You are on page 1of 32

ገድለ ቅዱስ ቴዎድሮስ

መግለጫ
በቤተ ክርስቲያናችን የትምህርተ ሃይማኖት መሠረት የሆኑ ፵፮ የብሉይ ኪዳን ፣ ፴፭ የሐዲስ ኪዳን ፤ በድምሩ
፹፩ አሥራው መጻሕፍት አሉን ። ደግሞ የረቀቀውን የሚያጎሉ ፡ ሀይለ ቃል የሚተረጉሙና የሚያብራሩ
መጻሕፍተ ሊቃውንት ፤ መጻሕፍተ መነኮሳት የሚባሉ አሉ ።
ከነዚህም ቀጥሎ ጌታ ለቤተክርስቲያን ፤ በቤተ ክርስቲያንም አማካኝነት ለምዕመናን የሠጣቸውን
ፀጋዎች የሚገልጹ ገድል ፣ ተዐምር ፣ ድርሳን የሚባሉ መጻሕፍት አሉ ።
ገደል ማለት ምዕመናን ጌታን ተከትለው በስሙ የተቀበሉትን መከራ የሚገልጽ ሲሆን ፤ ተዐምር ደግሞ
በተጋድሎ ውስጥ ሳሉ አምላካቸው ያመኑትንና የተማሩትን ትምህርት እውነተኛነት ለመግለጽ ያደረገላቸውን
ተዐምራት የሚተርክ ነው።
ድርሳንም እንደዚሁ አንድ የእግዚአብሔር ሰው የፈጸመውን አገልግሎቱን በአጠቃላይ የሚገልጽ የዜና
ሕይወቱ መግለጫ ነው ።
ለእነዚህ ሁሉ መሠረታቸው ግን በሉቃስ ም ፲፬ ቁ ፳፮ ፡ ዕብራም ፪ ቁ ፬ እና ፱ ፤ እንዲሁም በልዩ ልዩ
የወንጌል ምዕራፎች የተገለጹት ናቸው ።
ከዚህም በላይ የገድል ፤ የተዐምርና የድርሳን መሠረታቸው የሐዋርያት ሥራ የሚባለው መጽሐፍ
ሲሆን ምንጫቸው በአጠቃላይ ያው ወንጌል ነው ።
ገድልንም ፣ ተዐምርንም ፣ ድርሳንንም የሚነቅፉ ቢኖሩ ሁኔታውን በትክክል ያልተረዱ ሰዎች ናቸው ።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ግን “እናንተን የተቀበለ እኔን ተቀበለ ፤ እኔን የተቀበለ
የላከኝን ተቀበለ” (ማቴዎስ ም ፲ ቁ ፵) በሚለው መሰረት ፤ እሱን አምላክ ብላ እንደተቀበለች ፤ እሱን ያመኑ
፤ ስለእሱ ዞረው ያስተማሩ ፤ በአደባባይ የመሰከሩ ፤ እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ እሱን ያገለገሉ ፤ በቀን በሌሊት
እሱን የሚያመሰግኑ ፤ ሐዋርያትን ፣ ነቢያትን ፣ ሰማዕታትን ፣ ጻድቃንን መላዕክትን በስሙ ትቀበላለች ።
ቅድስናቸውንም ታውቃለች ። ስለእነሱም የተጻፈውን ዜና ሕይወት ትቀበላለች ። ምዕመናንም እነሱን
እንዲመስሉ ፤ እነሱን መስለው እንዲያገለግሉ ፤ እነሱ ከደረሱበት ማዕረግም እንዲደርሱ ፤ በአምላካችን ስም
የፈጸሙት ተጋድሎ ወይንም ገድል ፤ እግዚአብሔር ያደረገላቸውን ተዐምራት ፤ የተሰጣቸውን ጸጋ ፣ ክብርና
ቃልኪዳን ለምዕመናን ታስተምራለች ። ይኽም የቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ገድል የተዘጋጀው በዚሁ
መሠረት ነው ።
ቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ፵ ዘመን በፈጀው ዘመነ ሰማዕታት ተብሎ በሚታወቀው ድዮቅልጥያኖስ
ባስነሳውና በፈጸመው በሰማዕታት የተጋድሎ ዘመን ውስጥ በመጀመሪያ የሚገኝ ሰማዕት ነው ። የምሥራቁ
ንጉስ ድዮቅልጥያኖስ ክርስቶስን ክዶ ፤ ለጣኦት ሰግዶ ፤ ቤተክርስቲያንን ዘግቶ ፤ የጣኦት ቤት ከፍቶ
በክርስቲያኖች ላይ የመከራ አዋጅ በአወጀ ጊዜ የመጀመሪያውን የመከራ ጽዋ ከጠጡትና ድል ካደረጉት
የአንጾኪያ ሰማዕታት ውስጥ ተቀዳሚዎቹ የቤተ መንግሥት ተወላጆች ነበሩ ። ቅዱስ ቴዎድሮስ በአንጾኪያ
ቤተ መንግሥት ሶስተኛ የትውልድ ዘርፍ ያለው የመኮንን ሲድራኮስ ልጅ ሲሆን አንዱ ከአባቱ ወገኖች ፣
ሁለተኛው ከእናቱ ወገኖች የተሰየመ ሁለት መጠሪያ ስም ያለውና ቴዎድሮስ በናድልዮስ በመባል የሚጠራ ነው

በዘመኑ በቴዎድሮስ ስም የሚጠሩ ሞክሼዎች ሶስት ሲሆኑ አንዱ ሊቀጳጳሳቱ ፣ ሁለተኛው ሊቀ
ሠራዊቱ ሲሆኑ ሶስተኛው እራሱ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነው ።
ቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ በዘመኑ በሃይማኖቱና በሰይፍ ሀገሩን ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር ከሰውም
የተመረጠ ሐያል ሲሆን ለሀገሩ ለአንጾኪያና ለክርስትና ሃይማኖት ብዙ ሥራ ሠርቷል ። ገድሉም ይኸውና
ለምዕመናን እንዲያመች በአማርኛ ተተርጉመሞ ቀርቧል ።
ቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ድዮቅልጥያኖስን ከመንግሥት አውርዶ ገላውድዮስን በማንገስ አመ
ፀኞችንም በመቅጣት በጊዜው ታላቅ ሥራ ሠርቷል ። ግን የእግዚአብሔር መልአክ ጊዜው ምዕመናን
በሰማዕትነት ሊከብሩበት ፤ የእግዚአብሔር ሃያልነቱና ከሐሊነቱ በልዩ ልዩ የሰማዕትነት አደባባይ እንዲገለጥ
ለድዮቅልጥያኖስ የፈቀደለት መሆኑን ስለገለጸለት ሰይፉን አስቀምጦና ውትድርናውን ትቶ በፈቃደ
እግዚአብሔር ወደ ሰማዕትነት ገብቷል ። በድንግልና ፤ በበጎ ምግባር ፤ በእውነተኛ ሃይማኖት ፤ በሰማዕትነት
ሕይወቱን መስዋዕት አድርጎ እንደ አምላኩ ተሰቅሎ ፤ በ ፻፶፫ ችንካሮች ተቸንክሮ ድል የነሳ ሃያል ሰማዕት
ሲሆን ንጉስ ቁስጥንጢኖስ የሮምን መንግሥት ለመያዝ ከጠላቶቹ ጋር ሲዋጋ በነበረበት ጊዜ በመንፈስ መጥቶ
የረዳው ፤ ጠላቶቹ በብዛት ከበው ባስጨነቁት ወቅት ከጠላቶቹ እጅ ያዳነውና ኋላም በዚያ ሥፍራ ላይ
የቁስጥንጥንያን ከተማ እንዲመሰርት ያዘዘው ፤ የጌታን መስቀል ለማውጣት እንዲተጋ መምሪያ የሰጠው ሃያሉ
ሰማዕት ቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነው ።
ንጉሥ ቁስጠንጢኖስም በቁስጥንጥንያ ካሰራቸው አብያተ ክርስቲያናት አንዱ በቅዱስ ቴዎድሮስ ስም
ያሰራው ስለሆነ ከቅዱስ ጊዮርጊስ በኋላ በስሙ ቤተክርስቲያን የተሰራለት ሃያሉ ሰማዕት ቅዱስ ቴዎድሮስ
እረፍቱ ጥር ፲፪ ሲሆን የሞክሼው የሊቀ ሠራዊት ቴዎድሮስ ደግሞ ሐምሌ ፳ ቀን ነው ።
ቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ እጅግ የተፈራ ሰው ስለነበረ ንጉሱ ድዮቅልጥያኖስ ውሎ ሲያድር ሌላውን
ሕዝብ እንዳያነሳሳበትና እንዳይቀሰቅስበት ስለፈራ በአስቸኳይ እንዲሞት በሰጠው ፍርድ ጥር ፲፪ ቀን ተሰቅሎ
ሲሞት ለአንጾኪያ ሰማዕታት ሁለተኛው ነበር ። በመጀመሪያ የሞተው ከቤተ ዘመዶቹ አንዱ የነበረውና
ለአንጾኪያ ሰማዕታት ቀዳሚ ሰማዕት የሆነው በንጉሡ ቀኝ ቆሞ ሳለ የንጉሱ የድዮቅልጥያኖስ የክሕደት
ደብዳቤ እንደደረሰው ደብዳቤውን በመቅደዱ ድዮቅልጥያኖስ ራሱ ሰይፉን መዝዞ በገዛ እጁ ጥቅምት ፱ ቀን
የገደለው የሰማዕትነትን አክሊል የተቀበለው ቀዳሚ ሰማዕት እስጢፋኖስ ነው ። እንግዲህ ሁለተኛው ጥር ፲፪
ቀን በሰማዕትነት አክሊል የተከለለው ቅዱስ ቴዎድሮስ ነው ። ቁስጠንጢኖስንም የረዳው በሰማዕትነት ከሞተ
በኋላ ነው ።
በመግቢያው እንደገለጽነው ሀገራችን ኢትዮጵያ ክርስቶስንና ቅዱሳኑን ተቀብላ መታሰቢያቸውን
በየመልኩ የምትፈጽም በመሆኗ ከተቀበለቻቸው ሰማዕታትም አንዱ ቅዱስ ቴዎድሮስ ነው ። በኢትዮጵያ
በቅዱስ ቴዎድሮስ ስም የተሰሩ ብዙ ቤተ ክርስቲያኖች ሲኖሩ አንዱ የየረር ተራራን ተንተርሶ በሚገኘው
ቀድሞ ባዶቄ ፤ አሁን ግምቢ እየተባለ ከሚጠራው ተረተር ላይ የሚገኘው ነው ። በኢትዮጵያ ልዩ ልዩ ታሪክ
ያላቸውና በትንቢትም የሚጠበቁ ሥፍራዎች አሉ ። ከነዚህም አንዱ የረር ቴዎድሮስ ሲሆን በየረር ዙሪያ ብዙ
ሥውራን ቅዱሳን ሰዎች ይኖሩበታል ። ኋላም ቴዎድሮስ የሚባል ሃይማኖታዊ ደገኛ ንጉሥ ቴዎድሮስ
ይነግስበታል እየተባለ ስለሚተረክ ቀደም ሲል በሰማዕቱ በቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ስም ቤተክርስቲያኑ
የተሰራው በዚህ ምክንያት ነው ይባላል ።
ቤተ ክርስቲያኑ የተቆረቆረው በንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ዘመን ነው ። ጽላቱ የመጣው ከወደ ቡልጋ
እንደሆነ ይነገራል። አምጭዎቹ ቅድመ አያቶቻችን የመጀመሪያውን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ታቦተ
ሕጉን በተለያየ ሥፍራ በመቃኞ እያረፉ ቢሞክሩም ፈቃደ እግዚአብሔር የሆነላቸው ብዙ ዓመታት የሃይማኖት
ተጋድሎ ከፈጸሙ በኋላ ጥንተ ስሙ ባዶቄ ይባል ከነበረው የአብርሃና አጽብሃ ቤተ መንግሥት ከነበረበት
ኮረብታ (የዛሬ መጠሪያው ግምቢ ከሚባለው) ላይ ጸንቶላቸው ቤተ ክርስቲያኑን በቅዱስ ቴዎድሮስ ስም
አንጸው ጽላቱን አሁን ከሚገኝበት ሥፍራ ካሳረፉ ይኸው ከ፻ ዓመታት በፊት ሕዝቡን አስተባብረው ያሰሩት
አባ መዝገቡ የሚባሉ ደገኛ አባት ነበሩ ። ከቤተ ክርስቲያኑ በስተምስራቅ ፪፻ ሜትር ከሚሆን እርቀት ላይ
ከንግሥት ዘውዲቱ ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት ከመሬቱ ውስጥ የከበሩ ማዕድናት ውጤቶችና ንዋዬ ቅድሳት
ለነገስታቱ በጊዜ ቀርበዋል ። ሥፍራው ለጎብኚዎችና ተማራማሪዎች አሁንም ምቹ ነው ።
የቀደሙ አባቶቻችን ልዩ ልዩ መጽሐፍትን ከልዩ ልዩ ቋንቋ እየተረጎሙ ወደ ኢትዮጵያ ሲያስገቡ
ከመረጧቸው አንዱ ገድለ ቅዱስ ቴዎድሮስ ነው ። መተርጎሙም እንዲያው ለለከንቱ አይደለም ። ከቅዱሳኑ
ገድልና እምነት ጽናት ፤ እግዚአብሔር ካረገላቸው ተዐምራት ምዕመናን እንዲማሩና ለሃይማኖታቸው ፣
ለሀገራቸው ፣ ለክብራቸው ፣ ለመብታቸው ፣ የሚደርስባቸውን መከራ ሁሉ እየታገስ ሥጋዊና መንፈሳዊ ክብር
፣ ሥጋዊና መንፈሳዊ መብት ፣ ታሪክ ያጎናጸፋቸውን ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታቸውንና ኢትዮጵያን
ሀገራቸውን እንዲጠብቁ ነው ። እኛም ግዕዝ እየደገደገ በመሄዱ ገድለ ቅዱስ ቴዎድሮስን ብዙ ሕዝብ
በሚሰማው በአማርኛ ቋንቋ ተርጉመን አቅርበነዋል ። ሀሳባችን ግን አሁንም ምዕመናን ከኃያሉ ሰማዕት
ከቅዱስ ቴዎድሮስ በናጽልዮስ ገድልና ትዕግሥት ትምህርት እንዲቀስሙ ፣ ከልዑል እግዚአብሔር አምላክ
በተቀባው ቃልኪዳን እየተማጸኑ ስሙን በመጥራት መታሰቢያውን በማድረግ እንዲጠቀሙ ነው ። እንግዲህ
ተተርጉሞ ግዕዝ ከአማርኛው ጋር በንጽጽር ታትሞ የቀረበ ስለሆነ ይህን አገልግሎት ለመፈጸም ላስቻለ
አምላካችን ምሥጋና እያቀረባችሁ የሰማዕቱን የቅዱስ የቴዎድሮስን ስምና የአምላኩን ስም እየጠራችሁ
አምላከ ቴዎድሮስ እርዳን እያላችሁ እየተማጸናችሁ ሐብቱን ፣ ፀጋውን ፣ በረከቱን ለማግኘት እንድትጥሩበት
ይሁን ። አምላከ ቅዱስ ቴዎድሮስ ይህን መጽሐፍ ለማስተርጎም ፣ ለመፃፍ ፣ ለማሳተም ደከሙትን ፤
ገንዘባቸውን ዕውቀታቸውን በዚሁ ሥራ ላይ ያዋሉትን ምዕመናንና ምዕመናትን ልዑል እግዚአብሔር በቸርነቱ
ይባርክ ። ሀገራችንን ኢትዮጵያን ፣ ኦርቶድክሳዊ ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን በምህረቱ ይጠብቅ አሜን።
አለቃ አያሌው ታምሩ
ጥር 1988
አዲስ አበባ

ገድለ ቅዱስ ቴዎድሮስ።


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱ አሐዱ አምላክ የቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ገድልና ምስክርነት በንጉሡ
በድዮቅልጥያኖስ ዘመን በአንጾኪያ ሀገር ስለክርስቶስ የተቀበለው መከራ ጥር በገባ በአሥራ ሁለት ቀን ።
ልመናውና በረከቱ ከእኛ ጋራ ይሁን ። ለዘለዓለሙ አሜን ።
ምዕራፍ አንድ
፩. ብቻውን ታላላቅ ድንቅ ሥራ የሠራ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን ።
፪. ልጁ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይክበር ይመስገን።
፫. ሕያው ማሕየዊ መንፈስ ቅዱስም ይክበር ይመስገን።
፬. ዛሬ የታወቀችው የታላቁ የቅዱስ ቴዎድሮስ መታሠቢያ ናት።
፭. ዛሬ የፈጣኑ የኃያሉ መታሠቢያ ናት።
፮. ዛሬ የቴዎድሮስ በናድልዮስ መታሠቢያ ተገለጠችልን።
፯. የአንጾኪያ ሰው የቤተ መንግሥት ተወላጅ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ነው።
፰. እግዚአብሔር ኃይልን ብርታትን ሠጠው የቁዝንና የአረሚን ነገሥታት አጠፋቸው።
፱. ሰይፉንም በመዘዘ ጊዜ ከፊቱ መቆም የሚቻለው አልነበረም።
፲. ለቤተ ክርስቲያን ለድሆች ለጦም አዳሪዎች ብዙ በጎነት ያደርግ ነበር።
፲፩. የአያቱ ስም ፋሲለደስ ይባላል የምሥራቅ ንጉሥ ልጅ ነው ።
፲፪. የምሥራቁ ንጉሥም በሞተ ጊዜ ስለመንግሥቱ ሕዝቡ እርስ በርሳቸው ተለያዩ ።
፲፫. ፋሲለደስም ሚስቱን ወንዶችንና ሴቶች ልጆቹን ከሠራዊቱም ጥቂቶቹን ይዞ ሔደ አንጾኪያ ሀገርም ደረሰ
፲፬. ከዚያም ተቀመጠ በቤተ ክርስቲያን አምሳል ግንብን ሠራ
፲፭. ለቤተ ክርስቲያን ፣ ለድሆች ፣ ለጦም አዳሪዎች ፣ ቤት ሠሪ ዘር ዘሪ ለሌላት ፤ እናት ፣ አባቱ
ለሞተበት ፤ ለእንግዳ ፣ ረዳት ለሌለው ብዙ በጎነት ያደርግ ነበር።
፲፮. ስለበጎ ሥራውም ንጉሥ ወደደው የአንጾኪያ ሕዝቡም ሁሉ ።
፲፯. ከብዙ ቀንም በኋላ ፋሲለደስን አመመው ።
፲፰. ንጉሡም ሊጎበኘው ወደሱ ሄደ ።
፲፱. ፋለደስም ንጉሡን ስለክርስቶስ ስም ልጆቼን አደራ ሠጥቼሀለሁ ጠብቃቸው አለው ።
፳. እግዚአብሔር በፋሲለደስ ጸሎት ሁላችንንም ይጠብቀን አሜን ።
ምዕራፍ ፪
፩. ፋሲለደስ ሞቶ ከነገሥታት መቃብርም ቀበሩት ።
፪. የንጉሥ ልጅ ነውና በሀገር ያሉ ሕዝቡም ነገሥታቱም አለቀሱለት ።
፫. ፋሲለደስ ሶስት ልጆች ወልዶነበር አንዲቱ ሴት ልጅ ነበረች ።
፬. የፋሲለደስ ወንዶች ልጆቹ ሁለት ነበሩ የአንዱ ስም ሲደራኮስ የሁለተኛው ጠልሜዎስ የእኅታቸው
ስምም ማርታ ነበር ።
፭. ከጥቂት ቀንም በኋላ በአባታቸው ርስትና ሀብት ተጣሉ።
፮. ለፍርድም ወደ ንጉሡ ሔዱ ።
፯. ንጉሥም አስታርቆ የአባታቸውን ገንዘብ አከፋፈላቸው።
፰. ስለ ገንዘባቸውም ብዛት እጅግ አደነቀ ።
፱. ለንጉሡም ሁለት ሴቶች ልጆች ነበሩት ።
፲. ንጉሥም አንዲቱን ለሲድራኮስ አጋባት ሁለተኛይቱንም ለጠልሜዎስ ። እኅታቸውን ማርታንም
ለታላቁ መኮንን ለሕርማኖስ አጋባት እሱም በንጉሡ በስተ ቀኝ ከሚቀመጡት አራተኛው ነው ።
፲፩. ሲድራኮስም ልጅ ወለደ ስሙን ቴዎድሮስ በናድልዮስ አለው ።
፲፪. ከሱም ቀጥሎ ሴት ወለደ ስሟም ራስንድያ አላት ።
፲፫. ጠልሜዎስም ልጅ ወለደ ስሙንም ገላውዴዎስ አለው።
፲፬. ከሱም ቀጥሎ ሴት ልጅ ወለደ ስሟንም ቴፋስያ አላት።
፲፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ከገላውዴዎስ በቁመት ከፍ ከፍ አለ ።
፲፮. ወንድሞቼ እስኪ አንድ ነገር ልጠይቃችሁ ።
፲፯. ቅዱስ ቴዎድሮስ ለምን በሁለት ስም ይጠራል ።
፲፰. ምክንያቱም እንዲህ ነው ።
፲፱. ሕፃን ሣለ ያየው ሁሉ ይወደው ነበርና ።
፳. በእናቱ ወገን ያሉት ዘመዶች ሲያቅፉት በእናቱ በኩል በአለው በአያቱ ስም ይጠሩታል ።
፳፩. የአባቱ ወገኖች በሚያቅፉት ጊዜም በአባቱ በኩል በአለው በአያቱ ስም ይጠሩት ነበር ።
፳፪. በዚህ ምክንያት በሁለት ስም ተጠራ ።
ምዕራፍ ፫
፩. ገላውዴዎስም ትምህርት ሊቀበል ከሚችልበት ዕድሜ ሲደርስ ።
፪. ሁለቱንም እንዲማሩ ለመምህር ሰጧቸው የነቢያትን መጽሐፍና ትርጓሜውን የክርስቶስንም ሕግ ማለት
ወንጌልን አስተማሯቸው ።
፫. ሁለቱን እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሆኑ እንዳያገቡ እንደ መላእክት ንጽሕናን እንደ ሐዋርያትም ድንግልናን
ገንዘብ አድርገው እንዲኖሩ ተማከሩ ።
፬. ጾምን ጸሎትን የሚወዱ ሆኑ ።
፭. ሥጋውን ደሙን ሊቀበሉ ወደ ቤተ ክርስቲያንም በሚሄዱበት ጊዜ ድሆች ፣ ጦም አደሮች ይመጣሉ
በመንገድም ይጠብቋቸዋል እነሱም ግዳጃቸውን ይፈጽሙላቸዋል ፤ የተራቆቱትን ያለብሷቸዋል ፤
ለተራቡትም ምግብ ይሰጧቸዋል ፣ያጠጧቸዋል ፤ የተጠሙትንም የወደዱትን ሁሉ ይሠጧቸዋል ።
፮. ቴዎድሮስ በናድልዮስ ጭፍሮቹን ይዞ አራዊትን ለማደን ይወጣ ነበር አንበሳም ቢያገኝ በአንድ ጊዜ
ይገድለዋል ።
፯. አንድ ቀንም ለማደን ሲወጣ ሰይጣን ያደረበት ታላቅ ዘንዶ አገኘ ።
፰. ዘንዶውንም በአየው ጊዜ ፈረሱን እያኮበኮበ ሔደ ።
፱. ዘንዶውም ቴዎድሮስ በናድልዮስን በአየው ጊዜ አሥር ክንድ ያህል ራሱን ከመሬት ከፍ አደረገ በቁጣም
ራሱን ነቀነቀ ምላሱንም አውለበለበ ።
፲. የቴዎድሮስ በናድልዮስ ፈረስ ግን ከፍርሃት የተነሣ ወደ ዘንዶው መሄድን እንቢ አለ ።
፲፩. ያንጊዜንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላት ።
፲፪. አትፍራ ጽና በርታ እኔ ለዘለዓለም ከአንተ ጋር ነኝ አለው ።
፲፫. ያንጊዜም ቴዎድሮስ በናድልዮስ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ብሎ በሥላሴ ስም
በመስቀል ምልክት በፈረሱ ላይ አማተበና ሒድ ይህን ዘንዶ አትፍራ አለው ።
፲፬. ያንጊዜም ፈረሱ ወደ ዘንዶው ገሠገሠ ቴዎድሮስ በናድልዮስም ጦሩን ወረወራት ።
፲፭. የእግዚአብሔር መልአክም ፍላፃውን ከዘንዶው አጣበቃት ዘንዶውም ሞተ ።
፲፮. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሆይ ሰላሜ ከአንተ ጋር ይሁን ለመንግሥተ ሰማያት
ምስክር ትሆናለህ አለው ።
፲፯. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይህን ተናግሮ ወደ ሰማይ ዓረገ ።
፲፰. ያንግዜም ሰይጣን በሚያስከፋ መልክ ከዘንዶው ወጣ ጽሕሙ ረጅም የራስ ጠጉሩም የተከፈለ ዓይንም
የእሳት ፍህም የመሰለ ነበር ።
፲፱. ቴዎድሮስ በናድልዮስንም ከቦታየ አስወጣሀኝ አንተ ልታሸንፈኝ ነውን አለው ።
፳. ከዛሬ ጀምሮ ወዮልህ አዳምን ከገነት እንዲወጣ ያደረግሁት እኔ አይደለሁምን ።
፳፩. እኔ ቃየልን ወንድሙን አቤልን እንዲገድለው ያደረግሁት እኔ አይደለሁምን ።
፳፪. ሄሮድስ ዮሐንስ መጥምቅን እንዲገድለው ያደረግሁት እኔ አይደለሁምን ።
፳፫. እኔ ሊቀ ሐዋርያት ጴጥሮስን ጌታውን እንዲክድ አደረግሁት።
፳፬. ይሁዳን ከአይሁድ ጋራ እንዲማማል ያደረግሁት እኔ አይደለሁምን ክርስቶስን እንዲሰቅሉት እጁን እግሩን
እንዲቸነክሩት ለማድረግ ።
፳፭. አንተንም እንደ አምላክ እንዲሰቅሉህ አደርጋለሁ ።
፳፮. ይህንም ተናግሮ ሰይጣን የእሳት ነበልባል መሰለና ጠፋ ።
፳፯. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሔደ ከፈረስ ላይም ወረደ ፊቱንም መልሶ እጁን እንደ መስቀል ዘርግቶ ጸለየ
ይህንን መዝሙርም አነበበ እንዲህም አለ አቤቱ በረድኤት ስለ ተቀበልኸኝ አመሰግንሃለሁ።
የጠላትም መዘባበቻ አላደረግኸኝምና አቤቱ ፈጣሪየ ወደ አንተ ጮህሁ አንተም አዘንህልኝ (ራራህልኝ)
አቤቱ ሰውነቴን ከመቃብር (ከሲኦል) አወጣሀት ።
ወደ ጉድጓድ ከሚወርዱም ለይተህ አዳንኸኝ ።
ወዳጆቹ (ጻድቃኑ) ለእግዚአብሔር ዘምሩ ቅዱስ ስሙ ሲጠራም አመስግኑ (ስገዱ)
ከቁጣው መቅሠፍት ከፈቃዱም ሕይወት ይመጣልና ።
ማታ ልቅሶ ጧትም ደስታ ይሰማል ። እኔ በተድላ ደስታየ ለዘለዓለም አልታወክም ብየ ነበር ።፡
አቤቱ በፈቃድህ ለሕይወቴ ብርታትን ስጣት ።
ፊትህን መለስክ ደነገጥኩ ።
አቤቱ ወደ አንተ ወደ አምላኪየ እጮሀለሁ እማልዳለሁ።
ወደ ጥፋት ብወርድ የኔ ደም ምን ግዳጅ ይፈጽማል ።
መሬት ያምንሀልን ቸርነትህንስ ይናገራልን ።
እግዚአብሔር ሰማኝ ይቅር አለኝ እግዚአብሔር ረዳቴ ሆነኝ ኃዘኔን ለወጥክ ደስ አሰኘኸኝ
የኀዘን ልብሴን ቀደድክ ደስታንም እንደዝናር አስታጠቅኸኝ ።
መከበሪያዬ ሆይ ለአንተ እዘምርልህ ዘንድ አላደነግጥም ። አቤቱ ፈጣሪዬ ሆይ ለዘለዓለም ለአንተ እገዛልሀለሁና

ጸለየ ሰገደ እግዚአብሔርንም አመሰገነው ።
ምዕራፍ ፬
፩. ወደ አንጾኪያም ሀገር በገባ ጊዜ ወሬው በዚያ ሀገር ውስጥ ተሰማ ።
፪. ሕዝቡም ያደረገውን ሊያዩ ወጡ ።
፫. ያንንም ዘንዶ በአዩት ጊዜ አደነቁ በሠራው ድንቅ ሥራ ሁሉም አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ።
፬. የዚያም ዘንዶ ርዝመቱ ፳፭ ክንድ ነበር ውፍረቱም ክንድ ሙሉ ነበር ጎኑም ክንድ ሙሉ ነበር ።
፭. ንጉሡም ቴዎድሮስ በናድልዮስን አከበረው።
፮. በሠራዊቱ ሁሉ ላይ የተጋዳዮች አለቃ አድርጎ ሾመው።
፯. ከዚህ በኋላ ንጉሡ ሞተ ።
፰. የገላዴዎስንም አባት ጠልሜዎስን ንጉሥ አደረጉት ።
፱. ያንጊዜም ቴዎድሮስ በናድልዮስ ከጥቂት ሠራዊት ጋር ወደ ጦርነት ሔደ ቁዝን አረሚን አጠፋቸው ።
፲. በጦር ሜዳ የቴዎድሮስ በናድልዮስ ልማዱ እንዲህ ነበር ።
፲፩. ወደ ጦርነት ውስጥም በገባ ጊዜ እንዲህ ይል ነበር ። እኔ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነኝ በጌታየ በኢየሱስ
ክርስቶስ ኃይል ለአጠፋችሁ መጥቻለሁ ።
፲፪. ድምጹንም በሰሙ ጊዜ ይሸበሩ ነበር ።
፲፫. በሚዋጋበት ጊዜ በፊቱ መቆም የሚቻለው አልነበረም።
፲፬. አረሚና የቁዝ ንጉሥም በላዩ ተማከሩ።
፲፭. ከዚህ ሰው ጋር ብንዋጋ ልናጠፋው አንችልም ።
፲፮. ነገር ግን ከእኛ እያንዳንዳችንን ሊወጋ በመጣ ጊዜ እንዲህ እናድርግ ።
፲፯. የቁዝን ንጉሥ ሊወጋ ሲመጣ የአረሚ ነገሥታት በሌላ መንገድ ይሒዱና ሀገሩን ወግተው ያጥፉ ።
፲፰. የአረሚን ንጉሥ ለመውጋት ሲመጣም የቁዝ ንጉሥ በሌላ መንገድ ይሒድና ሀገሩን ወግቶ ያጥፋ ብለው
ተማከሩ ።
፲፱. የቁዝና የአረሚ ሰዎች ግን እንደ አንበጣ ብዙዎች ናቸው ።
፳. የቁዝ ንጉሥ ጠልሜዎስ ወደ ሚባለው ወደ ሮም ንጉሥ አሁን እንዋጋ ብሎ ላከ ።
፳፩. የሮም ንጉሥ ጠልሜዎስም በዚህ ነገር ተስማማ ።
፳፪. የቴዎድሮስ በናድልዮስ አባት ሲድራኮስና የገላውዴዎስ አባት ጠልሜዎስ ከአማካሪዎቻቸውና ከሮም
ታላላቅ ሰዎች ጋራ ተማከሩ የሠራዊቱን ዉጥር ቆጠሩ ቁጥራቸውም ሰባት መቶ ሺህ ሆኖ ተገኘ።
፳፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ከነሱ ሁለት መቶ ሺህ ወሰደ ።
፳፬. ለገላውዴዎስ አራት መቶ ሺህ ሠጠው ።
፳፭. እሱ አረሚን ሊወጋ ሔደ ።
፳፮. ገላውዴዎስም የቁዝን ንጉሥ እንዲወጋ አደረገ ።
ምዕራፍ አምስት
፩. የሮም ንጉሥም የቁዝ ነገሥታትን ይወጋቸው ዘንድ ገላውዴዎስን ላከው ።
፪. ገላውዴዎስ አሸነፈ የቁዝን ንጉሥ ልጅ አግራዶስንም ማረከው ።
፫. የቁዝ ሠራዊትም ወደ ንጉሥ ተመልሰን ልጅህ ተማረከ ብንለው ሁላችንንም ይፈጀናል አግራዶስን
ልንመልሰው እንችል እንሆ ገላውዴዎስን እንከተለው ያለዚያ ሁላችንም እዚያው ብንሞት ይሸለናል ብለው
ተማከሩ ።
፬. ሊዋጉ ሔዱ ገላውዴዎስንም በጦርነቱ ውስጥ ያዙት በዚች ቀን ከሮምም ከቁዝም ብዙ ደም ፈሰሰ ።
፭. ገላውዴዎስንም ወደቁዝ ንጉሥ ወስደው ሮማውያን ልጅህን አግራዶስን ወሰዱት እኛም ስለ ልጅህ ፈንታ
የንጉሣቸውን ልጅ አምጣንልህ አሉት ።
፮. ያንጊዜም ንጉሡ ሚስቱን ንግሥቲቱን ጠርቶ የሮሙን ንጉሥ ልጅ ውሰጂ ልጃችንን ይመልስልን ዘንድ ዕርቅ
እስከናደርግና ወደ አባቱ እስክንመልሰው ድረስ በሚገባ ጠብቂው አላት ።
፯. የሮም ሰዎችም ከጦር ሜዳ ተመልሰው የቁዝን ንጉሥ ልጅ ማርከን አመጣንልህ እነሱም ተከትለው ልጅህን
ገላውዴዎስን ከእኛ ነጥቀው ወስደውታል አሉት ።
፰. አባቱ ንጉሥም አዘነ ንግሥት እናቱም አዘነች ። የአንጾኪያም ሰዎችም ሁሉ አዘኑ የተራቡትን ያጠግብ
ነበርና ።
፱. ገላውዴዎስ ከነሱ ዘንድ ሣለ አንዱ አንዱን ሊበድለው የሚችል የለም ነበር ።
፲. ደግሞም ብዙ ደጋግ ሥራ ይሠራላቸው ነበር ።
፲፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም የአረሚን ነገሥታት ወግቶ ጨርሶ አጥፍቷቸው ወደ አንጾኪያ ተመለሰ ።
፲፪. የሀገሩም ሰዎች አዝነው አገኛቸው ወደ ንጉሡም ገብቶ በአረማውያን ሀገር በሰልፉ ውስጥ የሆነውን ሁሉ
ነገረው ።
፲፫. ንጉሥም ንግሥቲቱም ሕዝቡም አዝነው ተክዘው በአያቸው ጊዜ ።
፲፬. ቴዎድሮስ በናድልዮስ አንተ ንጉሥ ንግሥቲቱም ሕዝቡም አዝናችሁ አያችኋለሁ በምን ምክንያት ነው
አለው ።
፲፭. ንጉሡም ወንድምህን ገላዴዎስን የቁዝ ሰዎች ስለያዙት ነው አለው ።
፲፮. እሱም አትዘኑ ወንድሜን ገላውዴዎን እኔ በጌታየ በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል አመጣዋለሁ አላቸው ።
ምዕራፍ ስድስት
፩. እንግዲህ ተመልሰን የቁዝ ሰዎች ገላውዴዎስን እንደያዙትና ወደ ሀገራቸው እንደወሰዱት እንናገር ።
፪. ንግሥቲቱና ልጅዋ ግን ገላውዴዎስን በአዩት ጊዜ ደም ግባቱንና በላዩ የተሣለውን ብርሃን እጅግ አደነቁ ።
፫. ንግሥቲቱም ንጉሡን ልጅህን እንዲያገባ ለንጉሡ ልጅ ልትሠጠው ልጃችንንም እንዲመልስልን ወደ አባቱ
ብንልከው እወዳለሁ ከእንግዲህ ወዲያ እነሱም አይውጉን እኛም አንወጋቸውም አለችው ።
፬. ንጉሡም አንቺ ሄደሽ ንገሪው አላት ።
፭. እሷም ሔዳ ይህን ነገር ለገላውዴዎስ ነገረችው ።
፮. ገላውዴዎስ መልሶ እንዲህ አላት እኔ አላገባም ጋብቻውን ትቼ ራሴን ለክርስቶስ ሠጥቻለሁና ።
፯. ንጉሡም ገላውዴዎስን ጠርቶ እንዲህ አለው ደብዳቤ ጻፍና ወደ አባትህ ወደ ንጉሥ ላክ እሱ ልጃችንን
አግራዶስን እንዲጠብቀው ። እኛ አንተን እንደጠበቅንህ እስክንልክልህ ድረስ ልጃችንን ይመስልንናል ።
፰. ዳግመኛም ወደ አባትህ ላክ ቴዎድሮስ በናድልዮስን ወደኛ እንዲልከው ዜናውን ጀግንነቱን ሰምቻለሁና
ላየው እሻለሁ ።
፱. ገላውዴዎስም በእጆቹ እንዲህ ብሎ ጻፈ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
እግዚአብሔር የአባቴን የጠልሜዎስን መንግሥት ያጽና የእስራኤልን ነገሥታት የዳዊትን የሰሎሞንን
የሕዝቅያስን መንግሥት እንደ አፀና ።
፲. አባቴ ደስ ይበልህ እኔ በሕይወት አለሁና ።
፲፩. ደግሞም እዘን ተክዝ እኔ በአረማውያን ንጉሥ እጅ ነኝና ።
፲፪. እኔን በመልካም ይዞኛል አንተም ልጁን በመልካም ያዘው ።
፲፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስን ንጉሥ ሊያየው ይሻል ።
፲፬. ገላውዴዎስ ይህን ከጻፈ በኋላ ደብዳቤውን ለቁዝ ንጉሥ ሰጠው ።
፲፭. ንጉሥም አገልጋዮችን ደብዳቤውን አሲዞ ላከ ።
፲፮. የመልእክተኞቹም ስማቸው ሊወንድዮስና በንግሎስ ይባል ነበር ።
፲፯. ወደ አንጾኪያም ከተማ ደርሰው ደብዳቤውን ለንጉሥ ጠልሜዎስ ሠጡት ።
፲፰. በልጁ በገላውዴዎስ እጅ የተጻፈውን ደብዳቤ በአየ ጊዜ ፍጹም ደስታ ደስ አለው እግዚአብሔርንም
አመሰገነው ።
፲፱. ንግሥቲቱም ደስ አላት አገልጋዮቹም ደስ አላቸው በሀገሩም ውስጥ ያሉ ሰዎችም ሁሉ እስከ ሰባት ቀን
ፍጹም ደስታ ደስ አላቸው ለሕዝቡ ግብር አድርጉ ።
፳. ለድሆች ልብሳቸውን አለበሳቸው ለጦም አደሮችም ምግባቸውን ሰጣቸው ለእያንዳንዱም
የሚያስፈልጋቸውን ሰጣቸው።
፳፩. እነዚያን መልእክተኞችንም ከቴዎድሮስ በናድልዮስ ጋር አገናኛቸው ።
፳፪. አንድ ቀንም በመካከላቸው ጭውውት በተደረገ ጊዜ መልእክተኞቹ ቴዎድሮስ በናድልዮስን እንዲህ አሉት

፳፫. አለቃችን ሆይ እኛም ሌሎች የንጉሥ ሠራዊት ገላውዴዎስን ስንጠብቀው ሳለን በሌሊት ብርሃን ከሰማይ
ሲወርድ አይተናል ።
፳፬. አሁንም ሕጋችሁ ሥርዓታችሁ ምን እንደሆነ ትነግረን ዘንድ እንሻለን ።
፳፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ብልህ መጻሕፍትን አዋቂ የሆነ ስሙ አግልስቲኖስ የተባለ አንድ ቄስ አመጣ ።
፳፮. ለእነዚህ ለመልእክተኞች የክርስቶስን ሕግ ንገራቸው አለው ።
፳፯. የነቢያትን የሐዋርያትን መጽሐፍት ከነትርጓሜያቸው ስለ ክርስቶስ የሆነውንም ነገር ሁሉ
አስተማራቸው ።
፳፰. መልእክተኞችም ተነሥተው ለቴዎድሮስ በናድልዮስ እጅ ነሡ ።
፳፱. በክርስቶስ አምነናልና የሚያጠምቀን የክርስቶስን ሥጋውን ደሙን የሚያቀብለን ካህን አምጣልን አሉት ።
ምዕራፍ ሰባት
፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወደ ንጉሥ ሔዶ ይህን ነገር ነገረው ።
፪. ንጉሥም እነዚህን ሰዎች ተቀብላችሁ አጥምቋቸው ብሎ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ አባ ቴዎድሮስ ላከ ።
፫. ሊቀ ጳጳሳቱም ፵ ቀን እንዲጾሙ አዘዛቸው በየጊዜው በየሰዓቱ ጸሎት አታቋርጡ የኃጢአታችሁንም
ሥርየት ለምኑ ጾማችሁም እስኪፈጸም ሥጋ አትብሉ ብሎ አዘዛቸው ።
፬. ፵ቀን ከጾሙ በኋላም አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዲያጠምቃቸው
አግልስቲኖስን አዘዘላቸው ።
፭. አግልሲቲኖስም አጠመቃቸው የክርስቶስን ሥጋውን ደሙን አቀበላቸው ።
፮. ንጉሥም መልካም ነገር አደረገላቸው በሁለት ሀገሮችም ላይ ሾማቸው ።
፯. እነሱም ጾምንና ጸሎትን የሚወዱ ለድሆች ለጦም አዳሮችም ምጽዋትን የሚሠጡ ሆኑ ።
፰. በዲዮቅልጥያኖስም ዘመን ሰማዕት ሆኑ ስለ ክርስቶስም ሰውነታቸውን አሣልፈው ሰጡ ።፡ ቴዎድሮስ
በናድልዮስ ሰማዕትነትን በተቀበለ ጊዜ ።
፱. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሄደ የቁዝ ሀገር ንጉሥ ከተማ ወደ ሆነችው ወደ ጠርሴስ ሀገር ደረሰ ።
፲. ሊቀ ጳጳሳት ቴዎድሮስም አብሮት ሄደ ።
፲፩. ወደ ሀገርም በቀረበ ጊዜ ለቁዝ ንጉሥ ነገሩት ቴዎድሮስ በናድልዮስ መጥቷል አሉት ።
፲፪. ያንጊዜም በከተማው ያሉት ሕዝብ ሁሉ ቴዎድሮስ በናድልዮስን ሊያዩ ወጡ ።
፲፫. ወደ ንጉሥ ቤት ለመግባት በመንገድ ሲሔድም ሕዝቡ ቴዎድሮስ በናድልዮስን ሊያዩ ወደሰገነት ወጡ ።
፲፬. ከሕዝቡም ብዛት የተነሣ ፎቅ ቤቶች ከወጡባቸው ሰዎች ጋር ወደቁ ።
፲፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወደ ንጉሥ ገባ ።
፲፮. ንጉሥም ቴዎድሮስ በናድልዮስ አንተ ነህን? አለው እሱም አወን አለው ።
፲፯. ንጉሥም እኔ ኃይልና ብርታት እንደ አለህ ዝናህን ሰምቻለሁ አለው ።
፲፰. አሁንም የኃይልህን ጽናት ልታሳየኝ እሻለሁ አለው ።
፲፱. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ኃይልና ብርታት የክርስቶስ ነው አለው ።
፳. ንጉሥ ዕወቅ እኔ በጦርነቱ ውስጥ ኑሬ ቢሆን ሠራዊትህም ሁሉ ቢሰበሰቡ እንኳ ወንድሜን ገላውዴዎስን
ሊይዙት ባልቻሉም ነበር አለው ።
፳፩. ንጉሡም ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሒድ ከተወደደ ከገላውዴዎስ ጋር ተገናኝ አለው ።
ምዕራፍ ስምንት
፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ገላውዴዎስ ወደ አለበት ሔደ በአየውም ጊዜ ደስ አለው አንገቱንም አቅፎ ሳመው

፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ገላውዴዎስን እንዲህ አለው አትዘን እግዚአብሔር አምላካችን ከእኛ ጋር ነውና
ዳግመኛም በዉኑ ያደረጉብህ ክፉ ነገር አለን አለው ።
፫. የለም ነገር ግን ንግሥቲቱ ልጅዋን እንዳገባላት ጠይቃኝ ነበር ማግባቱን እንቢ አልኩ አለው ።
፬. ንግሥቲቱና ልጅዋም ከቤት በስተውጭ ቁመው እነዚህን ሁለት ቡሩካን ይመለከቷቸው ነበር ።
፭. የፊታቸውን ላይ ደም ግባታቸውንና በላያቸው ያረፈውን የክርስቶስን ብርሃን አይተው አደነቁ ። ዕጹብ
ዕጹብ አሉ ።
፮. ንግሥቲቱም አንድ ሰዓሊ ጠርታ እንዲህ አለች እነዚህ ያማሩ ጎበዛዝት እይ አንተ የነሱን መልክ በቤቴ
ግድግዳ ላይ ሣልልኝ አለችው እነሱንም አስመስሎ ሥዕል ሣለላት ።
፯. ንጉሡም ቴዎድሮስን በናድልዮስንና ገላውዴዎስን ጠራቸው ።
፰. ቴዎድሮስ በናድልዮስንም ወንድምህን ገላውዴዎስን ውሰደው ወደ ሀገራችሁ ሒዱ ልጄንም ወደ እኔ
ላኩልኝ አለው ።
፱. ያን ጊዜም ንግሥቲቱ እንዲሄዱ አታሰናብታቸው ይልቁንም ገላውዴዎስን አትልቀቅ አለች ።
፲. ያንጊዜም የመላእክት አለቆች ሚካኤል ገብርኤል ከሰማይ ወረዱ ።
፲፩. ሚካኤል ለቴዎድሮስ በናድልዮስ ሰይፉን ሠጠው ገብርኤልም ለገላውዴዎስ ሰይፉን ሠጠው ።
፲፪. ያንጊዜም ቴዎድሮስ በናድልዮስ በታላቅ ድምጽ ጮሆ በጌታየ በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ለአጠፋችሁ
መጥቻለሁ አለ ከጠላቶቻቸውም ጋር ይዋጉ ጀመር ።
፲፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ድምጹን ከፍ አድርጎ በጮኸ ጊዜ ንግሥቲቱ በቤቷ ግድግዳ ላይ ያሠራቻቸው
ሥዕሎች ከሱ ጋር ጮሁ ከቃላቸው የሚሰማውን ድምጽም ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሊያጠፋችሁ መጣ ይል ነበር

፲፬. ከቁዝ ሠራዊትና ከሀገሩ ሰዎችም ብዙዎች በሰይፍና በድንጋፄ አለቁ ።
፲፭. ያንጊዜም የሀገሩ ሰዎች ፍርሃትና ድንጋፄ ወረደባቸው ብዙዎችም ሞቱ ።
፲፮. በሰይፍም በድንጋጤም የሞቱት የቁዝ ሰዎች ሰባት ሺህ ሰዎች ነበሩ ።
፲፯. ንጉሡም ሊቀ ጳጳሳቱን ሕዝቤንና ሠራዊቴን እንዲያጠፉ መንግሥቴንም እንዲያሣልፉ ለነዚህ ለሁለት
ሰዎች ኃይልንና ብርታትን የሠጠሀቸው አምላካቸው አንተ ነህን? አለው ።
፲፰. ሊቀ ጳጳሳቱም እኔ የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ አምላክ አይደለሁም ነገር ግን ለባሮቼ እንድጸልይላቸው ሊቀ
ካህናት አድሮጎ ሾሞኛል አለ ።
፲፱. ንጉሡም ከፍርሃት የተነሣ ወደ ፎቅ ወጣ ።
፳. ሕዝቤንና ሠራዊቴን እንዳታጠፋብኝ መንግሥቴን እንዳታሳልፍብኝ በአምላክህና በወንጌል ተማፅኜ
እለምንሃለሁ ። ብሎ ወደ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ጮኸ ።
፳፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስና ገላውዴዎስ ሊቀ ጳጳሳቱን ይዘውት ከሀገር ወጡ ቴዎድሮስ በናድልዮስም የደም
ፈሳሽ እጁን ከሰይፉ ጋር ስለ አጣበቀው ውሀ በሌለበት እጁ ሊላቀቅ አልቻለም ።
ምዕራፍ ዘጠኝ
፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስና ገላውዴዎስ ወደ ሀገራቸው ተመለሱ ።
፪. ወደ ከተማው አቅራቢያ በደረሱ ጊዜ ለንጉሥ ጠልሜዎስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ እንደተመለሰ
ገላውዴዎስንም በደህና እንዳመጣው ነገሩት ።
፫. ንጉሡም ፍጹም ደስታ ደስ አለው ንግሥቲቱም ደስ አላት ሕዝቡም ሁሉ ደስ አላቸው ሠራዊቱም
ወጥተው በፍጹም ደስታ ተቀበሏቸው ።
፬. ንጉሡም እስከ ፲፭ ቀን ሕዝቡን በማብላት በማጠጣት ለቤተ ክርስቲያን ለካህናት ለእንግዳም ልብስና
ገንዘብ በመሥጠት የደስታ በዓል አደረገ ።
፭. ዳግመኛም ለድሆች ለጦም አዳሮች ባል ለሌላቸው ሴቶችና ለሙት ልጆች ለእያንዳንዳቸው አርባ አርባ
ወቄት ወርቅ ሠጠ ልብስም አለበሳቸው ።
፮. የቁዝ ንጉሥ ልጅ አግራዶስ ግን በማረኩት ጊዜ በጦርነት ላይ በጦር ወግተውት ስለ ነበረ ጥቂት ቁስል
ነበረበትና በዚያው ታሞ ሞተ ።
፯. ከዚያ ወራትም በኋላ ጠልሜዎስ ንጉሥ ሞተ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቴዎድሮስም ሞተ ።
፰. ከዚህ በኋላ የጠልሜዎስን ልጅ ገላውዴዎስን ንጉሥ ይዘው ንጉሥ አደረጉት ።
፱. መንግሥትን መያዝንም እንቢ አለ እኔ ንጉሥነትን አልሻም ራሴን ለክርስቶስ አሣልፌ ሠጥቻለሁና አለ ።
፲. ከመንግሥት ወገን የሚሆን ዑማርያኖስንም ወስደው በአንጾኪያ ዙፋን ላይ አነገሡት ።
፲፩. የቁዝ ሰዎችም የአንጾኪያ ንጉሥ ጠልሜዎስ እንደ ሞተ ሰሙ ።
፲፪. ሰባት የአረሚ ነገሥታትን አስተባብረው በጠላትነት ተነስተው ገላውዴዎስን በተንኮል እንዲገድለው ወደ
ዑማርያኖስ ላኩበት የልጃቸውን ደም ለመመለስ ዑማርያኖስ ግን አዘነና አርበኞች እንዲሰበሰቡ ወደ ግብፅ ሀገር
ላከ ።
፲፫. ከኃዘኑ ጽናትም የተነሣ ታሞ ሞተ ።
፲፬. መኳንንቱ ሌላ እንያነግሡ መከሩ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ግን ከለከላቸው እንሂድ አስቀድመን ከአረሚና
ከቁዝ ነገሥታት ጋር እንዋጋ ብሎ ።
፲፭. ብዙ ናቸውና ቁጥራቸውም ብዙ ነውና እግዚአብሔር በሰላም ቢመልሰን የወደድነውን ንጉሥ እናነግሣለን
አላቸው ።
፲፮. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሠራዊቱን ይዞ ሊዋጋ ሔደ ከግብጽ የመጡ ረዳቶችም አብረውት ሔዱ
ከግብፃውያንም በከተማ የቀሩ ጥቂቶቹ ነበሩ ። በመካከላቸውም አግሪጳ የሚባል አንድ ሰው ነበር መልካምም
ነበር በግብጽ ሣለ ፍየሎችን ይጠብቅ ነበር ።
፲፯. በአንጾኪያም ከፈረስ ዘበኞች ጋር ተቀላቀለ ።
፲፰. ፈረሱንም ገፈራ በሚያለብሱበት ጊዜ እንዚራውን አንሥቶ በፈረሱ ፊት ይዘፍን ነበር ።
፲፱. ሰይጣንም በፈረሱ ላይ አድሮ ያዘፍነው ነበር ዑማርያኖስም ሁለት ሴቶች ልጆች ነበሩት ከፎቅ ላይ
ተቀምጠው ነበር ። ከእነሱ አንዲቱ ፈረሱን ሲያዘፍነው አግረጳን አየችው ለታላቋም ልትነግራት ሔደች ይህን
ድንቅ ነገር ነይ እይ አለቻት ሔደች አየች ።
ምዕራፍ አሥር
፩. እሷ ግን ሰይጣን ኃጥያትን አጣፈጠላት አግሪጳንም ወደደችው ።
፪. ሌሊትም በሆነ ጊዜ ቤት ከፍታ አስገባችውና ከእሱ ጋራ አመነዘረች ድንግላዋንም አጠፋች ።
፫. አግሪጳን አግብቻለሁ የጋብቻ ሕግ ፈጽሙልኝ ብላ ወደ ካህናት ላከች ።
፬. አይሆንም ቴዎድሮስ በናድልዮስን እንፈራለን አሏት ።
፭. ልጂቱም መንግሥት የአባቴ አይደለምን ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወታደር ነው አለቻቸው ።
፮. ይህንንም ብላ ካህናቱን በብዙ ወርቅ ሸነገለቻቸው ለአግሪጳም አጋብተው አነገሷት።
፯. በአነገሡትም ጊዜ ዲዮቅልጥያኖስ አሉት ።
፰. ፊስንድያም በእጅዋ እንዲህ ብላ ጻፈች የንጉሥ ዑማርያኖስ ልጅ አንድ አግሪጳ ከሚባል ከፍየል እረኛ
ግብፃዊ ጋር ተጋባች የአንጾኪያ ሀገርም ንጉሥ አደረጉት ብላ ጻፈች ።
፱. ወደ ቴዎድሮስ በናድልዮስም ደብዳቤ ላከች ።
፲. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ያነን ደብዳቤ በአየ ጊዜ
፲፩. ሠራዊቱን በጦር ሜዳ ትቶ ወደ አንጾኪያ ከተማ ተመለሰ ወደ ንጉሥ ግቢም ገባ ።
፲፪. ይህን የፍየል እረኛ ግብፃ በሮም ላይ ንጉሥ ያደረገው ማነው? አለ ።
፲፫. የንጉሥ ዑማርያኖስ ልጅም ከፎቅ ላይ ሆና መንግሥቱ የአባቴ የእኔ አይደለምን አንተማ የጦር ሰው
አይደለህምን ብላ መለሰችለት ።
፲፬. ያንጊዜም ወዲያውኑ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሰይፉን መዞ ከልጅነቱ ሠራዊት ሰባት መቶ ሰው ገደለ ።
፲፭. እሳቱን ወስዶ ቤተ መንግሥቱን አቃጠለው ።
፲፮. ልጂቱንም ልብሰ መንግሥቱንና ዘውዱን ጠቅላ ከፎቅ ወደ ታች በገመድ አወረደችለት ቴዎድሮስ
በናድልዮስ እንዳታጠፋን በጌታህ ተማፅኜ እለምንሀለሁ ዘውዱንና ልብሰ መንግሥቱን ውሰድ የወደድከውንም
አንግሥ አለችው ።
፲፯. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ገላውዴዎስን ወስዶ በመንግሥት ዙፋን ላይ አስቀመጠው ። ልብሰ መንግሥት
አለበሰው ። አክሊለ መንግሥት አቀዳጀው ። አዋጅ ነጋሪም በከተማው እየዞረ ቴዎድሮስ በናድልዮስ
ገላውዴዎስን አነገሠው እያለ አወጀ።
፲፰. ሕዝቡም እውነት ነው ይገባዋል አሉ ።
፲፱. ገላውዴዎስም የቴዎድሮስ በናድልዮስ ቁጣው እንደበረደ በአየ ጊዜ ዘውዱን ከራሱ አወረደ ልብሰ
መንግሥቱንም አወለቀ።
፳. እኔ የዚህን ዓለም መንግሥት አልፈልግም አለ ።
፳፩. ያንጊዜም የእግዚአብሔር መልአክ ለቴዎድሮስ በናድልዮስ ተገለጠለትና እግዚአብሔር ኃይሉን ጽንዓቱን
ሠጠህ እነዚህን ክርስቲያኖች ለምን አጠፋሀቸው? አለው ።
፳፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም መልሶ የእግዚአብሔርን መልአክ ፤ አምፀው የፍየል እረኛ ግብፃ አንግሠዋልና
ስለዚህ ነው አለው ።
፳፫. የእግዚአብሔር መልአክም ቴዎድሮስ በናድልዮስን እንዲህ አለው አይሁድ በክርስቶስ ላይ ከአደረጉት
ይህኛው አመፅ ይበልጣልን የግርንግሪት አሠሩት ፤ በጲላጦስና በሊቃነ ካህናት ፊት በአደባባይ አቆሙት ።
፳፬. ሰደቡት ፤ ፊቱን በጥፊ መቱት ፤ ርኩስ ምራቅንም ተፉበት እንግዲህ ያ ዓመፅ ይበልጣል ግን
አላጠፋቸውም እግዚአብሔር ይቅር ባይ ታጋሽም ነውና ለዲዮቅልጥያኖስም ለአንድ ሰዓት መንግሥትን
ሠጥቷል አለው ።
፳፭. ቴዎድሮስ በናልዮስም እግዚአብሔር የፈቀደውን ያንግሥ አለው ።
፳፮. ይህን ከተናገረ በኋላ ወደ ሠራዊቱ ወደ ሰልፉ ተመልሶ ከአረማውያንና ከቁዝ ሰዎች ጋር ተዋጋ ።
፳፯. ቴዎድሮስ በናድልዮስም እኔ በጌታየ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ለአጠፋችሁ መጥቻለሁ ብሎ በጮኽ ጊዜ ያ
ጊዜ የቁዝና የአረሚ ሰዎች ከፊቱ ሸሹ ተከትሎም አጠፋቸው ዳዊት በመዝሙር ጠላቶቼን አሣድዳቸዋለሁ
እይዛቸዋለሁ እስከ አጠፋቸው ድረስም አልመለስም አስጨንቃቸዋለሁ መቆምም አይቻላቸውም ብሎ
እንደተናገረ ።
፳፰. የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስንም ማርኮ ወደ አንጾኪያ ወስደው ለንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም ሠጠው ።
፳፱. ዲዮቅልጥያኖስም እስክንታረቅ ወደ አባቱ እስክንመልሰው ድረስ የንጉሡን ልጅ ውሰድና ጠብቀው ብሎ
በአደራ ይጠብቀው ዘንድ ለሊቀ ጳጳሳቱ ለአባ አጋግዮስ ሠጠው ።
ምዕራፍ አስራ አንድ
፩. የቁዝ ንጉሥ ግን ስለ ልጁ በጣም አዘነ በልቡም ብዙ ገንዘብ ብልክለት የአንጾኪያው ንጉሥ ለልጄ
ይራራለታል መልሶም ይልክልኛል ብሎ አሰበ ።
፪. ይህንንም ብሎ ወርቅና ብር የከበረ ልብስ የተጫኑ መቶ በቅሎዎች ላከ ።
፫. ስለ ልጁ ስለኒጎሚዶስ ፈንታ ይህን ገንዘብ ተቀበልና ልጄን ስደድልኝ ብሎ ወደ ዲዮቅልጥያኖስ ላከ ።
፬. ዲዮቅልጥያኖስም መልክተኞችን እኔ የከበረ ወርቅና ብር የከበረ ልብስም አላጣሁም ስለልጅህም ፈንታ
የላክኸውን ገንዘብም አልቀበልም ሕዝበ ክርስቲያንን ሁሉ እንዳትወጋቸው ምድራቸውንም እንዳትነጥቃቸው
ማልልኝ እንጂ ብላችሁ ለጌታችሁ ንገሩት አላቸው ።
፭. መልእክተኞችም ወደ ንጉሡ ደብዳቤ ጻፉ በመልእክታቸውም ዲዮቅልጥያኖስ ያለውን ሁሉ ገለጡለት
ደግሞም ልጁ ከሊቀ ጳጳሳቱ ከአባ አጋግዮስ ዘንድ በአደራነት በደህና እንዳለ ነገሩት ።
፮. የቁዝ ንጉሥ ግን ይህን መልእክት በአነበበ ጊዜ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ በተንኮል እንዲህ የምትል ደብዳቤ ጻፈ ።
፯. አባቴ ሊቀ ጳጳሳት በእውነት የክርስቲያን አባት አንተ ነህ ስለእነሱም የምታስብ አንተ ነህ ቸርነትህም
ለሕዝበ ክርስቲያን ብቻ አይደለም ለክፉውም ለደጉም ለኃጥኡም ለጻድቁም ነው እንጂ ሰማያዊ አባትህ
ፍጹም እንደሆነ ።
፰. አሁንም በአንተና በእኔ መካከል ዕርቅ ይሁን ።
፱. ይህንን የመቶ በቅሎ ጭነት ወርቅና ብር የከበረ ልብስም ተቀበል ልጄን ኒጎሚዶስንም ስደድልኝ ።
፲. ይህ መንግሥት የማይገባው የፍየል እረኛ ግብፃዊ ግን ከጠብና ከጭቅጭቅ በቀር ዕርቅ አይወድም
ይነግሥባቸው ዘንድ የማይወዱ የአንጾኪያ ሰዎች እንዳይነሱበት ።
፲፩. ይህንን ጽፎ አትሞ ወደ ሊቀ ጳጳሳት በምሥጢር ላከ ።
፲፪. ደብዳቤይቱም ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ አባ አጋግዮስ በደረሰች ጊዜ ገንዘቡን ወርቁን ብሩን የከበረ ልብሱን
በሌሊት ተቀብሎ የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስን በሥውር ሠደደው ሔደ ወደ አባቱም ደረሰ ።
፲፫. ኒጎሚዶስም ወደ አባቱ በደረሰ ጊዜ የቁዝ ሰዎችና የአረሚ ነገሥታት ከብዙ ሠራዊት ጋር ተሰበሰቡ ።
መክረውም ሮማውያንን ሊወጉ ተነሡ ።
፲፬. ኒጎሚዶስም ሠራዊቱን አሰልፎ ከሮማውያን ጋራ ሊዋጋ ሔደ ።
፲፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሠራዊቱን አሰልፎ ከቁዝና ከአረሚ ጋር ሊዋጋ ሔደ ።
፲፮. ከዳኖፊሰ ባሕር አጠገብም ደርሰው ሠፈራቸውን ከዚያ አደረጉ ።
፲፯. የቁዝ ሰዎችና የአረሚ ነገሥታትም ወደነሱ ቀረቡ ሠፈራቸውንም በነሱ ትይዩ አደረጉ ።
፲፰. ሰይጣንም ከቁዝ ሠራዊት አንዱን መስሎ ወደ ሮማውያን ሠፈር ሔዶ ክፉ ነገር ተናገረ ።
፲፱. ከዚህም በኋላ ከሮማውያን አንዱን መስሎ ወደ ቁዝ ሰዎች ሔዶ ክፉ ነገር ተናገረ ።
፳. እንዲዋጉም አደረጋቸው ።
፳፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በሚዋጋበት ጊዜ የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስን ከጦርነት ውስጥ አየው ።
፳፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ቴዎድሮስ ይባል ለነበረው ለሠራዊቱ አለቃ ለሞክሼው የቁዝ ንጉሥ ልጅ
ኒጎሚዶስን አየዋለሁ ያው ብሎ ነገረው ።
፳፫. የሠራዊት አለቃ ቴዎድሮስ እሱ አይደለም እሱን የሚመስል ነው እንጂ አለው ።
፳፬. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወደ ቁዝና ወደ አረሚ ሰዎች ከዛሬ ጀምሮ እስከ ፲፪ ቀን ድረስ እንቆይ ከዚያ
በኋላ እንዋጋለን ብሎ ላከ እሽ ይሁን አሉ ።
ምዕራፍ አሥራ ሁለት
፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሠራዊቱን በሠፈር ትቶ ማንም ሣያውቅ የሠራዊቱን አለቃ ሞክሼውን ቴዎድሮስን
ይዞ ወደ አንጾኪያ ተመለሰ ።
፪. ወደ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ አጋግዮስም መጣ ከሱም ተባረከ ።
፫. እንዲህም አለው አባቴ ትናንትና በጦርነቱ ውስጥ ሣለን እሱ ወይም ምሣያው ይሁን እንጃ ኒጎሚዶስን
የመሰለ ሰው አይተናል ።
፬. አባታችን ምናልባት ከአንተ ጠፍቶ እንደሆነ አሁንም እንሂድና በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ይዘን እናምጣው
ወደ አንተም እንመልሰው ።
፭. በፈቃድህ ሠደኸው እንደሆነ ግን እንተወው በሰልፍ ውስጥም አንያዘው በአንተና በንጉሡ በዲዮቅልጥያኖስ
መካከል ፀብ እንዳይሆን አለው ።
፮. ሊቀ ጳጳሳቱ አባ አጋግዮስም ልጆቼ ሊቀ ሐዋርያት ጴጥሮስን በሾመው በኢየሱስ ክርስቶስ በከበሩ እጆቹ
እምልላችኋለሁ እውነቱን ልንገራችሁ የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስ ከእኔ ዘንድ ሞቷል በእጄ የቀበርኩትም እኔ
ነኝ አላቸው ።
፯. ቴዎድሮስ በናድልዮስና ሊቀ ሠራዊት ቴዎድሮስም ከሊቀ ጳጳሳቱ ተባርከው ወደ ሠፈራቸው ተመለሱ
ከቁዝና ከአረሚ ነገሥታትም ጋር ይዋጉ ጀመር ።
፰. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በጌታየ በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ለአጠፋችሁ መጥቻለሁ ብሎ በሰልፉ ውስጥ
ጮኽ ።
፱. ያንጊዜም የቁዝና የአረሚ ሰዎች ሸሹ ።
፲. ቴዎድሮስ በናድልዮስም የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስን ማረከው ወደ ሠፈርም አመጡት ።
፲፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በሠፈሩ ውስጥ አለቀሰ ኒጎሚዶስን ሠራዊቱ ሁሉ ስለ አየው ።
፲፪. ወደ ሊቀ ጳጳሳቱም በምሥጢር እንዳይመልሱት መሠወር ተሣናቸው ።
፲፫. ሠራዊቱ ሁሉ ስለአየውም የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስን ወደ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ አመጡት ።
፲፬. ዲዮቅልጥያኖስም አንተ ኒጎዲሞስ ነህን አለው ኒጎዲሞስም አውን አለው ።
፲፭. ንጉሡም ለሊቀ ጳጳሳት አደራ ብዬ አልሰጠሁህምን እሱ አልጠበቀህምን ወይስ አንተ ከእሱ ጠፍተህ
ሔድክን አለው ።
፲፮. ንጉሥም እንዴት ሔድክ ንገረኝ ብሎ እንደገና ጠየቀው ።
፲፯. ኒጎሚዶስም ንጉሡን እንዲህ አለው አባቴ ብር ብዙ ወርቅ የከበረ ልብስም ጨምሮ እጅ መንሻውን
ተቀብለህ እኔን እንድትሠጠው ደብዳቤና መልክተኞችን ወደ አንተ ላከ አንተ ግን አልቀበልም አልክ ።
፲፰. አባቴም ያን ገንዘብ ለሊቀ ጳጳሳቱ ሠጠው ሊቀ ጳጳሳቱም ገንዘቡን ተቀብሎ ለቀቀኝ ወደ አባቴም
ሔድኩ ።
፲፱. ወደ አባቴም ከደረስኩ በኋላ ብዙ ሠራዊት ይዤ ከሠራዊትህ ጋር ልዋጋ መጣሁ ተሸነፍን በሰልፍ ውስጥም
ማረኩኝ ያዙኝ ወደ አንተም አመጡኝ እግዚአብሔርም እንደገና በእጅህ ጣለኝ ።
፳. ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም ኒጎሚዶስ አትፍራ ዝም ብለህ ከመጋረጃ ውስጥ ከእኔ ዘንድ ተቀመጥ አለው ።
ምዕራፍ አሥራ ሶስት
፩. ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ ይጠሩት ዘንድ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ አባ አጋግዮስ ላከ እሱም ፈጥኖ
መጣ ።
፪. ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም አደራ የሠጠሁህን የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስን አምጣልኝ ከአባቱ ጋር ዕርቅ
አድርገናልና በእኔና በእሱ መካከልም ሰላም ይሆን ዘንድ ወደ አባቱ ልመልሰው እፈልጋለሁ አለው ።
፫. ሊቀ ጳጳሳቱ አባ አጋግዮስም የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስ ከእኔ ዘንድ ሞተ እኔም በእጄ ቀበርኩት አለ ።
፬. ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም ሂድ በእጅህ ቁርባንን ሥራ ማለት ቀድስና አቁርበን ለእግዚአብሔርም በዓል
እናድርግ ጠላቶቻችንን ድል አድርገናቸዋልና አለው ።
፭. ያንጊዜም ሊቀ ጳጳሳቱ ኤጲስ ቆጶሳቱ ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ተዘጋጁ መሥዋዕትንም አዘጋጁ ።
፮. ንጉሡም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ ሕዝቡም መኳንንቱም ከሱ ጋር ገቡ ።
፯. ሊቀ ጳጳሳት አባ አጋግዮስም ቁርባኑን ቀደሰ ።
፰. ቅዳሴውንም በፈጸመ ጊዜ ለያግሪሳን አለ የሚቀበል ሰው ይምጣ ማለት ነው ።
፱. ዲዮቅልጥያኖስም በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ቆመ ሊቀ ጳጳሳቱንም እንዲህ አለው በእውነት የቁዝ ንጉሥ
ልጅ በአንተ ዘንድ ሞቷልን ስለዚህ ነገር በዚህ መሠዊያ ማለት በታቦቱ በዚህም መሥዋዕት ማለት በክርስቶስ
በሥጋው በደሙ ትምላለህን አለው ።
፲. አባ አጋግዮስም የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኒጎሚዶስ ከእኔ ዘንድ እንደ ሞተ እኔ በእጄ እንዳ ቀበርኩት በእግዚአብሔር
ታቦትና በዚህ መሥዋዕት ማለት በክርስቶስ ሥጋና ደም እምላለሁ ብሎ ማለ ።
፲፩. ያንጊዜም ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ ወደ ሰማይ አንጋጦ እስከ ሁለት ሰዓት ቆመ እንዲያቃጥለው እሳት
ከሰማይ ይወርድ እንደሆነ ብሎ ጠርጥሮ ነበርና ።
፲፪. ነገር ግን እሳት በጊዜው ስለአልወረደ ዲዮቅልጥያኖስ መታገሥ ተሣነው ።
፲፫. ሰዓቲቱ ሶስት እስክትመላ ጠብቆ ቢሆን ኖሮ በሐሠት የማለውን ያቃጥለው ዘንድ እሳት በወረደ ነበር ።
፲፬. ያንጊዜም ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ሊቀ ጳጳሳቱን አባ አጋግዮስን እሱ ራሱ በቀሚሱ አንቆ ጎተተው
ለወታደሮቹም አሣልፎ ሠጠው ።
፲፭. ወታደሮቹም ወደ ቤተ መንግሥት ወሰዱት ።
፲፮. ንጉሡም ኒጎሚዶስን ጠራውና ከመጋረጃው ውስጥ ወጣ ሁለቱም ማለት ሊቀ ጳጳሳቱ አባ አጋግዮስና
የቁዝ ንጉሥ ልጅ ኖጎሚዶስ በአደባባዩ ውስጥ በሕዝቡ ሁሉ ፊት ቆሙ ።
፲፯. ንጉሡም ከሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ በምን አመለጥክ ብሎ ጠየቀው ።
፲፰. ኒጎሚዶስም ንጉሡን ዲዮቅልጥያኖስን እንዲህ አለው ቀድሞ ነግሬሀለሁ አሁንም ስማ ልንገርህ አባቴ ወደ
አንተ ላከ እኔን ትሰጠው ዘንድ ብዙ ወርቅ ብር የከበረ ልብስም ሰደደ አንተ ግን እንቢ አልክ አባቴም በሚሥጢር
ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ላከ አንተ አልቀበልም ያልከውን ገንዘብ ሰጠው ።
፲፱. ሊቀ ጳጳሳቱም ገንዘቡን ተቀብሎ ሰደደኝ ሔድኩ ወደ አባቴም ደረስኩ ።
፳. ከዚህም በኋላ ብዙ ሠራዊት ሰብስቤ ከሠራዊትህ ጋር ልዋጋ መጣሁ በሰልፍ ውስጥም ያዙኝ
እግዚአብሔርም በእጅህ አሣልፎ ጣለኝ ።
፳፩. ያጊዜም ንጉሡ የሊቀ ጳጳሳቱን ቤት እንዲበረብሩ ወታደሮቹን ላከ ።
፳፪. በቤቱ የተገኘውን ሁሉ በረበሩ ወደ ንጉሡም የመቶ በቅሎ በጭነት የከበረ ልብስ ወርቅና ብር አመጡ
ገንዘቡንም በሕዝቡ ፊት አኖሩት ።
፳፫. ንጉሡም ሊቀ ጳጳሳቱን እንዲህ አለው ወርቅና ብር ከፈለግህ በእግዚአብሔር ስም በሐሰት ከምትምል
ይልቅ እኔ ከዚህ አሥር እጥፍ የሚበዛ በሰጠሁህ ነበር ።
፳፬. አሁንም አንተ ወርቅ ወደሀል እኔም እመግብሀለሁ ።
፳፭. ይህንንም ብሎ ወርቅ አንጣሪ አስመጣና ወርቁን አስቀልጦ አፉን ከፍቶ ለሊቀ ጳጳሳቱ የቀለጠ ወርቅ
አጠጣው ሊቀ ጳጳሳቱም ወዲያው ሞተ ።
ምዕራፍ አሥራ አራት
፩. ከዚህም በኋላ ንጉሡ ዲቅልጥያኖስ አብያተ ክርስቲያናትን እንዲዘጉ አብያተ ጣዖታትን እንዲከፍቱ አዘዘ ።
፪. ዳግመኛም ንጉሡ ከወርቅ ምስል ፸ ጣዖታት እንዲሠሩ ከእነሱም ፴፭ቱ በወንዶች አምሳል ፴፭ቱ በሴቶች
አምሳል እንዲሆኑ አዘዘ ።
፫. ለአማልክቱም ከእንስሳት ወገን መሥዋዕት አምጥቶ ሠዋ የጣዖታቱ ካህናትም ለጣዖታቱ ዕጣን መሥዋዕት
ለእያንዳንዱ ስም አወጡ ።
፬. አስቀድሞም ንጉሡ ቀርቦ ለጣዖታት ሰገደ ብዙ ሰዎችም አብረውት ሰገዱ ለጣዖታትም ከሰገዱት ሰዎችም
በዚያች ዕለት መቶ አምሣ ሰዎች በግፊያው ሞቱ ።
፭. ንጉሡም ለጣዖታት የማይሰግድ ቢኖር ራሱ ይፈረድበት ይቀጣ ገንዘቡም ይወረስ አንገቱም በሰይፍ ይቆረጥ
ብሎ አዘዘ ።
፮. በሚገዛው ሀገር ሁሉ አብያተ ክርስቲያናት ይዘጉ አብያተ ጣዖታት ይከፈቱ ሰው ሁሉ ለአማልክት ይስገድ
ለአማልክት ያልሰገደላቸው ቢኖር ይፈረድበት አንገቱን በሰይፍ ይቀላ ቤቱ ይወረስ የሚል ደብዳቤ ጽፎ ላከ ።
፯. በንጉሡ ቀኝ ከቆሙት መኳንንት ለአንዱ እስጢፋኖስ ለሚባው መኰንን ደብዳቤውን ሠጡት
እስጢፋኖስም ደብዳቤይቱን ተቀብሎ ቀደዳት ክርስቶስን የሚወድ ነውና ።
፰. ዲዮቅልጥያኖስም ሰይፍ መዞ ራሱ እስጢፋኖስን መታው ለሁለትም ከፈለው ።
፱. አንጾኪያም እንደ ኢየሩሳሌም ሆነች በኢየሩሳሌም ሊቀ ዲያቆናት እስጢፋኖስ መጀመሪያ ሰማዕት ሆኗልና

፲. በአንጾኪያ ከተማም በፊት የፋሲለደስ ልጅ እስጢፋኖስ ሰማዕት ሆኗልና ።
፲፩. በኢየሩሳሌም ሰማዕታት ከሆኑት ይልቅ የአንጾኪያ ሀገር ሰማዕታት ይበልጣሉ ።
፲፪. በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን ሰማዕት የሆኑ ክፉና በጐ የማያውቁ ሕፃናት ናቸው ።
፲፫. በሚገሏቸው ጊዜም ከአባቶቻቸውና ከእናቶቻቸው ጋር እንዳሉ ይስቁ ነበር ሞትንና ሕይወትን
አያውቁም ነበርና ።
፲፬. እነዚህ በአንጾኪያ ሰማዕት የሆኑት ግን ታላላቆች ናቸው ቤት አላቸው እርሻ አላቸው አባት እናት ወንድም
እህት ሚስት ልጆች የመንግሥት ሹመት አሏቸው ።
፲፭. ይህን ሁሉ የዚህን ዓለም ከብርም ናቁ ድንግልናን መረጡ ስለ ክርስቶስም ሰውነታቸውን አሣልፈው
ለሞት ሠጡ ።
፲፮. ለሞት ሲሔዱም ወደ ሠርግ ቤት እንደሚሔድ ሰው ደስ ይላቸዋል የሞትን መራራነትም እንደሚጣፍጥ
የመዓር ወለላ አደረጓት በዓለሙ ያለውን ሁሉ ትተው ስለክርስቶስ ፍቅርም እንደትቢያ አደረጉት ።
፲፯. ዲዮቅልጥያኖስም የተቀደደችውን ደብዳቤ ወርውሮ ጥሎ በፊተኛው ዓይነት ሌላ ደብዳቤ አስጻፈ ወደ
ሚገዛውም ሀገር ሁሉ ሠደደው ።
፲፰. ከዚች ቀን ጀምሮም ንጉስ ዲዮቅልጥያኖስ ክርስቶስን ካደው ከወርቅ ከብር ከእንጨት ከደንጊያ በልዩ ልዩ
መልክና ምሳሌ በሰው ብልሀት ለተቀረጹ ለርኩሳን አማልክት ይሰግድ ጀመረ ።
፲፱. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በክርስቶስ መንገድ ሔደ በሃይማኖትም ፀና ወደ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ
አልሔደም ።
ምዕራፍ አሥራ አምስት
፩. ከዚህም በኋላ ንግሥቲቱ ንጉሡን እንዲህ አለችው ለጣዖታት ከሰገድን ወዲህ እነሆ ቴዎድሮስ በናድልዮስ
እስከ ዛሬ ወደ እኛ አልመጣም ወደ ቤታቸችንም አልገባም ።
፪. አሁንም እሱን የተውከው እንደሆነ በእኛ ላይ ፀብ ያነሣል ብዬ እጠረጥራለሁ ይህ ነገር ሊሆን አይገባም
ከእሱ በቀር መንግሥታችንን የሚሽር የለምና ።
፫. ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም ሚስቱን እንዲህ አላት በእሱ ላይ ምን ማድረግ ይቻለኛል ብርቱ ኃያል ነውና
መኳንንቱ ሕዝቡም ሠራዊቱም ይወዱታል ።
፬. ይህንም ብሎ እያዘነ ተኛ ።
፭. ከዚህም በኋላ ሰይጣን ከብርሃን የተራቆተ ሲሆን ብርሃን የለበሰ መልአክ መስሎ ታየው ።
፮. ንጉሡም ሰይጣንን አንተ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነህን አለው ።
፯. ሰይጣንም እንዲህ አለው ይህን ስም ዳግመኛ አትጥራው እግዚአብሔር ጨርሶ ስሙን ከምድረ ገጽ
ደምስሶታልና ።
፰. ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም በላ እንግዲያ ስምህን ንገረኝ አንተ ማነህ ።
፱. ሰይጣንም እንዲህ አለው አንተ ዲዮቅልጥያኖስ ሐዲስ አድርገህ የሰገድክልኝ አዲሱ አምላክህ እኔ ነኝ
መንግሥትህን እኔ አጸናታለሁ በጦርነት ውስጥም ከእንተ ጋር እኖራለሁ ጠላቶችህንም አጠፋቸዋለሁ ።
ቴዎድሮስ በናድልዮስን ክብረ መንግሥትህን ከመግፈፉ አማልክቶችህንም ከማጥፋቱ በፊት አንተ ልታጠፋው
ትችላለህ ።
፲. ዲዮቅልጥያኖስም መልሶ ሰይጣንን እንዲህ አለው እኔ እንዴት ላጠፋው እችላለሁ እሱ ጽኑዕ ኃያል ነውና
እኔም እፈራዋለሁ ።
፲፩. ሰይጣንም ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስን እንዲህ አለው ቁዝና አረሚ በእኛ ላይ ተማክረዋል ። እንዋጋ
በማለትም ደብዳቤ ልከዋልና ስለመንግሥትም ሥራ ሆነ ስለጦርነቱም ነገር ና እንማከር ብለህ ላክበት ።
፲፪. ብዙ ኃያላን ጐልማሶች ምረጥና በቤተ መንግሥትህ ውስጥ ደብቃቸው ምልክት በሠጠሀቸው ጊዜም
እንዲወድቁበትና አጽንተው እንዲይዙት እዘዛቸው ።
፲፫. መምጣቱንም ስትሰማ በፍቅር ተቀብለው በሽንገላም አነጋግረው ምሣ እንዲያመጡ እዘዝ ብላም በለው
ያንጊዜ ሰይፍ የያዙ ኃያላን ጐልማሶች ይግቡና እንደታዘዙ ያድርጉበት እኔም ረዳት እሆናቸዋለሁ አለው ይህን
ተናግሮ ከእሱ ተሠወረ ።
፲፬. ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም በነቃ ጊዜ በሕልሙ የሆነውን ይህን ሁሉ ነገር አሰበ ዲያብሎስ እንደመከረውም
ወደ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ላከ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ከመምጣቱ አስቀድሞ ንጉሡ በቤተ መንግሥቱ ውስጥ ፮፻
ሰይፍ የታጠቁ ኃያላን ጐልማሶች በድብቅ አኖረ የወደደውንም ሁሉ እንዲያርጉ አዘዛቸው ሰይጣንም
እንዳስተማረው ሁሉን አዘጋጀ ።
፲፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወደ ንጉሥ መጣ ምንም አልተጠራጠረም ነበር ንጉሡም በሽንገላ ቃል ዛሬ በቤቴ
ደስታ ሆኗል ቴዎድሮስ በናድልዮስ መጥቷልና አለ ።
፲፮. እንዲበላም ማዕድ አዘጋጅቶ በፊቱ አቀረበለት ።
፲፯. ያንጊዜም ማለት በማዕድ ላይ ሣለ ፮፻ ኃያላን ጐልማሶች መጥተው ከበቡና ያዙት ።
፲፰. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ማዕድህ የቁጣ ማዕድ ነውን አለው ።
፲፱. በእግር ብረት በሰንሰለት እጁን እግሩን በጽኑዕ አሠሩት ።
ምዕራፍ አሥራ ስድስት
፩. መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜም ቴዎድሮስ በናድልዮስ የሚጠብቁትን ወንድሞቼ ሆይ ወደ እግዚአብሔር
እንድጸልይ አንድ ጊዜ ፍቱኝ አላቸው ።
፪. የሚጠብቁትም አለቃችን ሆይ ይህን ለመሥራት ሥልጣን የለንም ልንፈታህም አንችልም ንጉሡን
እንፈራዋለንና አሉት ።
፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በእግዚአብሔር ታምኖ እጆቹን ዘረጋ ከእጁም ከእግሩም እግር ብረቱንና ሰንሰለቱን
ፈታ ቀድሞ የጳውሎስን እግር ብረቶች የፈታ ዛሬም ኃይሉን ገልጾ በሰማዕቱ በቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ
ተመሰገነ ።
፬. ያንጊዜም ጠባቂዎችን ፍርሃት ረዓድ ያዛቸው ፈሩ ተብረከረኩ አንዱም በአንዱ ላይ ወደቁ ።
፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ከእንግዲህ ዳግመኛ በእጄ ሰይፍ አልይዝምና አትፍሩ አላቸው ።
፮. ከዚህም በኋላ ሊጸልይ ተነሣ ይህንን መዝሙርም ጸለየ እንዲህም አለ ጌታ ጌታዬን እንዲህ አለው በቀኜ
ተቀመጥ ። ጠላቶችህን ከእግርህ በታች እስክጥላቸው ድረስ ። እግዚአብሔር ከጽዮን የኃይል በትር ይልክልሀል
። በጠላቶችህ መካከል ትገዛለህ ትፈርዳለህ በኃይል ቀን ቀዳማዊው ከአንተ ጋር ነው ። ለቅዱሳን ብርሃን
በሚወጣበት ቀን ያጥቢያ ኮበብ ከመፈጠሩ አስቀድሞ ከሆድ ወለድኩህ ። እግዚአብሔር ማለ አይጸጸትም ።
እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዓለም ካህን አንተ ነህ እግዚአብሔር በቀኝህ ነው በተቆጣበት ቀን ነገሥታቱን
ይቀጠቅጣል ። አሕዛብን ይቀጣቸዋል ሬሣዎችንም ያበዛል በምድር ላይም የብዙዎችን ራስ ይሰብራል ።
በመንገድ ከፈሳሹ ውሀን ጠጡ ስለዚህም አለቃው ከፍ ከፍ ይላል ።
፯. ሌላውንም ጸሎት እንደ አስለመደ ጸለየ ።
፰. ከዚህም በኋላ ተመልሶ የሚጠብቁትን እንግዲህ ንጉሥ እንደ አዘዛችሁ አድርጉ አላቸው ተነስተውም እንደ
ቀድሞው በእግር ብረት በሰንሰለት አሠሩት ።
፱. በነጋ ጊዜም ንጉሥ ድዮቅልጥያኖስ ቴዎድሮስ በናድልዮስን ከእሥር ቤት እንዲያመጡት ለፍርድም በፊቱ
እንዲያቆሙት አዘዘ ።
፲. በመጣ ጊዜም ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሆይ ለጣዖታት ስገድ ክርስቶስን ካድ አለው ።
፲፩. ቴዎድሮስ በናድልዮስም እንዲህ አለው ዳዊት ጣዖታትንና በነሱ የሚታመኑትን ሲያሣፍራቸው እንዲህ
አላለምን ።
፲፪. የአሕዛብ አምላኮቻቸው የወርቅና የብር ናቸው የሰው እጅ ሥራ ናቸው ።
፲፫. አፋ አላቸው አይናገሩም ።
፲፬. ዓይን አላቸው አያዩም ።
፲፭. ጆሮ አላቸው አይሰሙም ።
፲፮. አፍንጫ አላቸው አያሸቱም ።
፲፯. እጅ አላቸው አይዳስሱም ።
፲፰. እግር አላቸው አይሄዱም ።
፲፱. በጉሮሮአቸው ድምፅ አይሰማም ።
፳. በአፋቸው ትንፋሽ የለም ።
፳፩. የሠሯቸው ሁሉ የሚታመኑባቸው ሁሉ እንደነሱ እንጨት ድንጋይ ይሁኑ ።
ምዕራፍ አሥራ ሰባት
፩. ንጉሥ ድዮቅልጥያኖስም ከታላላቆች የጣዖታት ካህናት ሁለቱን ታላላቆቹን ጠራቸው የአንዱ ስሙ ሐሪክ
የሁለተኛውም ስሙ ሴሬንዮስ እናውቃለን ባዮች ኮከብ ቆጣሪዎች ነበሩና ።
፪. ድዮቅልጥያኖስም በሉ የአማልክትን ሕጋቸውን ገናና ክብራቸውን የማይበገር ኃይላቸውን ለቴዎድሮስ
በናድልዮስ ንገሩት አላቸው ።
፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ንጉሡን እንዲህ አለው ንጉሥ ሆይ መልካሙ የሚበልጠውስ የትኛው ነው እሳትን
የሚያነድ በእሳት ውስጥም ሰይጣንን ሊያነጋግረው የሚያሟርት ሐሪክ ነውን ወይስ እሳት ከቁጥቋጦ ተዋሕዶ
ቁጥቋጦይቱ ሣትቃጠል ያየ እግዚአብሔር ከእሳት ውስጥ ያነጋገረውና ጽዮንን የሠጠው ሙሴ ።
፬. ንጉሥ የሚበልጠው የሚሻለው የትኛው ነው ሁለት ሚስት ያገባ መተት የሚያደርግ ሴሬንዮስ ነውን ወይስ
ዝናም እንዳይዘንም ጸሎት ያደረገ ኤልያስ ጸለየ ፫ ዓመት ከመንፈቅ ዝናም አልዘነመም ዳግመኛም ዝናም
እንዲዘንም ጸለየ ሰማይ ዝናሙን ሠጠ ምድርም የዘሩባትን አበቀለች ።
፭. ንጉሥ የትኛው መልካም ነው የሚበልጠውስ የትኛው ነው አመንዝራው ጠንቋዩ ሐሪክ ነውን ወይስ
እግዚአብሔር ያነጋገረው ዳዊትን ቀብቶ ያነገሠው ሳሙኤል።
፮. መልካሙ የሚበልጠውስ የትኛው ነው ሴረኛው ኤሬንዮስ ነው ወይስ በባቢሎን ከአንበሳ ጉድጓድ የጣሉትና
አንበሶች የሰገዱለት ዳንኤል የእግዚአብሔር መልአክ ዕንባቆምን በራስ ጠጉሩ ተሸክሞ ማዕድ በእንባቆም እጅ
ሣለ ከኢየሩሳሌም ወደ ባቢሎን አደረሰው ጉድጓዲቱን ሣይከፍትም ወደ አንበሶች ጉድጓድ አስገባው ምግቡንም
ለዳንኤል ሠጠው በላ ዳንኤልም ለአንበሶች ሠጣቸው አንበሶችም በሉ ።
፯. ንጉሥ መልካሙ የትኛው ነው የሚበልጠውስ መተት እያደረጉ ሴቶችን የሚያሣብዱ ጐረምሶችን
እንዲከተሉና እንዲያመነዝሩ የሚያደርጓቸው ኤሬንዮስና ሐሪክ ናቸውን ወይስ ሙታንን ያስነሡ
በፈጣሪያቸው ሥልጣን ታላላቅ ተአምራት የአደረጉ ጴጥሮስና ጳውሎስ ።
፰. ንጉሥ አሁን አንተ እፈር አባትህ ሰይጣንም ይፈር ለጣዖታት የሚሰግዱ ሁሉም ይፈሩ ።
፱. ክርስቶስ በሰማይ ደመና ሁኖ በሚመጣበት ኃይሉንም በሚገልጥበት የዕልፍ ዕልፍም መላእክት በዙሪያው
በሚቆሙበት ጊዜ ሚካኤል መለከት ያሰማል ሙታን ይነሣሉ ፍጹም ጸጥታ ይሆናል ጌታችን ኢየሱስ
ክርስቶስም ከሰማይ ወደ ምድር ይወርዳል በጌትነቱም ዙፋን ይቀመጣል ያንጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው
ይከፍለዋል ።
፲. አንተ ንጉሥ ያን ጊዜ ወዮልህ ለጣዖታት የሚሰግዱ ሁሉም ወዮላቸው ።
፲፩. ለአባትህ ለሰይጣን ወዮለት ይይዙታል ያሥሩታል ይጐትቱታል ያዳፉታል ወደ እሳት ይጥሉታል
እግዚአብሔርም በዚያች ቀን ለዘለዓለም ያጠፋዋል ።
፲፪. ንጉሥ ድዮቅልጥያኖስም ይህን ሰምቶ ተቆጣና እንዲህ አለ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሆይ ወዮልህ አሁን እንደ
አምላክህ እንዲሰቅሉህ እኔ አዝዛለሁ ከእጄም የሚያድንህ እንደሌለ ታያለህ ።
፲፫. በዚያች ሀገርም ኮሞል የሚባል ታላቅ ዛፍ አለ ።
፲፬. ንጉሡም ቴዎድሮስ በናድልዮስን ወሰደው በግንዱ ላይ በልቡ እንዲያስተኙትና መቶ አምሳ ሶስት ረጃጅም
ወፋፍራም ችንካር አምጥተው ከዛፉ ጋር እንዲቸነክሩት አዘዘ ።
፲፭. የችንካሮችም ርዝመት ክንድ ክንድ ያህል ነበር በመዶሻም እነዚህን ችንካሮች በመላ ሰውነቱ መታው
ከዛፉም ጋር ቸነከሩት ።
፲፮. ያ ቅዱስ ሰማዕት ግን ሲቸነክሩት አንዲት ቃል እንኳን አልመለሰም ።
፲፯. የቴዎድሮስ በናድልዮስ እኅቱ ሬሰንድያም ከዚያ ቆማ ሲቸነክሩት ትመለከት ነበር ።
፲፰. በምር ስታለቅስም ከኃዘን ብዛት የተነሣ ሆዷ እንደ እሳት ተቃጠለ ።
፲፱. ከዚያ የቆሙ ሕዝቡም ንጉሡን እየረገሙ እየወቀሱ ከእሷ ጋር ያለቅሱ ነበር ።
፳. ስለ እርሱም ይህ ሰው ከጠላቶቻችን እጅ ያዳነን ጀግና ነበር ይህ ዓመፀኛ ንጉሥ ዛሬ የዓይኖቻችንን ብርሃን
አሳጣን ይሉ ነበር ።
ምዕራፍ አሥራ ስምንት
፩. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለቴዎድሮስ በናድልዮስ ተገለጠለት እንዲህም አለው ሰላም ለአንተ ይሁን
ይህን ሁሉ መከራ ታግሠሀልና ።
፪. አሁንስ ይህን ሁሉ ችንካር ከሥጋህ እንዳወጣልህና ይህን ዓላዊ ንጉሥ እንድታሣፍረው ትሻለህን ።
፫. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አይደለም ስለስምህ መሞት ይሻለኛል አለው ።
፬. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቴዎድሮስ በናድልዮስን እንዲህ አለው ሶስት አክሊል አዘጋጅቸልሀለሁ አንዱ
ስለድንግልናህ ነው አንዱ ደግሞ እኔን በመውደድ የደከምክ ስለሆንክ ነው አንዱም በእኔ ስም ስለሞትክ ነው ።
፭. ያዘነ የተከዘ መከራ የደረሰበትና የተጨነቀ ቢኖር ስምህን ጠርቶ እኔን ቢለምን ማለት አምላከ ቴዎድሮስ
እርዳኝ ቢል እኔ የተጨነቀበትን አቀልለታለሁ ከመከራው አድነዋለሁ ደስም አሰኘዋለሁ ።
፮. በባሕር ውስጥ በመርከብ ሆኖ የተቸገረ ቢኖር ስምህን ጠርቶ ማለት ስለ ቅዱስ ቴዎድሮስ አድነኝ ቢል እኔ
አድነዋለሁ ።
፯. ወደ ሰልፍ ወደ ጦር ሜዳ ቢሄድ ስምህንም ቢጠራ እኔ ረዳት እሆነዋለሁ ።
፰. ቤተ ክርስቲያንህን የሠራ ገድልህን የጻፈ መታሠቢያህን ያደረገ በስምህ ማለት በዕረፍትህ ቀን መሥዋዕት
ያቀረበ ቢኖር እኔ እቀበለዋለሁ በመንግሥተ ሰማያትም ደስ አሰኘዋለሁ ። አምላከ ቴዎድሮስ በናድልዮስ
እርዳኝ እያለ ስምህንና ስሜን አንድ አድርጎ የሚጠራውን ሰው ሁሉ እኔ ጸሎቱን እቀበለዋለሁ እንደ ቸርነቴም
እረዳዋለሁ ።
፱. በስምህ ለድሆች ፣ ለጦም አዳሪዎች ፣ ለእስረኞች ለእንግዶች ምጽዋት የሠጠ ቢኖር እኔ ኃጢአቱን
አስተሠርይለታለሁ መንግሥተ ሰማያትንም አድለዋለሁ ።
፲. በበዓልህ መታሠቢያህ በሚደረግበት ቀን መታሠቢያህን ያደረገ ስለአንተ ይድናል ።
፲፩. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይህን ቃልኪዳን ከሠጠው በኋላ ከእሱ ተሠወረ ።
፲፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ሶስቱ መላእክት ሶስት አክሊል ሲያቀዳጁት አየ ከዚህም በኋላ አረፈ ።
፲፫. መላእክትም መጥተው ተቀበሉት እንዲህ እያሉ በዓለም የደከመ ለዘለዓለም በሕይወት ይኖራል ። ሃሌ ሉያ
ወደ እግዚአብሔርም አሣረጉት ።
፲፬. ሌሊትም በሆነ ጊዜ ሕዝቡ በሰማዕቱ በቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ሥጋ ላይ ፍጹም ብርሃን ከሰማይ
ሲወርድ አዩ ።
፲፭. ድዮቅልጥያኖስም በቴዎድሮስ በናድልዮስ ላይ ብርሃን እንደ ወረደ በሰማ ጊዜ ከተደረገው ኃይልና ተአምር
የተነሣ ሕዝቡ በክርስቶስ ያምኑ ይሆናል ብሎ ፈራ ።
፲፮. ንጉሡ ድዮቅልጥያኖስም የቴዎድሮስ በናድልዮስን እህት ፊስድያን ጠርቶ የወንድምሽን አስከሬን ወስደሽ
ቅበሪው አላት።
፲፯. እህቱ ፊስንድያም በድኑን አንሥታ በክብር ገነዘችው በሣጥንም አድርጋ በቤቷ ውስጥ አኖረችው ።
፲፰. ዕረፍቱም ጥር አሥራ ሁለት ቀን ነው ።
፲፱. ድዮቅልጥያኖስም አርባ አንድ ዓመት ነገሠ ሐያ ሶስት ዓመት በክርስቲያን ሕግ ክርስቲያን ሆኖ ኖረ አሥራ
ስምንት ዓመት ደግሞ ክርስቶስን ክዶ ለጣዖት እየሰገደ ኖረ ።
፳. በክርስቶስ ያመነውን ሁሉ ሲገድል ኖረ ።
፳፩. አርባ አንድ ዓመትም ከኖረ በኋላ ሊቀ መላእክት ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ከመንበሩ (ከዙፋኑ) ገለበጠው
ከመንግሥቱም አስወጣው ዓይኑንም አጠፋው ።
፳፪. እግዚአብሔርም የተጠላ ደሀ አደረገው በመንገድ ዳርም ተቀምጦ እንጀራ ሲለምን ኖረ ።
፳፫. የአንጾኪያ ሀገር ሕፃናትም ሊዘባበቱበት ሊስቁበት ይመጡ ነበር እንዲህም ይሉት ነበር ዲዮቅልጥያኖስ
ሆይ እኛ በክርስቶስ እናምናለን ግደለና ። እርሱም ይረግማቸው ነበር እነሱም ይረግሙት ይሰድቡትም ነበር ።
፳፬. ሰይጣንም ከብርሃን የተራቆተ ሲሆን የብርሃን መልአክ መስሎ ታየው ።
፳፭. ድዮቅልጥያኖስም አንተ ማነህ አለው ሰይጣንም አንተ አዲስ አምላክ አድርገህ የሰገድክልኝ እኔ ነኝ ።
፳፮. ስለ በደልከኝ ዓይንህን አሣወርኩህ ከመንግሥትህም ሻርኩህ ።
፳፯. አሁንም ወደ መንግሥትህ እንድመልስህ ዓይንህንም እንደ አበራልህ ያዘዝኩህን ታደርጋለህ አለው ።
፳፰. ድዮቅልጥያኖስም እንደ አደርገው ትእዛዝህ ምንድን ነው አለው ሰይጣንም በክርስቶስ ያመኑትን
ክርስቲያኖችን ትገድላለህን አለው ።፡
፳፱. ድዮቅልጥያኖስም አዎ እገድላቸዋለሁ አልምራቸውም የክርስቶስን ስም የሚጠራ አንድ እንኳን
አይተርፈኝም አለው ።
፴. ሰይጣንም ድዮቅልጥያኖስ ለእኔም ወዮልኝ ለአንተም ወዮልህ አለው ።
፴፩. ሰይጣንም የእሳት ነበልባል መስሎ ሔደ ።
፴፪. ድዮቅልጥያኖስም ፅኑ ቁስል ደዌ ያዘው ሥጋው ሁሉ ሸተተ ተላ ምላሱም ተልቶ ተቆራረጠ ክፉ ሞትንም
ሞተ ።
ምዕራፍ አሥራ ዘጠኝ
፩. ከዚህም በኋላ የሮም መኳንንት ተማከሩ ከነገሥታቱ ወገን የሚሆን ስሙ ቁስጠንጢኖስ የሚባል አንድ ሰው
መረጡ በሮምና በአንጾኪያ ሀገር ላይም በሙሉ አነገሡት ።
፪. ከጥቂት ቀን በኋላም ንጉሡ ቁስጥንጢኖስ በቤተ መንግሥቱ ተኝቶ ሣለ ልብሱን ከፊቱ ዝቅ አድርጎ ነበር
ወደ ላይም በተመለከተ ጊዜ በመስቀል ምልክት አራት ከዋክብት አየ በመካከላቸውም በሮም ቋንቋ በዚህ
የመስቀል ምልክት ጠላትህን ድል ታደርጋለህ የሚል ተጽፎ ነበር ።
፫. እግዚአብሔርም የቁስጠንጢኖስን ዓይነ ልቡና አበራለት መጽሐፍቱን አነበባት በሕልም ከተገለጠለት
መልአክም ትርጓሜዋን ተረዳ ።
፬. የመጽሐፉ ንባብ የጠላቶቹን ጥፋት የመንግሥቱን መቅናት ያመለክት ነበርና ።
፭. በጠባም ጊዜ በዚያች ሌሊት ያየውን ሁሉ ለሚስቱ ለንግሥቲቱ ነገራት ።
፮. የሮምን ጠቢባን ሁሉ እንዲጠሩለት አዘዘ ያየውን ይተረጉሙለት ዘንድ ።
፯. ከዋክብትን በመመርመርም ቢሆን ሕልምን በመተርጎምም ቢሆን ከጠቢባን ሁሉ ሐሪክና ኤሬንዮስ
ይበልጣሉ አሉት ።
፰. ያንጊዜም ንጉሡ ሐሪክንና ሴሬንዮስን ጠርቶ ያየውን ነገራቸው ።
፱. እስከ ሶስት ቀን ቀጠሮ ስጠን ትርጓሜውን እንነግርሀለን አሉት ።
፲. ቀጠሮ ሠጣቸው ።
፲፩. በሶስተኛው ቀንም ሐሠት ነገስ መክረው ወደ ቁስጠንጢኖስ መጡ ።
፲፪. ንጉሥ ሆይ ያየሀቸው አራቱ ከዋክብት ድዮቅልጥያኖስ ያመልካቸው ከነበሩ ጣዖታት መካከል ከፍተኞቹ
አራቱ ናቸው አሉት ።
፲፫. ስማቸውም አጵሎስ ዴርሜስ አቴና ዜዉስ ይባላሉ ።
፲፬. ተጽፎ ያየኸውም ትርጓሜው ይህ ነው ።
፲፭. ድዮቅልጥያኖስ እንደ አደረገ ስለነዚህ ጣዖታት ብትሰግድላቸው በዓለም ብታደርግላቸው መንግሥትህ
ትቀናለች ትጸናለች በጦር ሜዳም ጠላትህን ታሸንፋለህ እነሱም ይረዱሀል ማለት ነው አሉት ።
፲፮. ንጉሡም እሺ እኔ ለአማልክት እሰግዳለሁ በዓልም አደርግላቸዋለሁ አላቸው ።
፲፯. ሐሪክና ኤሬንዮስም ከንጉሡ ዘንድ ደስ እያላቸው ወጡ ።
፲፰. የቴዎድሮስ በናድልዮስ አገልጋይ የነበረው አውስግንዮስ የሚባል አንድ ጃንደረባ ነበር ። ሲማር በነበረ
ጊዜም አብሮት ነበር በሕይወቱ ዘመንም ሁሉ ከእሱ አልተለየም ።
፲፱. ቴዎድሮስ በናድልዮስም የነቢያትን መጽሐፍና ትርጓሜውን የክርስቶስን ሕግም ሲማር ሰምቷል ።
፳. እሱም ለአለቃው ሲያስተምሩት የሰማውን ሁሉ ለብዙዎች አስተምሯል ።
፳፩. ያም ጃንደረባ ወደ ቁስጠንጢኖስ ገባ ንጉሥ ሆይ ሐሪክንና ኤሬንዮስን አትስማቸው ሐሠተኞች ናቸውና
የነገሩህም ሐሠት ነውና ።
፳፪. ከክርስቶስ ሕግ በቀር መልካም ሕግ የለም አለው ።
፳፫. ከዚህም አያይዞ ነቢያት ስለ ክርስቶስ የተነበዩትን ሁሉ ነገረው ትርጓሜውንም ገለጠለት ።
፳፬. ንጉሥም አውስግንዮስ በነገረው አመነ በክርስቶስም ደስ አለው ።
፳፭. ሐሪክና ኤሬንዮስም አውግስንዮስ የንጉሡን ልብ እንደለወጠው ክርስቶስንም ወደማመን እንደመለሰው
ሰሙ ።
፳፮. ሐሪክና ኤሬንዮስም የጣዖታት ካህናትን ሰበሰቡ በራሳቸውም ላይ አመድ ነሰነሱ ወደ ንጉሥም ገቡ
እንዲህም አሉት ። ንጉሥ ሆይ እንዴት በአንድ ጃንደረባ አገልጋይ ሰው የሮምን መንግሥት ታጠፋለህ
በአማልክት ኃይል የድዮቅልጥያኖስ መንግሥት እንደጸናች እንደቀናች አላየህምን ።
፳፯. አሁንም ይህን ጃንደረባ አገልጋይ እንግደለው ፍቀድልን አንተን አሣስቷልና አሉት ።
፳፰. ንጉሡም እንዲህ አላቸው ይህ ነገር ዛሬ አይሆንም ወደ እሥር ቤት እናግባውና በአማልክት ኃይል
አምነንም ወደ ጦርነቱ እንሒድ ቁዝን አረሚንም እንዋጋቸው ።
፳፱. ድል ከአደረግናቸው እኔም ለአማልክት እሰግዳለሁ በዓልም አደርግላቸዋለሁ ጃንደረባውንም ያን ጊዜ
እንገድለዋለን ።
፴. እኛ ድል ከሆን ደግሞ እኔ በክርስቶስ አምናለሁ ።
፴፩. የጣዖታት ካህናትም እሺ ይሁን አሉ ።
ምዕራፍ ሐያ
፩. ንጉሥ ቁስጠንጢኖስም ሠራዊቱን ሰበሰበ ለጦርነትም ተዘጋጀ ከቁዝና ከአረሚ ጋርም ሊዋጋ ሔደ ከሮም
ወገንም ብዙዎች ሞቱ ።
፪. ቁስጠንጢኖስንም ከጠላቶቹ ወገን ከራስ ጠጉሩ የሚበዙ ከበቡት እግዚአብሔርም በአገልጋዩ በቴዎድሮስ
በናድልዮስ እረድቶ ከሰልፍ መሀል አወጣው ከሞትም አዳነው ።
፫. ቁስጠንጢኖስንም ከቁዝ ሠራዊት አንዱ የተሸከመው መስሎት ነበር ።
፬. ቴዎድሮስ በናድልዮስም አወቅኸኝን እኔ ማነኝ አለው ።
፭. ቁስጠንጢኖስም አላወቅሁህም አንተ ማነህ አለው ።
፮. ያ ተገልጦ የረዳው ያዳነው ሰውም እንዲህ አለው ። እኔ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነኝ እንዴት በአማልክት
ታምነህ ለጦርነት ወጣህ ሠራዊትህንስ እንዴት አጠፋህ እኔ በፈጣሪየ ኃይል በቸርነቱም ከሰልፍ አወጣሁህ
ከከበቡህ ከጠላቶችህ እጅም አዳንኩህ ስለወደድከኝም ልረዳህ እግዚአብሔር ላከኝ እኛ ልጆች ሣለን እንማር
በነበርንበት ጊዜም ጓደኞች ነበርን ።
፯. አሁንም በክርስቶስ እመን እሱ ይረዳሀል አውስግንዮስ የነገረህ ሁሉ እውነት ነው ቃሉን ሰማው አንተ አሁን
ቆመህ ባለህበት በዚች ቦታ ላይ ከተማ ሥራ በስምህ ትጠራ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደህ የክርስቶስን መስቀል
ከተቀበረበት አውጣ ።
፰. አሁንም ተወኝ ወደ ሠራዊትህ ልሔድና የተረፉትን ልሰብስባቸው አለው ።
፱. ይህንንም ብሎ ቁስጠንጢኖስን ትቶት ወደ ቁዝና ወደ አረሚ ሔደ ።
፲. እንዲህ እያለም ድምጹን አሰማ እኔ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ነኝ ለአጠፋችሁ መጣሁ ።
፲፩. ቁዝና አረሚም ሸሹ ከሠራዊቶቻቸውም ብዙዎች እየፈሩ እየተጨነቁ አለቁ ።
፲፪. ከሮም ሠራዊት የተረፉትም በመንገዳቸው እያዘኑ መመለስ ጀመሩ ንጉሣቸውም የሞተ መስሏቸው ነበር

፲፫. ጥቂት እንደሔዱም ንጉሣቸውን አገኙት ደስ አላቸው እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ።
፲፬. ንጉሡም ሮማውያን ድል ሆኑ ብለው ለማንም ቢሆን አንዳች ነገር እንዳይናገሩ አዘዘ ።
፲፭. ይህንንም ያዘዘ የጣዖታቱ ካህናት እንዳይሸሹና እንዳይደበቁ ነው ።
፲፮. ንጉሡም ወደ አንጾኪያ በደረሰ ጊዜ ወደ ጣዖታቱ ካህናት ላከ እንዲህ ብሎ እነሆ በአማልክት ኃይል
ጠላቶቻችንን ድል አድርገናቸዋል ደስ ብሎናል አሁንም ተዘጋጁ የሚያስፈልገውን ሁሉ አዘጋጁ ለአማልክት
እንስገድ በዓልም እንድናደርግላቸው ።
፲፯. የጣዖታትም ካህናትም በሰሙ ጊዜ ወደ እስር ቤት ወደ አውስግንዮስን ለመታረድ ተዘጋጅ እናርድሀለን
ሥጋህንም ለጣዖታት መሥዋዕት እናደርጋለን አሉት ።
፲፰. አውስግንዮስም አዘነ አለቀሰ ኃዘኑና ልቅሶው ግን ሞትን ስለ መፍራት አይደለም ሥጋህን ለጣዖታት
መሥዋዕት እናደርጋለን ስለ አሉት ነው እንጂ ።
፲፱. በልቡም ጌታየ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሥጋየ ለጣዖት መሥዋዕት እንዳይሆን አዝናለሁ እንጂ ስለ ስምህ
ሞትን እንደማልፈራ አንተ ታውቃለህ አለ ።
፳. በሌሊትም ሊጸልይ ተነሣ እንዲህም አለ አቤቱ መከራ የሚያጸኑብኝ እንዴት በዙ ብዙዎች በእኔ ላይ ቆሙ
ብዙዎችም ሰውነቴን አምላክሽ አያድንሽም ይሏታል ። አንተስ አምባየ መጠጊያየ ራሴን ከፍ ከፍ
የምታደርግልኝ ክብሬ ነህ ። ቃሌ ወደ እግዚአብሔር ነው ጮህሁ ከመመስገኛው ተራራም ሰማኝ እኔ ተኛሁ
አንቀላፋሁ ። ተነሣሁም እግዚአብሔር አስነሥቶኛልና። ከከበቡኝ በእኔ ላይ ከተነሡት ከብዙ አሕዛብ
አልፈራም ። አቤቱ አምላኪየ ተነሥ አድነኝ ። በከንቱ የሚጣሉኝን ሁሉ አንተ አጥፍተሀቸዋልና ። የኃጥአንን
መንጋጋም ሰብረሀልና የእግዚአብሔር ትድግና በረከትህም በሕዝብህ ላይ ነው አሜን ።
፳፩. ይህን መዝሙር እስከ መጨረሻው ጸልዮ በፈጸመና አሜን ባለ ጊዜም ።
፳፪. እንሆ የእግዚአብሔር መልአክ ታየው እንዲህም አለው ። አውስግንዮስ ሰላም ለአንተ ይሁን አትዘን
ለመታረድ ተዘጋጅ እናርድሀለን ሥጋህንም ለጣዖታት መሥዋዕት እናደርጋለን ያሉህ በእግዚአብሔር ፍርድ
እነሱ ይጠፋሉና የጣዖታትን ካህናትም እጃቸውን እግራቸውን እያሰሩ ወደ እሳት ሲጨምሯቸው አንተ
ታያቸዋለህ ።
፳፫. ጣዖታቱም በመዶሻ በመደቆሻ ራሳቸውን ይቀጠቅጣሉ ።
፳፬. አንተ ግን ዛሬ ትድናለህ ።
፳፭. ነገር ግን ከጥቂት ቀን በኋላ ጥቂት መከራ ያገኝሀል ጌታ ክርስቶስም ያድንሀል አለው ።
፳፮. መልአክ ይህንን ነገረውና ከዚህ በኋላ ወደ ሰማያት ዐረገ ።
ምዕራፍ ሐያ አንድ
፩. ንጉሡ ቁስጠንጢኖስም ወደ አንጾኪያ ከተማ ደረሰ ።
፪. ሐሪክና ኤሬንዮስም የጣዖታት ካህናት ሁሉ የክብር ልብሶቻቸውን ለበሱ ንጉሡንም ሊቀበሉ ወጡ ።
፫. ንጉሡም አውስግንዮስን ቶሎ አምጡልኝ አለ ።
፬. ሔደውም እንደታሠረ እየደበደቡ አመጡት ።
፭. ንጉሡም በአየው ጊዜ አዘነለትና ፍቱት አለ ።
፮. ንጉሡም ከፈረስ ወርዶ እንዲህ አለው ወንድሜ ይቅር በለኝ ወዲያውም ባርከኝ በአንተ ምክንያት ኢየሱስ
ክርስቶስ አበርትቶኛል መንግሥቴንም አጽንቷታል ።
፯. ያንጊዜም ንጉሡ የጣዖታትን ካህናት ያዙ ብሎ አዘዘ ያዟቸው እጃቸውን እግራቸውን አሠሯቸው
የአውሰግንዮስን ሥጋ ሊጠብሱ በአነደዱት እሳት ውስጥም ጣሏቸው ።
፰. ንጉሥ ቁስጠንጢኖስም የጣዖታትን ቤት እንዲያፈርሱ የሐሠት ሥራ የሆኑ ጣዖታትንም በድጅኖ በመዶሻ
እንዲቀጠቅጧቸው እና እንዲሰባብሯቸው ሠራዊቱን አዘዘ ።
፱. የጣዖታትንም ቤቶች በረበሩ ሰው ሰራሽ የሆኑ ጣዖታትንም ሰባበሩ በየጣዖታቱ ቤትም ብዙ ወርቅና ብር
አገኙ ስንዴን እንደሚሰፍሩም በዕንቅብ ሰፈሩት ።
፲. ገንዘቡንም ለንጉሥ ቁስጠንጢኖስ ወሰዱለት ንጉሡም ለድሆች ለጦም አዳሪዎች ሠጠው ከነዳያን
በተረፈውም ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራበት ።
፲፩. ንጉሡ ቁስጠንጢኖስም ሁለት መስቀል አሥራ አንዱ የወርቅ አንዱን የብር በየሔደበትም መንገድ ሁሉ
የወርቁን መስቀል ከፊቱ የብሩን መስቀል ከኋላው ይይዙለት ነበር ።
፲፪. ንጉሡ ቁሰስጠንጢኖስም አንድ ቄስ አገኘ አዋቂ መጽሐፍትን ሁሉ የተማረ ትሑትና የዋሕ ነበር ስሙም
ጴጥሮስ ይባል ነበር ሊቀ ጳጳሳት አድርጎ ሾመው ንጉሡም ስለ ትሕትናውና ስለንጽሕናው ስለ ደግነቱና ስለ
ሃይማኖቱ ወደደው እጅግም አከበረው ።
፲፫. ሊቀ ጳጳሳቱም ኤጲስ ቆጶሳትን ቀሳውስትን ዲያቆናትን አናጉንስጢሳትን ሾመላቸው አብያተ
ክርስቲያናትንም ባረከላቸው።
፲፬. በንጉሡ በቁስጠንጢኖስም ዘመን በአንጾኪያ ከተማ ጾምን ጸሎትን የሚጾሙባቸውን የሚጸልዩባቸውን
ጊዜውን ሰዓቱን ወሰነላቸው ።
፲፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ቁስጠንጢኖስን በአዳነው ጊዜ ከጦር ሜዳም በአወጣው ጊዜ አሁን አንተ
በቆምክባት ቦታ ከተማ ሥራ በአንተ ስም ሰይማት ብሎት ነበር ።
፲፮. ቁስጠንጢኖስም በዚያ ስፍራ ታላቅ ከተማ ሠራ በስሙም ቁስጥንጥንያ ብሎ ጠራት ።
፲፯. በውስጧም ብዙ አብያተ ክርስቲያናት ሠራ በዚያም በቴዎድሮስ በናድልዮስ ስም ታላቅ ቤተክርስቲያን
ሠራ ቤተ መንግሥቱንም ከዚያ አደረገ ።
፲፰. ወደ አንጾኪያ ከተማም ላከ የቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስን ሥጋውን የቸነከሩበትን ችንካሮች ሰይፉንም
ጦሩንም አስመጣ ።
፲፱. በታላቂቱ ከተማ በቁስጥንጥንያ በቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ስም በአነፃት ቤተክርስቲያን ውስጥ
አስቀመጣቸው ።
፳. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ከሞተ ጀምሮ ሰይፉን ከሰገባው ሊያወጣ የቻለ አልነበረም በሕይወት ሣለ ጌታየ
ኢየሱስ ክርስቶስ ሰይፌን ለሌላ አትስጥብኝ ብሎ ጸልዮ ነበርና ።
ምዕራፍ ሐያ ሁለት
፩. ብዙ ዘመንም ከኖረ በኋላ ንጉሥ ታመመ ለሞትም ደረሰ ልጁንም ጠርቶ እግዚአብሔር በመንግሥት ዙፋን
ላይ ያስቀመጠህ እንደሆነ ወደ ኢየሩሳሌም ሂደህ የክርስቶስን መስቀል ፈልግ አለው ።
፪. ቁስጠንጢኖስም ሞተ በዚፋኑም በእሱ ፈንታ ልጁን አነገሡት ስለ አባቱ ፍቅርና ስለ አባቱ ሃይማኖትም
ጽናትም በአባቱ ስም ቁስጠንጢኖስ ብለው ሰየሙት እግዚአብሔርም የልጁን መንግሥት አጸና ።
፫. በዚያ ወራትም ጊዮርጊስ የሚባል አንድ ባለፀጋ አረማዊ ሰው ነበር ።
፬. የንጉሡንም አማካሪዎች በገንዘብ ያታልላቸው ጀመር ሣይከለከል ገብቶ ከንጉሡ ጋር እንዲበላ ይነግሩለት
ዘንድ እንዳለውም ሆነ ።
፭. ንጉሡ ወደደው ከሱ ጋርም ሲበላ ሲጠጣ ኖረ ።
፮. አረማዊ ጊዮርጊስ ግን ንጉሥን ከቀናችው ሃይማኖት ሊመልሰውና ለጣዖት ሊያሰግደው ይወድ ነበር ።
፯. ዘወትርም ንጉሡን ያባብለው ነበር ንጉሡ ታናሽ ሕፃን ነበረና ።
፰. የንጉሡ እናት ንግሥት እሌኒም ታዝን ነበር እንዲህም ትለው ነበር ልጄ ቁስጠንጢኖስ ወደ ኢየሩሳሌም
ልትሄድ ንጉሥ አባትህ እንደ አዘዘህም የክርስቶስን መስቀል ልታወጣ ይገባሀል ።
፱. ንጉሡ ግን የእናቱን ቃል አልሰማም ።
፲. ከዕለታት አንድ ቀንም አረማዊ ጊዮርጊስ ከንጉሡ ጋር ሲበላና ሲጠጣ አውስግንዮስ ወደ ንጉሥ ገባ
ንጉሡንም እንዲህ አለው ንጉሥ ሆይ የዚህ ዓለም መብልና መጠጥ ምን ይጠቅምሀል የሚያልፍ አይደለምን ።
፲፩. በምድር ያለ ክብር ብልፅግና መንግሥትም ኃላፊ ነው ሰማይና ምድር ያልፋል መንግሥተ ሰማያት ግን
የማያልፍ የማይጠፋ ነው ።
፲፪. ንጉሥ ሆይ የአባትህን ትእዛዝ ፈጽም እንጂ ይህ ሁሉ ማለት የዚህ ዓለሙማ ይጨመርልሀል ።
፲፫. አረማዊ ጊዮርጊስም ንጉሡን መጥፎ አገልጋይ በንጉሥ ፊት እንዲህ ሲናገር ሞት ይገባዋል አለው ።
፲፬. ያንጊዜም ንጉሡ አውስግንዮስን ወደ ውጭ አውጥተው እንዲገድሉት አዘዘ ።
፲፭. ሊገድሉትም ወሰዱት ቴዎድሮስ በናድልዮስም ወደ እሱ ወረደ በመንፈሳዊ ፈረሱ ላይም ተቀምጦ ነበር
አራት መላእክት በሰው አምሳል ይከተሉት ነበር ።
፲፮. ይህን ሰው የምትገድሉት በምን ኃጢአትና በደል ነው አላቸው ።
፲፯. ጭፍሮችም በንጉሡ ፊት ክፉ ነገር ስለተናገረ እንድንገድለው ንጉስ አዝዞን ነው አሉት ።
፲፰. ቴዎድሮስ በናድልዮስም አትግደሉት እኔ ሔጀ ለንጉሥ እነግረዋለሁ አላቸው ።
፲፱. አንተውም ንጉሡን እንፈራለንና አሉት ።
፳. ቴዎድሮስ በናድልዮስም እኔ አድናችኋለሁ አላቸው ።
፳፩. ወደ ንጉሡም በሔደ ጊዜ ንግሥት እሌኒን ከበር ቆማ ስታዝን አገኛት ።
፳፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ከፈረሱ ላይ እነዳለ ንግሥት እሌኒ ለምን ቆመሽ ትተክዣለሽ አላት ።
፳፫. ስለ አውስግንዮስ እየለመንኩ ከልጄ ዘንድ ቆሜያለሁ አለችው ።
፳፬. ሒጂ አትዘኚ አላት ሔደች ።
፳፭. ቴዎድሮስ በናድልዮስም በፈረሱ ላይ ሆኖ ወደ ንጉ ገብቶ ንጉን ቁስጠንጢኖስን አውስግንዮስን
የምትገድሉት በደሉ ምንድን ነው አለው ።
፳፮. ንጉሡ ግን የሚነግረውን አልሰማም ያነጋገረው በመላእክት ቋንቋ ነበርና ።
፳፯. ዳግመኛም በሮማይስጥ ቋንቋ አነጋገረው ።
፳፰. ንጉሡም ጊዮርጊስም ሰሙ ።
፳፱. አረማዊ ጊዮርጊስም ተነሥቶ ክፉ አገልጋይ በንጉሥ ፊት የማይገባ ነገር ሲናገር ሞት ይገባዋል አለ ።
፴. ቴዎድሮስ በናድልዮስም አረማዊ ጊዮርጊስን በጦር ከደረቱ ላይ ወጋው ምግቡን በአፉ እንደጎረሰ ወዲያውኑ
ሞተ ።
፴፩. ዕሌኒም ስለ ልጅዋ ጮኸችና እየሮጠች ገባች ።
፴፪. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ንጉሡን ቁስጠንጢኖስን እንዲህ አለው ። አባትህ ወዳጄ ባይሆን ኖሮ አንተንም
ባልማርኩህ ነበር አለው ።
፴፫. አሁንም አውስግዮስ የነገረህ ሁሉ እውነት ነውና አንተም እሱ እንደአዘዘህ አድርግ ወደ ኢየሩሳሌም ሔድ
የክርስቶስንም መስቀል አውጣ ።
፴፬. ቴዎድሮስ በናድልዮስም ይህን ተናግሮ እያዩት ሐደ ።
፴፭. ያንጊዜም ንጉሡ ቁስጠንጢኖስ በአረማዊ ጊዮርጊስ ላይ ከተደረገው ኃይልና ተአምር የተነሣ ደነገጠ ።
፴፮. ከቅዱስ ሰማዕት ከቴዎድሮስ በናድልዮስ አነጋገር ጣዕም ከግርማውና ከደምግባቱ የተነሣ አደነቀ ።
፴፯. በሥጋና በነፍስ ላይ ሥልጣን ላለው ለአንድ አምላክ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ሰገደ ።
፴፰. ስለ ሥራውም ተጸጸተ መልዕክተኞችንም ላከ አውስግንዮስንም እንዳይገድሉት አዘዘ ።
፴፱. በዚያች ቀንም ታማኙ ሰማዕት አውስግንዮስ በእውነተኛው አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት በሰማዕቱ
በቴዎሮስ በናድልዮስ ረዳትነት ከሞት ዳነ ።
፵. ለእኛም ሰማዕቱን ቴዎድሮስ በናድልዮስን የመረጠው ከፍ ከፍ ያደረገው የአንዱ አምላክ የአብ የወልድ
የመንፈስ ቅዱስ ይቅርታውና ቸርነቱ ይደረግልን ።
፬፩. ስለክርስቶስ መስቀል ሰማዕት የሆነው የቅዱስ ቴዎድሮስ በናድልዮስ ፀሎቱና በረከቱ ከሁላችን ከሕዝበ
ክርስቲያን እና ከሀገራችን ከኢትዮጵያ ጋር ይሁን ። ለዘለዓለሙ አሜን ።

You might also like