Professional Documents
Culture Documents
2009 Driver Training Study
2009 Driver Training Study
በዚህ ረገድ የከተማውን የትራንስፖርት አገልግሎት ውጤታማ ከማድረግ አኳያ የተጀመሩትን የፈጣን አውቶቡስ ትራንዚት
ፕሮጀክቶችን እንዲሁም በአሁኑ ወቅት በስራ ላይ የሚገኙትን የከተማ አውቶቡሶች፣ ሌሎች በዘርፉ የሚሳተፉ አዳዲስ
የመንግስት ተቋማትንና የግል የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ማህበራትን ማበራከትና የትራንስፖርት አገልግሎቱን
በማቀናጀት የሚፈለገውን ጠቀሜታ እንዲያስገኙ የማድረግ ስራ ያከናውናል፡፡ በተለይም የትራፊክ አደጋውን ለመቀነስና
ፍሰቱን ለማሻሻል በከተማዋ በሚገኙ የመንገድ መጋጠሚያዎችና አጠቃላይ የመንገድ መረቡ ላይ መጠነ-ሰፊ ጥናት
በማካሄድና ተገቢውን የማስተካከያ እርምጃ በመውሰድ የትራፊክ ፍሰቱንና ደህንነቱን ማሻሻል ከመቼውም ጊዜ በተለየ
ሁኔታ በጽ/ቤቱ ትኩረት የሚሰጣቸው ጉዳዮች ናቸው፡፡
ስለሆነም እነዚህንና ሌሎች የዘርፉን ቁልፍ ጉዳዮች በመለየት፣ የችግሮቹን መንስኤዎች በጥልቀት በመረዳት እና አገልግሎት
አሰጣጡን ደረጃ በደረጃ በማሻሻል የተሻለ የትራንስፖርት አገልግሎት እውን እንዲሆን ማስተባበሪያ ጽ/ቤቱ የመንገድ
ትራፊክ ማኔጅመንት ኤጀንሲ፣ የትራንስፖርት ባለስልጣን፣ የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፍቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን እና
የሸገር የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅትን በማቋቋም ወደ ስራ እንዲገቡ አድርጓል፡፡
ተቋማት መንግስት የነደፋቸውን ፖሊሲዎችንና ስትራተጂዎችን ከመፈጸም አኳያ ያላቸው ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ በዘርፉ
የተሰማሩት የመንግስት ተቋማትም ሆኑ የግል ተቋማት የማስፈጸም አቅማቸውን እንዲያጎለብቱና በትራንስፖርት ሴክተሩ
አመርቂ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ማስተባበሪያ ጽ/ቤቱ አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ሴክተሩንም ወደ ላቀ
ደረጃ ለማሳደግ ከግሉ ዘርፍ ጋር ትስስር በመፍጠር ተቀናጅቶ መስራት ወሳኝ ነው፡፡
ማስተባበሪያ ጽ/ቤቱ በስሩ ያቋቋማቸውን የተለያዩ የሥራ ክፍሎች ወደ ሥራ በማስገባት በትራንስፖርት ዙሪያ የሚታዩትን
በርካታ ችግሮች ለመቅረፍ ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ በጽ/ቤቱ ተቋቁመው ካሉት የሥራ ክፍሎች አንዱ
የትራንስፖርት አገልግሎት የሥራ ክፍል ነው፡፡ የሥራ ክፍሉ በትራንስፖርት ዙሪያ የሚታዩትን ችግሮች በጥናት በመፈተሽ
የመፍትሔ ሃሳቦችን ለሚመለከተው ባለድርሻ አካላት በማቅረብ የበኩሉን ድርሻ በማበርከት ላይ ይገኛል፡፡
2.የጥናቱ አስፈላጊነት
ይህን ጥናት ማካሄድ ያስፈለገበት ምክንያት በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኙ የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት ተገቢውን
አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችላቸውን አደረጃጀት በመፍጠር ብቃት ያላቸው አሽከርካሪዎችን ለማፍራት የሚያስችል
አሰራር መኖሩን፣ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩ ችግሮችን በመለየት የመፍትሄ አቅጣጫዎችን ለመጠቆም ጥናት
አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡
2.1.የጥናቱ ዘዴ
ይህ ጥናት የተካሄደው የመጀመሪያ ደረጃና ሁለተኛ ደረጃ መረጃዎችን በመሰብሰብ ሲሆን፡-
የመጀመሪያ ደረጃ መረጃዎች፡- እነዚህ መረጃዎች የተሰበሰቡት የስልጠና አገልግሎት እየሰጡ ከሚገኙ የአሽከርካሪ
ማሰልጠኛ ተቋማት ዳይሬክተሮች፣ ከክፍለ ከተማ መንገድና ትራንስፖርት ጽ/ቤት የስራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ ከተገልጋዩ
ህብረተሰብ (ሰልጣኞች) ጋር ቃለ መጠይቅ በማድረግ እና በቃሊቲ የአዲስ የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ ማዕከል
በአካል በመገኘት የነባራዊ ሁኔታ ቅኝት በማድረግ መረጃዎችንና የተለያዩ አስተያየቶችን በመሰብሰብ ሲሆን፣
የሁለተኛ ደረጃ መረጃዎች፡- ለአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ተሞክሮ ሊሆኑ የሚችሉ በፌዴራል ትራንስፖርት ባለስልጣን
የተዘጋጁ ማኑዋሎችና የአሰራር መመሪያዎች፣ የአሽከርካሪ ተሸከርካሪ ፍቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን የጥናት ሰነድ፣
የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፍቃድ አሰጣጥ የጥናት ሰነድ እንዲሁም የሌሎች አገሮች የአሽከርካሪ የስልጠና አሰጣጥ
ተሞክሮዎችን የሚዳስሱ ከድረ-ገጽ የተገኙ መረጃዎች ለጥናቱ የሁለተኛ ደረጃ የመረጃ ምንጭ ተደርገው ተወስደዋል፡፡
2.2. የጥናቱ ወሰን
ይህ ጥናት በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኙ የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት በዘርፉ ብቁ አሽከርካሪዎችን ለማፍራት
የሚያስችላቸው አደረጃጀት፣ አሰራርና በአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ የሚታዩትን መሰረታዊ ችግሮች ማጥናት እና የመፍትሄ
ሃሳብ መጠቆምን የሚያካትት ነው፡፡
2.3.የጥናቱ ዓላማ
አጠቃላይ ዓላማ
የዚህ ጥናት ዓላማ በአዲስ አበባ ከተማ አሽከርካሪዎችን ለማሰልጠን ፍቃድ ወስደው በሥራ ላይ የሚገኙ ተቋማት
በሥልጠና አሰጣጥ ዙሪያ በተጨባጭ ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ በመዳሰስ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩትን መሰረታዊ
ችግሮችና ክፍተቶች በመለየት የአገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል የሚያስችል የመፍትሄ ሃሰቦችን ማቅረብ ነው፡፡
ዝርዝር ዓላማ
የማሰልጠኛ ተቋማት የቢሮ አደረጃጀት ለተገልጋይና ለፈጻሚው በሚያመች መልኩ መደራጀቱን መገምገም፣
የስልጠና ቦታው ለሰልጣኞች ምቹ መሆኑን እና ለስልጠናው የሚያስፈልግ ግብዓቶች በበቂ ሁኔታ መሟላቱን
መገምገም፣
በተቋማቱ እየተሰጠ ባለው የንድፈ ሃሳብ እና የተግባር ስልጠና፣ የምዘና ሥርዓት ላይ ያሉ ክፍቶችን መለየት፣
በማሰልጠኛ ተቋማት የሚሰጡ ስልጠናዎች እንዳሉ ሆነው የንድፈ ሀሳብ እንዲሁም የተግባር ስልጠና በግላቸው
ሰልጥነው ለመፈተን ለሚፈልጉ ተገልጋዮች የስልጠና አገልግሎት ማግኘት የሚችሉበት የስልጠና አመራጮችን
ማስቀመጥ፣
የሌሎች አገሮች የአሽከርካሪ የስልጠና አሰጣጥና የምዘና ሥርዓት ተሞክሮዎችን በመዳሰስ ተገቢውን የማሻሻያ
ሃሰቦች ማቅረብ ነው፡፡
3. የማሰልጠኛ ተቋማት ነባራዊ ሁኔታ
የአንድን ተቋም አደረጃጀትና አሰራር ለማሻሻልና የአገልግሎት አሰጣጡን ተገልጋይ ተኮር ለማድረግ በነባሩ አደረጃጀት
የሚከናወኑ ተግባራትን እንዲሁም የነበሩን ዋና ዋና ችግሮችን መዳሰስ አስፈላጊ ነው፡፡ በከተማችን በአሁኑ ወቅት
የአሽከርካሪነት ፍቃድ ማውጣት ለሚፈልጉ ዜጎች የንድፈ ሃሳብና የተግባር ስልጠና እንዲሰጡ የብቃት ማረጋገጫ
ተሰጥቷቸው በማሰልጠን ላይ የሚገኙ 66 የሚሆኑ የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት ይገኛሉ፡፡ ማሰልጠኛ ተቋማቱ
ለከተማችን ነዋሪዎች የአሽከርካሪ የስልጠና ፍላጎት ለማሟላትና ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት ወደ ተግባር የገቡ
ቢሆንም በተጨባጭ ያለው ሁኔታ ሲታይ አብዛኞቹ በቀጣይ ትኩረት ሰጥተው ሊያስተካክሏቸው የሚገቡ በርካታ ጉድለቶች
አሉባቸው፡፡ በዚሁም መሰረት በአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽ/ቤት የትራንስፖርት
አገልግሎት የሥራ ክፍል ጥናቱን በማካሄድ ከየክፍለ ከተሞቹ ናሙና በመውሰድ በቁጥር 38 ከሚሆኑ የአሽከርካሪ
ማሰልጠኛ ተቋማት በተዘጋጀው መጠይቅ መሰረት ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የታዩ ክፍተቶች ዙሪያ መረጃዎችንና
አስተያየቶችን ለመሰብሰብ የተቻለ ሲሆን በቃሊቲ የአዲስ የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ ማዕከል እንዲሁም የተግባር
ሥልጠና የሚሰጥባቸው ሥፍራዎችም ላይ የመስክ ምልከታ በማካሄድ በተለያዩ ማሰልጠኛ ተቋማት የሚሰለጥኑ ሰልጣኞች
ከሰጡት በርካታ አስተያየቶች በአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ችግሮችና ቅሬታዎች መኖራቸውን በጥናቱ ለመዳሰስ ተችሏል፡፡
በአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማት በኩል ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ ያለባቸውን ችግሮች መፈተሽና ተቋማቱ
በተጨባጭ ያሉበትን ሁኔታ መዳሰስ በቀጣይ ችግሮቻቸውን ለይቶ ለመደገፍና በአገልግሎት አሰጣጡ የሚስተዋሉትን
ችግሮች ለመቅረፍ ስለሚያስችል ተቋማቱ ያሉበት ነባራዊ ሁኔታ እንደሚከተለው ተዳሷል፡፡
የተቋማት ዳይሬክተሮች የትምህርት ደረጃ እና ዓይነትን በሚመለከት በተለያዩ የሙያ ዘርፎች የተመረቁ ሲሆን ከነዚህም
መካከል በህግ፣ በማኔጅመንት፣ በኢኮኖሚክስ፣፣ በታሪክ፣ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው ናቸው፡፡ ከተቋማቱ ፋሲሊቲዎች ጋር
ተያይዞ ወንበሮች፣ጠረጴዛዎች፣ የማስተማርያ ክፍሎች፣ የመጸዳጃ ክፍሎች፣የስልጠና ማኑዋሎችና መጽሐፎች፣ የኮሚፒዩተር
ማለማመጃ ክፍሎች እና ወርክሾፖችን ማየት ተችሏል፡፡
3.2. የአሽከርካሪዎች የንድፈ ሀሳብና የተግባር አሰልጣኞች የትምህርት ደረጃ፣ ዓይነትና አፕሩቫል
የተቋማቱ የማስተማርያ ተሽከርካሪዎች በተቋማቱ ስም የተመዘገ የባለቤትነት መታወቂያ ደብተር (ሊብሬ ፣ሰሌዳ ቁጥር እና
በተቋሙ ስም ለስልጠና አገልግሎት ተብለው የተመዘገቡ መሆናቸውን ለመረዳት ተችሏል፡፡
ብዙ የመማሪያ ክፍልና ወንበር እንጠየቃለን ነገር ግን ለማስፈተን የሚፈቀድልን በጣም ጥቂት ተማሪዎችን ብቻ
ነው፣
በአንድ የተሽከርካሪ ምድብ ስልጠና ጨርሰን በሌላ ምድብ ሰልጣኞችን ተቀብሎ ለማሰልጠን ሁለት ወርና ከዚያ
በላይ (75 ቀን መጠበቅ አለብን፤ መመሪያው ጥናት ቢደረግበት)
ተማሪ ማሰልጠኛ ተቋም ገብቶ ሳይማር በራሱ ሰልጥኖ መፈተን የሚችልበት መመሪያ የወጣ እንደሆነ ሰምተናል፤
የተሳሳተ ሀሳብ ስለሆነ ቢታሰብበት፣
የህዝብ መንጃ ፍቃድ እያለን የአውቶ መንጃ ፍቃድ እንድናወጣ እንጠየቃለን፤ ትክክል አይደለም፣
የቤተ መጻህፍት የማስተናገድ አቅም በሰልጣኞች ልክ 25 እንዲሆን ባንገደድ ምክንያቱም አብዛኞቹ ሰልጣኞች
ስለማይጠቀሙ፣
ጥሩ ስነ ምግባር የሌላቸውን ተማሪዎች የሚቀጣ መመሪያ ቢኖር፤ አንድ አንድ ተማሪዎች የትራንስፖርትን
ባለስልጣን እንደ መመኪያ በማድረግ ያስፈራሩናል፤ ይቆጡናል፣
የቅበላ አቅም ላይ ችግር አለ፡፡በአንድ ተሽከርካሪ አሥር ሰልጣኝ ይፈቀዳል፡፡ ሰልጣኞች ስልጠና ካጠናቀቁ በኋላ
ከአሥሮቹ 2 ወይም 3 ሰልጣኞች የሚጠፉበት አጋጣሚ አለ፡፡ይህም የሆነበት ምክንያት ከረዥም ጊዜ በኋላ
ስለሚፈተኑ ነው፣
የንድፈ ሀሳብ ፈተና ላላለፉ ሰልጣኞች የማብቂያ ስልጠና ክለሳ የሚሰጡ መኖራቸው፣
የስነ-ምግባር ችግር ባላቸው አሰልጣኞች ላይ ምክር የሚለግሱና የማስተካከያ እርምጃ የሚወስዱ መኖራቸው፣
አሰልጣኞች ፈተና አለብን እያሉ የመቅረት ችግር አለ፤ የረጅም ጊዜ ቀጠሮ ይሰጡናል፣
አንዳንድ ማሰልጠኛ ተቋማት የተግባር ማሰልጠኛ ቦታ ከማጣት የተነሳ በግላቸው ቦታ ፈልገው የሚያሰለጥኑበት
ሁኔታ አለ፣
ሰልጣኞች የተግባር ልምምድ የሚያደርጉበት ቦታ የመሰናክል ቦታ ጭቃማ እና መኖሪያ አካባቢ መግቢያና መውጫ
አጠገብ በመሆኑ ብዙ ጊዜ ከነዋሪዎቹ ጋር ውዝግብ እንደሚነሳና ምቹ አለመሆኑ፣ በቂ የማለማመጃ ጠርዝ
አለመኖሩ እና ለአደጋ ተጋላጭ መሆኑ ፡፡ ለምሳሌ አንፎ እና ኪዳነ ምህረት አካባቢ፣
አሰልጣኝ ከሰልጣኙ ጋር ቀጠሮ ከያዘ በኋላ ጠፍቶ ሰልጣኙ በግሉ የሚሰለጥንበት አጋጣሚ አለ፣
የተግባር ስልጠና ላይ የቴክኒክ ብቃት ባልተሟላ አሽከረካሪ ማሰልጠን፡፡ለምሳሌ የእጅ ፍሬን፤ፍሬቻ፤ ክላክስ
በማይሰራ ተሽከርካሪ ስልጠና የሚሰጥበት ሁኔታ አለ፡፡ የተሽከርካሪ ፍተሻ አለ ሲባል ተሽከርካሪው ጋራዥ ይገባል፡፡
ተመልሶ ወዲያውኑ ይበላሻል፣
ሰልጣኙን የተግባር ስልጠና ሳያሰለጥኑ አቴንዳንስ የሚያስፈርሙ አሰልጣኞች አሉ፡፡ ሰልጣኝ ቆይቶ ሲመጣ የ 3
ቀን አንዴ የሚፈርምበት አጋጣሚ አለ፡፡
ለአካል ጉዳተኞች የአሽከርካሪነት ስልጠና መኖር አለበት፡፡ሰው እችላለሁ እያለ አትችልም በማለት የሰውን ሞራል
የሚሰብሩ አሰልጣኞች አሉ፡፡ አንድ አካል ጉዳተኛ የሆስፒታል የጤና ምርመራ አልፎ አካል ጉዳተኛ በመሆኑ ብቻ
መንዳት አይችልም የሚባልበት ሁኔታ አለ፣
አንዳንድ አሰልጣኞች ሰልጣኞቻቸውን ከተግባር ልምምድ በኋላ ሰልጣኙ ይችላል አይችልም ብሎ መከታተል
የለም፡፡ ሰልጣኙ በአቋራጭ መንጃ ፍቃድ እንዲያገኝ ያበረታታሉ፣
በአንዳንድ አሰልጣኞች ሰልጣኙ በአግባቡ ስልጠና ሳይሰለጥን ወደ ፈተና ግባ ማለትና ማስገደድ ይታያል፣
ብዙ ማሰልጠኛ ተቋማት አንድ ቦታ ላይ የተግባር ስልጠና ስለሚያሰለጥኑ ለብዙ ሰዓት ቆሞ መጠበቅ ፣ የቦታ
ሽሚያ አለ፡፡ አንፎ አካባቢ 11 ተቋማት በዛ ጠባብ ቦታ ላይ እንደሚያለማምዱ ለማየት ተችሏል፡፡ በተጨማሪም
አንፎ መሐል መንገድ ላይ የመሰናክል ልምምድ ለደረቅ ተሽከርካሪ ለማጅ መሆኑ ለሰልጣኞቹም ሆነ
ለአሰልጣኞቻቸው ምቹ አለመሆኑ እና ለአደጋ ተጋላጭ መሆኑ ታይቷል፡፡
በአንዳንድ ማሰልጠኛ ተቋማት የስነ-ምግባር ጉድለት ያለባቸው አሰልጣኞች አሉ፡፡ ሰልጣኙን አለማክበር፤ ፆታዊ
አድልዎ ማድረግ፣
የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችን አለመጠቀም፡፡ ለምሳሌ የተሟላ የተሽከርካሪ የተለያዩ ክፍሎችን ማሳያ ሞዴል ፤
በቪዲዮ የተደገፈ ምስል አለማሳየት፣
የንድፈ ሀሳብ ስልጠና ከምዝገባ ጀምሮ በ3 ወር ያልቃል ተብሎ ከ3 ወራት በላይ መጉላላት፡፡
ከፈተና በፊት ለተፈታኞች መረጃ አለመስጠት፤ ለምሳሌ - ፈተናውን ለመጨረስ የሚፈጀውን ሰዓት፤ የጥያቄ ብዛት፣
አሰልጣኞች በመቀራረብ ነው የሚሰሩት፡፡ የተቋማት አሰልጣኞች ከአዲስ የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ ተቋም
ፈተና ፈታኞች ጋር ልዩ ጥቅም ከመፈለግ የተነሳ እጅና ጓንት ሆነው የሚሰሩበት ሁኔታ አለ፡፡ተፈታኝ ከማሰልጠኛ
ተቋም ለፈተና ብቁ ነው ተብሎ ወደ አዲስ የአሽከርካሪዎች ብቃት ማረጋገጫ ተቋም ለፈተና ሲላክ የተግባር ፈተና
በሚፈተንበት ጊዜ ዛሬ አታልፍም፣ወድቀሃል ውረድ ፣የደህንነት ቀበቶ ካላሰርሽ በቃ ወድቀሻል የሚባልበት ሁኔታ
አለ፣
ተፈታኙ የተግባር ፈተና ላይ ስህተት የሰራበት ቦታ ሳይነገረው ወድቋል ተብሎ ይለጠፋል፡፡ ለዚህ ተጠያቂ የሚሆን
ማንም የለም፡፡ ተፈታኙ የተግባር ፈተና ላይ በትክክል ሰርቻለው በሚልበት ጊዜ ሰሚ ባለመኖሩ ለቀጣይ ፈተና
ብቻ ነው የሚቀርበው፣
አንዳንድ አሰልጣኞች የተቋማቸውን ሰልጣኞች ትተው ከሌላ ተቋም የመጣውን ሰልጣኝ የግል ጥቅም ከመፈለግ
የተነሳ ሰልጣኙን በማግባባት ለፈተና እናበቃለን ብለው የሚያሰለጥኑበት ሁኔታ አለ፡፡
4. የሌሎች ሀገራት ተሞክሮዎች
በአለማችን በስልጣኔ ከፍተኛ ደረጃ ከደረሱ ከተሞች መካከል እንግሊዝ፣ አሜሪካ፣ስዊድን፣ ጀርመን፣ኖርዌይ ተጠቃሾች
ናቸው፡፡ በእነዚህ ሀገራት የሚሰጠው የአሽከርካሪዎች የብቃት ማረጋገጫ ስልጠናና የምዘና ሥርዓት እንዲሁም የሚሰጡት
አገልግሎቶች በተመራጭ ቴክኖሎጂ የታገዙ በመሆናቸው ተገልጋዩ በቀላሉ በድረ-ገፆች መገልገል ይችላል፡፡ ዕጩ
አሽከርካሪዎች ለንድፈ ሀሳብ ፈተና የሚረዳቸውን መፅሓፍቶችን በቀላሉ ከድረ-ገፅ ማግኘት ይችላሉ፡፡
ከአሽከርካሪዎች የብቃት ማረጋገጫ ስልጠናና የምዘና ሥርዓት ጋር ተያይዞ የእንግሊዝ፣ አሜሪካ፣ ስዊድን፣ጀርመን፣ ኖርዌይ
እና የኬንያ ሀገራት ተሞክሮዎች ተወስደዋል፡፡
ስልጠናውን በማሰልጠኛ ተቋም የሚሰለጥን ሰልጣኝ ለንድፈ ሀሳብ ስልጠና የሚረዳው ማኑዋል ከስልጠና
ማዕከሉ፤ከማሰልጠኛ ተቋሙ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች፤ ከቤተ መጻሕፍት፤ ከመጻሕፍት መደብር እንዲሁም ከድረ-ገፅ ማግኘት
ይችላል፡፡
የንድፈ ሀሳብ ፈተና በኮምፒዩተር ላይ ተፈትኖ ውጤቱን ወዲያው ማወቅ ይችላል፡፡ ማንበብ ካልቻለ አሳማኝ ምክንያት
አቅርቦ የፈተና ጊዜ እንዲራዘምለት በመጠየቅ የቃል ፈተና ወይም በአስተርጓሚ ፈተና እንዲሰጠው ጥያቄ አቅርቦ መፈተን
ይችላል፡፡ የተግባር ፈተና የማሰልጠኛ ተቋሙ በሚያቀርብለት ተሽከርካሪ መፈተን ይችላል፡፡ ከዚህ ውጭ በአገሪቱ
ከሚገኘው የትራንስፖርት አስተዳደር በመከራየት እንዲሁም በግሉ ባመጣው ተሽከርካሪ መፈተን የሚችልበት አማራጭ
አለው፡፡
በስዊድን የአሽከርካሪዎች የብቃት ማረጋገጫ ፍቃድ ለ 2 ዓመት የሙከራ ጊዜ ይፈቀዳል፡፡በ 2 ዓመት የሙከራ ጊዜ ውስጥ
ከ3-4 ጊዜ የደንብ መተላለፍ ጥፋት ከፈጸመ እንደ አዲስ የንድፈ ሀሳብና የተግባር ፈተና እንዲወስድ የሀገርቷ ሕግ
ያስገድዳል፡፡
የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፍቃድና ቁጥጥር ባለሥልጣን የሱፐርቭዥን ቡድን በመመደብ የተቋማት የንድፈ ሀሳብ
እና የተግባር ስልጠና አሰጣጣቸውን በአካል ተገኝቶ እንዲገመግሙ ቢያደርግ ጥሩ ነው፣
ሰልጣኞች ግርታ እንዳይፈጠርባቸው ስልጠና ሳይጀምሩ የብቃት ማረጋገጫ ፈተና የሚወስዱበት ቦታ በቂ ግንዛቤ
ቢያገኙ፣
በንድፈ ሀሳብ ፈተና ብዙ ተፈታኞች ስለሚወድቁ የንድፈ ሀሳብ ፈተና ትኩረት ተሰጥቶበት ቢፈተሽ፣
የቴክኒክ ብቃታቸው ያልተረጋገጠና ችግር ያለባቸውን ተሸከርካሪዎች ለስልጠናና ለፈተና በሚያቀርቡ እንዲሁም
የሰልጣኝ ተሽከርካሪ ጥምርታን በመጠበቅ በማያሰለጥኑ ማሰልጠኛ ተቋማት ላይ ተከታትሎ ተገቢውን እርምጃ
መውሰድ፣
በማሰልጠኛ ተቋማት የሚሰጡ ስልጠናዎች እንዳሉ ሆነው በግላቸው በማጥናት የንድፈ ሀሳብም ሆነ የተግባር
ፈተና ለመፈተን ለሚፈልጉ ተገልጋዮች አገልግሎቱን ማግኘት የሚችሉበት ሁኔታ ቢፈጠር፣
ለዕጩ አሽከርካሪዎች የተግባር ስልጠና ከማእከል በተጨማሪ በተመረጡ መንገዶች ላይ ብዙ ርቀት የሚሸፍን
የአነዳድ ስልጠና እንዲሰለጥኑና የተግባር ፈተናውም በእነዚሁ መንገዶች ላይ በተመራጭ ቴክኖሎጂ በመታገዝ
የሚሰጥበት አሰራር ቢኖር፣
የተግባር ማሰልጠኛ ቦታዎች ለሰልጣኞች የሚመቹ እንዲሆኑ ሰፊና የትራፊክ ምልክቶች ያላቸው ቢሆኑ፣
ማጠቃለያ
በከተማችን የአሽከርካሪ ስልጠና አሰጣጥ፣ ብቃት ማረጋገጥና የፍቃድ አሰጣጥ አገልግሎቶች ዙሪያ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ
በመረዳት እና የሌሎች ሀገራት ተሞክሮዎችን በመለየትና ከከተማው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማጣጣም ለተገልጋዩ
ህብረተሰብ የሚሰጠውን አገልግሎት ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ተደራሽ በሆነ መልኩ በመስጠት የተጠቃሚውን ኅብረተሰብ
ፍላጎት ማርካት ወሳኝ ነው፡፡ ከከተማው ዕድገት ጋር ተያይዞ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ህብረተሰብ ቁጥርና ፍላጎት በከፍተኛ
ሁኔታ እየጨመረና አገልገሎቱ በተመራጭ ቴክኖሎጂ በመታገዝ የማይሰጥ በመሆኑ በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ የሚፈለገውን
ውጤት ለማምጣት አልተቻለም፡፡
በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ በስፋት የሚስተዋሉ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት እንዲቻል የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፍቃድና
ቁጥጥር ባለሥልጣን የአገልግሎት አሰጣጡ የሚሻሻልበት ሥራዎች ላይ ትኩረት ሰጥቶ ወጥ የሆነ የክትትልና ቁጥጥር
ስርዓት በመዘርጋት አገልግሎቱን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ እንዲቻል የታዩ ችግሮችን መነሻ በማድረግና የቁጥጥር ስርዓቱን
በማጠናከር የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል፡፡ በተለይ የአሽከርካሪ ማሰልጠኛ ተቋማትን የመፈፀም አቅም
በማሳደግ የዘርፉን ተቋማዊ አቅምን በመገንባት ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ ተቋማቱ ሙሉ አገልግሎት መስጠት ወደ
ሚችሉበት ደረጃ ማድረስ ያስፈልጋል፡፡
መረጃና አስተያየት የተሰበሰበባቸው የማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር