You are on page 1of 3

ሐዋርያዊ መልሶች - Apostolic Answers

ተከታታይ የክርስትና ትምህርት መስጫ አጋዥ ጽሑፍ - 4

የክርስቶስን ትምህርት እንዴት(ከየት) እናገኘዋለን..??

ቅዱስ ትውፊት
አስቀድመን እንግዲህ ቀጥታ ትውፊት የሚለውን ነገር ለመረዳት ያህል በአጭሩ ቅብብሎሽ ማለት ነው። ለምሳሌ የሆነ ትምህርት
ከሆነ ትውልድ ወደ ቀጣዩ ትውልድ በተለያየ መንገድ እየተላለፍ ሲሄድ ይሄ ቅብብሎሽ ትውፊት ይባላል። ትውፊትን በዋናነት
ለሁለት መክፈል እንችላለን.. ይህም የእግዚአብሔር መገለጥ ያለበት ቅዱስ ትውፊት እና የእግዚአብሔር መገለጥ የሌለው ተራ
ትውፊት ነው። መገለጥ የሌለው ትውፊት ብዙ ጊዜ ሰዋዊ ትውፊት ነው.. ስለዚህም መነሻው ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከሰዎች
ብቻ ነው። ይህ ሰዋዊ ትውፊት የተለያየ ቅርጽ ሊኖረው ቢችልም እኛ ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ከተቀመጠልን ከአይሁዳውያን
ትውፊት አንጻር ከሁለት በኩል ልናየው እንችላለን.. ይህም አንደኛው ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ምንም ግንኙነት የሌለውና
ከእለት እለት ኑሮዋቸው ጋር ሊገናኝ የሚችል ትውፊት ብቻ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የምንመለከተው ሰዋዊ ትውፊት
የእግዚአብሔርን ቃል የሚሽረውን ነው።
በማርቆስ ወንጌል 7 ላይ ካለው ተነስተን የተወሰነች ማብራሪያ እናስቀምጥ፡
1. በአይሁዳውያን ዘንድ ለምሳሌ እጅን ታጥቦ መብላት የሽማግሌዎች ወግ(ትውፊት) እንደሆነ ይነገራል.. ይህ ከመገለጥ ጋር
ምንም የማያገናኘው የሰዎች ሥርዓት ብቻ ነው.. ታድያ ግን አንዳንድ ጊዜ አይሁዳውያን ይህንን ሰዋዊ ትውፊት አጥብቀው
ሲይዙ በጎን ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል ቸል ይሉም ነበር። ለማንኛውም ከትውፊትነቱ አንጻር ይሄ ቢደረግ ሥጋን የሚጠቅም
መልካም ነገር ነው ግን ሁሉን በአግባቡ ሲሆን መልካም ይሆናል። እንዳልኳቹ ግን ከሃይማኖት ጋር ምንም አያገናኘውም።
2. ታድያ እዛው የማርቆስ ወንጌል ምእራፍ ላይ ጌታ ኢየሱስ አይሁዳውያንን ሌላ የራሳቸውን ትውፊት በመጥቀስ
የእግዚአብሔርን ቃል እንደሻሩ ሲናገራቸው እንመለከታለን። ይህም አባትህን እና እናትህን አክብር የሚለውን ትእዛዝ ልጆች
ሁሉ አባቶቻቸውን እናቶቻቸውን በመርዳትም(በገንዘብ) ጭምር ሊተገብሩት የሚገባ ሲሆን በቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት
እነርሱ ግን ለእናት ለአባት የሚገባውንም ወደ እነርሱ ለመሳብ ሕግን ያስቀምጡ ነበር። ያው ወደ ቤተ መቅደስ የሚገባው ሁሉ
ለአገልጋዮቹ ስለሚሆን ማለት ነው። ስለዚህም የራሳቸውን ኪስ ለማወፈር የራሳቸውን ትውፊት በመያዝ ዋናውን
የእግዚአብሔርን ቃል ሲሽሩበት እንመለከታለን። ቅዱስ ትውፊት ስንል ደግሞ በተለየ መልኩ ምንጩ እግዚአብሔር ሆኖ
ከእግዚአብሔር ለሰዎች ሲሰጥ.. የተቀበሉትም ሰዎች ወደ ቀጣዩ ትውልድ ሲያስተላልፍ ይህንን ቅብብሎሽ(ትውፊት) ቅዱስ
ትውፊት እንለዋለን።
ቅዱስ ትውፊት የቤተ ክርስቲያን ሕይወቷ ነው(Tradition and Orthodoxy, Fr Tadros Malaty) እናም ከቅዱስ
ትውፊት ውጪ የሆነ ሕይወት የላትም። ቅዱስ ይሁዳ በመልእክቱ ሲናገር “ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለተሰጠ ሃይማኖት”
በማለት ይናገራል። ይህም የተሰጠው ከእግዚአብሔር ዘንድ ሲሆን የተሰጠውም ወደ ቀጣዩ ትውልድ እየተላለፈ እስከ አለም
ፍጻሜ ይሄዳል ማለት ነው። የቅብብሎሹ መነሻ ራሱ ቅዱሱ እግዚአብሔር ነው.. ስለዚህም ይህ ቅብብሎሽ ቅዱስ ነው። ልክ
መጽሐፍ ቅዱስን “ቅዱስ” የሚያስብለው ምንጩ ቅዱሱ መንፈስ መሆኑ እንደሆነ ሁሉ ማለት ነው። እስቲ ይህንን ቅብብሎሽ
የተወሰኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን አንስተን እንመልከት፡
ይሁዳ 1: 3 - ወዳጆች ሆይ፥ ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ፥ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ
ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ። (በዚህ ክፍል ላይ እንደምንመለከተው
ሃይማኖት(እምነት) በራሱ የተሰጠ ነው። ትውፊት ደግሞ መቀበል እና ማቀበል ወይም ቅብብሎሽ እንደሆነ ተመልክተናል)
ገላ 1፡ 11-12 - ወንድሞች ሆይ፥ በእኔ የተሰበከ ወንጌል እንደ ሰው እንዳይደለ አስታውቃችኋለሁ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ገልጦልኛል
እንጂ እኔ ከሰው አልተቀበልሁትም አልተማርሁትምም። (እዚህ ላይ ቅዱስ ጳውሎስ ግልጽ እንደሚያደርገው ወጌልን ወይም
ትምህርትን ከሰው አልተቀበለም ይልቁንም ከጌታ እንጂ። ስለዛ ቅብብሎሹ ከሰው አይጀምርም ከጌታ እንጂ)
1 ቆሮንቶስ 11፡ 23 - ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና (ቅዱስ ጳውሎስ ከጌታ የተቀበለውን
ትምህርት አሳልፎ ደግሞ ለሌሎች ይሰጣል። ከጌታ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ፤ ከጳውሎስ ደግሞ ወደ ሌሎች። ቅብብሎሽን
አስተዋልክ..??)
2 ጢሞቴዎስ 2፡ 2 - ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች
አደራ ስጥ። (እዚህ ላይ ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ የሰጠውን እሱ ደግሞ ለሌሎች ለታመኑ ሰዎች አደራ እንዲሰጥ
ሲነግረው እንመለከታለን። ስለዚህም ከጌታ ወደ ጳውሎስ፤ ከጳውሎስ ወደ ጢሞቴዮስ፤ ከጢሞቴዎስ ደግሞ ወደሌሎች
የታመኑ ሰዎች። ዛሬ ላይ የደረሰው ሃይማኖት እንዲሁ አይደለም.. ይልቁንም እንዲህ ባለ ቅብብሎሽ ውስጥ አልፎ ነው። ያለ
ትውፊት ቤተ ክርስቲያን ሕይወት የላትም የሚለውን አስተዋልክበት..??)
1 ቆሮንቶስ 11፡ 2 - ወንድሞች ሆይ፥ በሁሉ ስለምታስቡኝና አሳልፌ እንደ ሰጠኋችሁ ወግን(ትውፊትን) ፈጽማችሁ ስለ
ያዛችሁ አመሰግናችኋለሁ። (ይህ የሚተላለፈው ትውፊት ደግሞ ጅማሬው ከራሱ ከእግዚአብሔር ነውና ይህንን ትውፊት
አሳልፎ እንደሰጣቸው ፈጽመው በመያዛቸው ያመሰግናቸዋል። የትውፊትን ወሳኝነት አስተዋልክበት..??)

ቅዱስ ትውፊት በምን መልኩ ተላለፈልን..??


ቅዱስ ትውፊት የተላለፈልን በጽሑፍ እና በቃል ነው። ሐዋርያት አብዛኛዎቹ ምንም ጽሑፍ ሳይጽፉ አልፈዋል ያ ማለት ግን
የእግዚአብሔርን ቃል አላስተላለፉልንም ማለት አይደልም.. ይልቁንም በጽሑፍ ሳይሆን በቃል ብቻ አስተላለፉ እንጂ።
ሐዋርያት መሠረት ተብለዋል.. ለምሳሌ በራዕይ መጽሐፍ እንዲህ የሚል አለ፡ “ለከተማይቱም ቅጥር አሥራ ሁለት መሠረቶች
ነበሩአት፥ በእነርሱም ውስጥ የአሥራ ሁለቱ የበጉ ሐዋርያት ስሞች ተጽፈው ነበር።”(ራዕ 21፡14) - (አስራ ሁለቱ ሃዋርያት
መሰረቶች ከሆኑ መቼስ ወንጌልን በማስተላለፍም ጭምር ነው መሠረት የሚባሉት.. እንግዲያውስ ከእነዚህ ሐዋርያት ውስጥ
ከነበሩት ውስጥ የእንድርያስ፣ የፊሊጶስ፣ የበርተሎምዮስ፣ የማትያስ እንዲሁም የልብድዮስ እና የቀነናዊው ስምዖን ትምህርቶች
ወዴት አሉ..?? ወይስ አላስተማሩም..?? በአጭሩ አዎ አስተምረዋል ግን ትምህርቱን በጽሑፍ አላደረጉትም.. ይልቁንም በቃል
እንጂ። ስለዛ አንዴ በቃል ያስተማሩት ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ተገልጦ ይኖራል።) ታድያ ግን ያልጻፉት
ሐዋርያት ብቻ ሳይሆኑ የጻፉትም ቢሆኑ በሕይወት ዘመናቸው ከሰበኩት ውስጥ እጅግ በጥቂቱ በጽሑፍ ደግሞ አስተላልፈዋል
ነው። ለምሳሌ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፡ “እንድጽፍላችሁ የምፈልገው ብዙ ነገር ሳለኝ በወረቀትና በቀለም ልጽፈው አልወድም፥
ዳሩ ግን ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ወደ እናንተ ልመጣ አፍ ለአፍም ልናገራችሁ ተስፋ አደርጋለሁ።”(2ዮሐ 12) ቅዱስ
ዮሐንስ ይጽፍላቸው ዘንድ የሚወደው ብዙ ነገር እንዳለ ያስቀምጣል። ታድያ ግን ከመጻፍ ይልቅ አፍ ለአፍ(በቃል) ይነግራቸው
ዘንድ ደግሞ ተስፋ እንደሚያደርግ ይነግረናል። ቅዱስ ጳውሎስም እንዲህ ይላል፡ “ከእኔ የተማራችሁትንና የተቀበላችሁትን
የሰማችሁትንም ያያችሁትንም እነዚህን አድርጉ፤ የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል።”(ፊል 4፡9) በዚህ ክፍል ላይ
ሃዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከውህኒ ቤት ሆኖ ደብዳቤን ሲጽፍላቸው “የሰማችሁትን ያያችሁትን” በማለት የተናገረው አስቀድሞ
በአካል አግኝቶ ስላስተማራቸው ነው ይሄም በሃዋ 16፡11 ጀምሮ የተገለጸ ሲሆን ይህንን የሰሙትን እንዲያደርጉ ሲናገራቸው
እንመለከታለን። ስለዚህም በዋናነት በቃል እና በጽሑፍ ይህ ትውፊት ተላልፎልናል ማለት ነው። ለዛም ነው ቅዱስ ጳውሎስ
እንዲህ በማለት የሚናገረው፡
2 ተሰሎንቄ 2፡ 15 - እንግዲያስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ጸንታችሁ ቁሙ፥ በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን
የተማራችሁትን ወግ(ትውፊት) ያዙ። በቃልም በመልእክትም(በጽሑፍም) የተማሩትን ወይም የተቀበሉትን ትውፊት እንዲይዙ
ሲናገር እንመለከትበታለን ስለዚህም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የቃሉም የጽሑፉም ትምህርት ጸንቶ ይኖራል ማለት ነው። እስከ
መቼ ያልን እንደሆነ ከላይ እንዳልነው እስከ ዓለም ፍጻሜ ነው። ለዛም ነው ጌታ እንዲህ የሚለው፡
ማቴዎስ 28፡ 19-20 - እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥
ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ
ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ። - ጌታ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከእኛ ጋር የሚኖረው በዚህ ቅብብሎሽ ውስጥ ነው። ታድያ ግን
እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ የዚህ ትውፊት ጠባቂው መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ልብ ልንለው ይገባል። ምክኒያቱም ጌታ እንዲሁ
ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች ጥሎን የሄደ ሳይሆን ከእኛ ጋር ለዘላለም ይኖር ዘንድ መንፈስ ቅዱስን በመላክ ነው። ጌታ
ሐዋርያቱን ሲያጽናና እንዲህ አለ፡
ዮሐንስ 14፡ 15-16 - ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ
ይሰጣችኋል

You might also like