ( በአብዛኛው ሰው ቅቡል የሆነ ውበት ) አለና ... ከዛ
የተነሳ ኅሊናችን ፤ በኅሊና ያለውን የቀድሞውን ስዕል ኮፒ ፤ መሬት ላይ ካለው ወቅታዊ ስዕል ጋር ውበቱን አነጻጽሮ
... የቀድሞው ካሁኑ ይሻላል ( ያምራል ) ፣ ያሁኑ ከቀድሞው ... ... ... እያለ የራሱን ፍርድ ቢሰጥ ያስኬዳል ባይ
ነኝ። ... ከዛ አልፎ ግን በተፈጠረው ልዩነት መነሻነት ፤ ከመጠን ባለፈ መከፋት ፣ መበሳጨትና ማዘን ፤ ብሎም
በሰዎች ላይ በጥላቻ መነሳሳት ፤ የሚኖሩበትን ዓለም ተለወዋጭነት አለመረዳት ወይም መካድ ነው።
Reply
•
KD HYPERLINK "http://www.danielkibret.com/2011/08/blog-post_12.html?
showComment=1313147788767"August 12, 2011 at 2:16 PM
Thank you Abatachin Danel.
God bless!!!.
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 3:56 PM
thanks dani emebete mariam atleyih
Reply
•
DawitAugust 12, 2011 at 4:09 PM
ሁላችንም የተሳልንባቸውን ስእሎቻችንን የወረስናቸው በገሀዱ አለም ከምንኖረው ማሕበረሰብ ነው፡፡ መጥፎም
ይሁን ጥሩ ስእል ሁሉም በአንድነት አብሮ አለ፡፡ ለመጥፎ ነገር ማነጻጸሪያው ጥሩ ነገር ስለሆነ ሰአሊዎቹ ሲስሉ
ወይንም ስንስል ጥሩውን ነገር ከተነጻጻሪው መጥፎ ብለን ከምንለው ሙሉ በሙሉ ነጥለን ስለምንስለውና የስእሉን
ጎደሎነት ስለማንረዳው ነው እህህ ወደሚለው መብሰልሰል የሚያደርሰን፡፡
መጥፎ የነበረ ነገር ጥሩ እነዲሁም ጥሩ የነበረ ነገር መጥፎ የሚሆነው ሁላችንም በገሀዱ አለም በሚኖረን የዘወትር
እንቅስቃሴ ነው፡፡ ለመጥፎውም ለጥሩውም ነገር ሁላችንም ባለድርሻዎች ነን ማለት ነው፡፡
እጅግ ድንቅ መጣጥፎችህ ሕሊናውስጥ ዘልቀው የሚገቡና አስተማሪ ናቸው፡፡ እውቀትህን እግዚአብሔር
ይባርክልህ፡፡
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 4:13 PM
አንዳንዴ ሳስበው ግን እኛ ሰውን መልአክ አድርገን መሳላችን ብቻ አይደለም ችግሩ የሰዎችም እንዳኖራቸው
ያለመገኘት ይመስለኛል አባቶቻቸን በጣም በሳል ናቸው በጸሎታቸው መጨረሻየን አሳምርልኝ አትቀርም ዛሬ እንዴት
ያለ ክርስቲያን የሆነ ሰው ነገ ሌላሆኖ ይገኛልና
Reply
•
DawitAugust 12, 2011 at 4:23 PM
ሁላችንም የተሳልንባቸውን ስእሎቻችንን የወረስናቸው በገሀዱ አለም ከምንኖረው ማሕበረሰብ ነው፡፡ መጥፎም
ይሁን ጥሩ ስእል ሁሉም በአንድነት አብሮ አለ፡፡ ለመጥፎ ነገር ማነጻጸሪያው ጥሩ ነገር ስለሆነ ሰአሊዎቹ ሲስሉ
ወይንም ስንስል ጥሩውን ነገር ከተነጻጻሪው መጥፎ ብለን ከምንለው ሙሉ በሙሉ ነጥለን ስለምንስለውና የስእሉን
ጎደሎነት ስለማንረዳው ነው እህህ ወደሚለው መብሰልሰል የሚያደርሰን፡፡
መጥፎ የነበረ ነገር ጥሩ እነዲሁም ጥሩ የነበረ ነገር መጥፎ የሚሆነው ሁላችንም በገሀዱ አለም በሚኖረን የዘወትር
እንቅስቃሴ ነው፡፡ ለመጥፎውም ለጥሩውም ነገር ሁላችንም ባለድርሻዎች ነን ማለት ነው፡፡
እጅግ ድንቅ መጣጥፎችህ ሕሊናውስጥ ዘልቀው የሚገቡና አስተማሪ ናቸው፡፡ እውቀትህን እግዚአብሔር
ይባርክልህ፡፡
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 4:52 PM
dane thanks egezer edmehin yarezmelen nurelen betam enakeberhalen from harar
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 4:59 PM
ትክክል ብለሃል፡፡የአሁኑም ሰው ሆነ የድሮው እንዲሁ ጓደኝኅ እንደሚያስበው እንደተናገረውም ነው ከዚህ
አስተሳሰብ መውጣት ይኖርብናል ባይ ነኝ፡፡ጥሩ አመንክዮ ነው
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 7:19 PM
«እና ጥፋተኛው እኔ ነኝ በለኛ» እ.በ.ጥሩ ነው፡፡ ምስጋና ያንስብሀል እንጅ አይበዛብህም፡ ግን ዳኒ ምስጋናውን
ንቃበት፣ ይበልጥ በርታ፡፡
TA,mekelle
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 7:43 PM
Nice article!!!!!!!!!. that was exactly how i were percived about you b/r you wrote about
MK. But now i understand that this was the image which i have created, not the actual
one!!!!!!!!!!!!!. God bless u
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 8:32 PM
enamasagenalane Dn danel
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 9:18 PM
praise to be God for giving you this kind of knowledge. you are a man of ethiopian ppl!!!
Reply
•
christina HYPERLINK "http://www.blogger.com/profile/09017664179607669869" wright
HYPERLINK "http://www.danielkibret.com/2011/08/blog-post_12.html?
showComment=1313175468636"August 12, 2011 at 9:57 PM
በስመአብ ዳኒ በጣም የሚኮረኩር ትንታኔ ነው ጓደኛህ ይበለውም አይበለው የነገርከን ግን ሺህ ጊዜ እራሳችንስ
እንዴት ነን ብለን እንድንመረምር ነው የሚያደርገው መቼም እኔ ባንተ ጽሁፍ ላይ የማገኘውን እውቀት ከትምህርት
ቤት ካገኘሁትም እየበለጠብኝ ነው ህይወትን በደንብ እያየኋት ነው ለማንኛውም ቃልህን ጠባቂ ያድርግልን መልካም
ጉዞ
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 10:14 PM
ውድ ወንድማችን ዲያቆን ዳንኤል! እግዚአብሔር ጸጋውን አብዝቶ ሰጥቶሃል።አሁንም የበለጠ ያብዛልህ።ባለፈው
ጽሁፍህ መንገድ እና ሕሊና በሚል ርእስ በታም አስተማሪ እና መካሪ የሆነ ጽሁፍ አስነብበኸን ነበር።ዛሬ ደግሞ
ሥእሎቻችን እጅግ የሚአስደንቅ ስሁፍ ነው።እንደስብከቶችህ ሁሉ ሁልጊዜም ስሁፎችህ ለአንባብያ እንግዳ
ናቸው።ሞት ሕንፃ ላሊበላ ኩለሄ እንግዳ እንዳለ ባለቅኔ።
እግዚአብሔር ይባርክህ
Reply
•
AnonymousAugust 12, 2011 at 11:50 PM
አንድ ሰው ዛሬ ያልሆነውን ነገ ሊሆነው እንደሚችል ሁላችንም ማመን አለብነን፡፡ ዳዊት ሰይፉ ከአ.አ
Reply
•
AnonymousAugust 13, 2011 at 1:11 AM
SELAM DN/DANEL "GOD BLESS YOU" AND THANK YOU
Reply
•
AnonymousAugust 13, 2011 at 2:58 AM
አስተማሪ ጽሁፍ ነው:: እግዚአብሄር ይባርክህ::
Reply
•
AnonymousAugust 13, 2011 at 7:51 AM
እግዚአብሄር ማስተዋልህን እና እጅህን ጨምሮ ይባርክ
እንዳለ ዘ አጋሮ
Reply
•
Abes FelekeAugust 13, 2011 at 10:03 AM
Dani, you make me remember one of my friend. I asked him four years ago why he
wasn't married yet? He replied that he couldn't find the right woman. I was like, what is
your dream woman? I asked. His right woman, according to his opinion, must be a
graduate from university, comes from a good family, a member of certain ethnic,
religious and orthodox christian, very beautiful inside and out, tall like he is, chocolate
color, and so on. He had so many lists, which I don't remember them all right now.
That was his picture of his future wife, which he couldn't find her and will not find that
kind of woman in the near future too. The guy is around late thirties and still single,
imagine. That is because of his imagination problem and too many predefined criterion
for one person to live with.
What makes me wonder is that himself, the guy, my friend doesn't fulfill some of those
requirements at all. How in the earth somebody wants to have such a list, which he
doesn't even have them.
Peace!
Reply
•
AnonymousAugust 13, 2011 at 10:16 AM
thank you
Reply
•
Birhan Ze-BeamanAugust 13, 2011 at 11:06 AM
በጣም ጥሩ ጽሁፍ ነው እግዚአብሔር ይስጥልን
አዳምና ሔዋን እንዴት ባለ ተድላ ደስታ አንዳች ሳይጎድልባቸው እየኖሩ እንዴት አዲስ በመጣ ምክረ ከይሲ ተሳሳቱ
?
ስህተት አላዋቂነት የሚስማማው ሥጋን ስለለበሱ ይህ ሆነ እንዲህ አደረጉ።
ሰውንም መረዳት የሚገባን እንዲህ ይመስለኛል ምን በጎ ቢሰራ ለበጎ ነገር ቀን ከሌሊት ቢተጋ የአዳም ልጅ የሄዋን
ፍሬ መሆኑን አለመዘንጋት ይህም እንዳልከው ጥቅሙ ለኛም ለሰውየውም ነው ምክንያቱም የምንችል በበጎ ስራው
እንዲተጋ ራሱን/ሰው መሆኑን/ እንዳይረሳ በምክረ ከይሲ እንዳይወሰድ እንንከባከበዋለን እንመክረዋለን እንገስጸዋለን
ለሰው መትረፍ የማንችል ደግሞ ቢያንስ እራሳችንን እንጠብቅበታለን ምክንያቱም ሰው መምርኮዝ ሸንበቆ መመርኮዝ
ነውና መሰበሩም ከርሱ አልፎ ለተመረኮዘውም ይተርፋልና። ሰው ሁሉ ሊሳሳት የሚችል ድቀት ክፋት የሚስማማው
ፍጥረት ነው ብለን የምናስብ ከሆነ በማንም ዉድቀት አንሰናከልም አንደነቅም እናዝንለት ይሆናል እንጅ።እናም
ኑሯችንን መጽሃፍ እንደሚለን በብልሃትና /የሚቀርቡልንን ነገሮች የምንችለውን ያህል እየመረመርን አካሔዶቻችንን
ሁሉ በተቻለ መጠን መስሎ ለሚገባ እድል የማይሰጡ በማድረግ/ በየዋህነት /ጠባቂ መላክ እንሁን ሳንል ምክንያቱም
መሆን አንችልምና ብንሞክረው ምናልባት የሰዎቹ መቀየር ሊያመጣብን ከሚችለው በላይ ሊያደክመን ሊጎዳን
ይችላልና/ ሊሆን ይገባል።
ለምሳሌ ከሰሞኑ ማኅበረ ቅዱሳን የስለላ ወይስ የሃይማኖት ድርጅት የሚል ደብዳቤ አየሁ ትንሽ እንዳየሁት ግን
እውነተኛነቱን ተጠራጠርኩት ምክንያቱም ደብዳቤው የተጻፈው በ 2003 ነው ግን ራስጌው ላይ መቀሌ ንዑስ
ማእከል ይላል እስከማውቀው ደግሞ ንዑስ ማእከል የሚለውን ስም መጠቀም የቀረ ይመስለኛል ታዲያ ለምን
እንዲህ ሆነ ብዙ መላምቶችን ማቅረብ ይቻላል አላማየ ስለዚያ ደብዳቤ ማብራራት አይደለምና ልተወው ግን
የቀረበልንን ነገር በትኩረት ብናጤነው የሚያሳየን ነገር ይኖራል እና ነገሮችን ሁሉ በትኩረት እንመርምር እላለሁ
ሌላው ይህንን ደብዳቤ የማህበሩን አሰራር ጠንቅቆ የሚያውቅ ሰው ቢያየው ከኔ በተሻለ ትክክለኛ ነው ወይም
አይደለም የሚያስብሉ መረጃዎችን ማውጣት ይችል ይሆናል እናም በነገሮች ላይ ያለን ትክክለኛ እውቀትም የራሱ
ሚና ይኖረዋል።
ነገር ግን በትኩረትና በእውቀት አይተንም 100% እውነቱን እንረዳለን ማለት አይደለም ማእከሉ ተሳስቶ ቢሆንስ
እንዲህ አድርጎ የጻፈው አልያም ተቀናብሮ ይሁንና ያቀናበረው ሰው ደግሞ በደንብ ተጠንቅቆ ፍጹም አስመስሎ
አዘጋጅቶት ቢሆንስ? እንዲያውም አንዳንዴኮ ባለቤቱ ራሱ የማያውቀው እውነት ውስጡ ይኖርና ከጊዜ በኋላ
ለሰዉም ለርሱም ሊገለጽ ይችል ይሆናል። በቀድሞው ሆነ ደም የተቃባ ሰው ደም ሲመልስ ሴት አትገደልም ይባል
ነበር አሉ ምክንያቱም ከማኅበረሰቡ ግንዛቤ አንጻር ደም ትመልሳለች ተብላ ስለማትጠበቅ። እናም አንድ ሰው ነው
ደም ለመመለስ ሄደና ደመኞቹ ቤት ገብቶ ወንዶቹን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ ሴቶቹን ትቶ ሄደ ይህን ካደረገ በኋላ
ቤተሰቡንም ሁሉ ይዞ ራቅ ወዳለ ሃገር ተሰደደ በስደቱም ኑሮ ተሳክቶለት ይኖር ጀመር። ግን ከተገዳዮች የአንዱ
ሚስት ነብሰጡር ነበረችና ወንድ ልጅ ወለደች ያም ልጅ ይህ ታሪክ እየተነገረው አደገ ባደገም ጊዜ ያባቱ ገዳዮች
ወዳሉበት ሃገር ሄዶ በእነርሱው ቤት በገበሬነት ተቀጥሮ ማገልገል ጀመር ሰዎቹ ቅጥረኛነቱን እስኪዘነጉት ድረስ
እጅግ ትሁት ታታሪ ብልህ የያዘው ሁሉ የሚሳካለት ሆነ እንዲህ እምነታቸውን ካገኘ በኋላ ግን አሳቻ ቀንን ፈልጎ
የአባቱን ገዳይ ብቻ ለብቻ ያዘው ታሪኩን ሁሉ ዘርዝሮ ከነገረው በኋላ ገድሎት ሄደ ከዚያ በኋላ ሴት ነብሰጡር
ከሆነች ትገደል ተባለ አሉ።ግን ይህም ቢሆን ችግራቸውን ይቀንስላቸው እንደሆን እንጅ አያጠፋውም ምክንያቱም
እርግዝናኮ በሰው ቀርቶ በሴትየዋ በራሷ እንዲያውም በምርመራ እንኳን የማይታወቅበት ደረጃ አለውና ታድያ
የሆዷን አለመግፋት አይተው ነብሰጡር አይደለችም ያሏት ራሱን ያልገለጸ ጽንስ ይዛ ቢሆንስ እናም አካሄድን ጥንቃቄ
ማድረግ ነገሮችን ሁሉ በጥንቃቄ በእውቀት መመርመር ከዚህ በላይ ያለውን ደግሞ ለአምላክ መተው ይገባል
እላለሁ።
ሌላው ግን ምናልባት የተቀየርነው/የተበላሸነው እኛው እራሳችን ብንሆንስ አንድ ወንድም ነበረ እጅግ የሚያስቀና
ስብእና ያለው ብዙውን ነገር ከሰው በላይ የሚፈጽመው ይህ ልጅ በበዓል ሃምሳ እንኳን ስጋ አይበላም ነበር ታዲያ
ለበለጠ ት/ት ተላከ ሲመለስ ግን በአርቡ ምድር ቁርስ እንብላ ማለት ጀመረ እኛስ እንደዚህ ወደ ታች አድገን ቢሆንስ
እንደ ዴማስ ተሰሎንቄ ባየንበት ዓይን እያየን ቢሆንስ ድሮ እንወደው የነበር ነገር አልዋጥህ ያለን።
ደግሞ በሌላ አቅጣጫ እንየውና ሰው አሳስቶ ሲስለን ዝቅ ሲያደርገን ብቻ ሳይሆን ከፍ ሲያደርገንም የለም እንደዚህ
አይደለሁም ብንልስ የተሳሳቱ ሰእሎች እንዳይፈጠሩ አይረዳም ? እርግጥ ሰሚው ለትህትና ነው እንዲህ ያለኝ ብሎ
የነገርነውን ላይቀበለን እንደሰቀለን ሊቀር ይችላል ግን እንዲህ እውነቱን ተናግረን ነገ ከነገ ወዲያ እውነቱን ቢረዳ
አልያም ባልጠበቀን ነገር ቢያገኘን እጅግ አይደንቀዉም።እዚህ ላይ ጓደኛየ የነገረኝ ተረት ትዝ አለኝ ቅምቡርስ ነው
አሉ መንደራቸው ማዶ ያለውን ተራራ ተሻግሮ ያሉ ሰፈሮች አንድ ግዳጅ ፈጽሞ እንዲመጣ ተላከ አሉ ተነሳና
መንገዱን ቀጠለ ግን ዳገቱን መውጣት ከበደው ዳጡ እንቅፋቱ አስቸገረው ቢሆንም ኳትኖ ኳትኖ ደርሶ ለመመለስ
የሚፈጀውን ያህል ጊዜ ተጠቅሞ ዳገቱን ወጣና አፋፉ ላይ አረፍ አለ ይሄኔ አሻግረው ያዩት ዘመዶች ግድጁን ፈጽሞ
የመጣ መስሏቸው አያ ቅምቡርስ እንኳን ደህና መጣህ አሉት እርሱ ግን መመለሴ አይደለም ገና እየሄድኩ ነው
አላቸው አሉ። እኛ ብንሆን ይሄኔ እንኳን ቀዳዳ አግኝተን እንኳን ራሳቸው ተሳስተውልንና ጎደሏችንን ከስሩ
አስተካክለን ከመታረም ይልቅ እንደኛ መንደር አስፋልት ተለጣጥፈን መስለን ለመቅረብ የምንጥር በሰው ያለን ቫልዩ
እጅግ የሚያስጨንቀን ዓለማዊያን ነንና መልሳችን ሌላ ይሆን ነበር።
አሁን አሁን ግን እኔን ያስመረረኝ ከዚህ ጉድፉን በምኑም በምኑም ለመሸፋፈን ከሚጥረው መስሎ አዳሪ የከፋ
ህጋዊም ባለቆብም ነኝ ጥርስና ቀንድ የቀረው አውሬ ሆኖ ከሰውም በላይ መላክ ነኝ የሚል የኛን ማልያ ለብሶ በኛው
ጎል ሊያስቆጥር የሚጥር ፈጣጣም ነው።
Reply
•
AnonymousAugust 13, 2011 at 2:56 PM
ተባረክ ዳኒ:: ግን እኮ ቀለም ተቀብተው የሚቀርቡም አሉ:: የነርሱ ያልሆነ ባህርይ ተከናንበው አብረውን የሚኖሩም
አሉ ከኛ ብቻ አይደለም:: ነብር ሳይሆኑ ነብር መስለው የሚኖሩትስ ዳኒ?? የተቸገርነው በዚህም ነው: አብሶ
በማህበራዊ ግንኙነት ወቅት:: ያነበቡትን; በፊልም ያዩትን ሰው ሆነው የሚኖሩ ነገር ግን በሆነ አጋጣሚ እውነተኛ
ማንነታቸው የሚወጣ ክፉ ሰዎች; ከኛ ግምትና ሃላፊነት ውጭ ናቸው:: ጉዋደኛህ በዚህ አቅጣጫም ያላስተዋለው
ያለ ይመስለኛል:: ተናዳጁ ጉዋደኛህ ደግሞ ያያቸውና የሚያውቃቸው ሰዎች የሊላ ሰው ባህሪ ተላብሰው
የሚጫወቱትን ወይም የሚኖሩትን ነገር ግን በዛ አጋጣሚ እውነተኛ ማንነታቸው የተገለጠ ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ::
በርታ ውድ የኢትዮጵያ ልጅ!!!!
Reply
•
tigist tirunehAugust 13, 2011 at 4:23 PM
I proud of you man !!!!!!!
keep it up...
Reply
•
AnonymousAugust 14, 2011 at 9:56 AM
ነፍሳቸውን በአብርሃም እቅፍ ያስቀምጥልንና አንድ ታላቅ የቤተ ክርስትያናችን ሊቅ አንድ ቀን ሲናገሩ የሰማሁት ትዝ
አለኝ
“ሰው በባህሪው መልአዊም እንስሳዊም ነው ታዲያ እንስሳዊ ባህሪው ያየለ ጊዜ እኔ አንበሳው እኔ ነምሩ ይላል
ልጁንም አውራሪስ ጎሹ አንበሳው እያለ ይሰይማል”
Reply
•
AnonymousAugust 14, 2011 at 11:24 AM
well- said Dane
Reply
•
Addis AAugust 14, 2011 at 6:56 PM
Nice
Reply
•
Mehari Gebremarqos HYPERLINK "http://www.danielkibret.com/2011/08/blog-
post_12.html?showComment=1313394296085"August 15, 2011 at 10:44 AM
What we know is the product of who we are, which is again the product of our culturally
conditioned minds, our anxieties, fears, expectations,...
Whenever we see things we see them "as something" based on who we are. Yet, because
we cling to this perception we are doomed to be deceived. That is what happened to
Dani's friend, who believed that the people are as he perceived them. Let alone the
profane things of the world, we even often formulate God based on our perceptions and
expect Him to be like us. We want Him to hate what we hate and love what we love.
Hence, even though he didn't say it in such context, Thomas Aquinas (13th century
Theologian and Philosopher) was right when he said "the known is in the mind of the
knower."
Reply
•
AnonymousAugust 15, 2011 at 11:13 AM
I wish God help you to create a person who advice you in your day to day activity ,as you
tried to advice us in our day to day life.
WUBSHET
Reply
•
EYOB OTSEAugust 15, 2011 at 2:18 PM
FACT THAT WE DON'T WANT TO ACCEPT.
Reply
•
AnonymousAugust 15, 2011 at 5:27 PM
Knowing Self? Part-1
mesi negn.
Reply
•
haqAugust 25, 2011 at 2:50 PM
oh.... wherever or whatever it is you have to accept what is really happening now, not
what you think. Moreover you have to keep on investigating what you hold, and be open
mind to accept the truth.
Truth is not what you think, or follow or hold it before, it is the fact and reality at the
moment.
It is a very nice article
Reply
•
የመስቀል ስጦታ October 23, 2012 at 7:53 PM
ማስተዋል ለምንችል ሰዎች ይህ ታሪክ ወይም ደግሞ የዉይይት ሰዓት ብዙ አስተምሮናል ... በጣም ነው
የማመሰገነዉ ማየት ያልቻልኩትን ነገር ዛሬ ለማየት በመቻሌ ፈጣሪ ይስጥልኝ